March 7, 2013
14 mins read

አሃዳዊ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴና ችግሮቹ በ ኢትዮጵያ –

BD

ከ ብርሃኔ አሰበ አለሁድረስ

ትምህርት የችግር ፈችነትን አቅምና ባህል ለማጎልበት እንዲያስችል የትምህርት ይዘት፟_ የስርአተ ትምህርት አወቃቀርና የትምህርት አቀራረብ የትምህርት ቅስሞሽንና ሳይንሳዊነትን የተከተለ መሆን አለበት።

ጥራት ያለውና ደረጃውን የጠበቀ ትምህርት በየደረጃው በመስጠት ትምህርት የዕውቀት አምድ የሆኑትን ክህሎት፣ ጥራትና በራስ መተማመንን ማምጣት ካልቻለ የሃገር እድገትና ብልጽግና አይታሰብም። ትምህርት ገና ከጅምሩ ብቁ ዜጋን መፍጠር የሚያዳግተው ከሆነ እውቀትና ፈጠራን ጥበብና ክህሎትን ማቀናጀት የሚሳነው ከሆነ ትምህርት ከጊዜ ማሳለፊያነት የዘለለ ፋይዳ አይኖረውም።

በሃገራችን ኢትዮጵያ ገዥው ፓርቲ /ኢህአዴግ/ አሃዳዊ የትምህርት ስርዓትን/self-contained/ መሰጠት ከጀመረበት አንስቶ ትምህርት የኋልዮሽ ዳዴ ሲል ይታያል። አሃዳዊ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ /self containde/ ከ1 እስከ 4ኛ ክፍል የሚሰጠው ትምህርት ለጋ ህጻናት ፟ሀ፟ ብለው የትምህርትን ዑደት በሚጀምሩበት የክፍል ደረጃ አንድ መምህር ሁሉንም የትምህርት አይነት በማስተማር እንዲዘልቅ መደረጉ ዛሬ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ድረስ ላለው የትምህርት ጥራት ችግር ዋነኛው መንስኤ ነው። በዚህ የትምህርት ሳይክል ውስጥ አንድ መምህር ሁሉንም የትምህርት አይነት እያስተማረ 1ኛ ክፍል የተረከባቸውን ተማሪዎች እንዳለ ይዞ 4ኛ ክፍል ማድረሱ ባልከፋ ነበር ጥያቄው ከሃገሪቱ የመምህራን ስልጠናና ከግለሰቡ ተሰጥኦ ጋር ተያይዞ መምህሩ ሁሉንም የትምህርት አይነት ለማስተማር ምን ያህል ዕውቀትና ብቃት አለው/ት­­­

የዕውቀትችግር ውስንነት ባለው/ት መምህር ለ4 ዓመት በሌላ መምህር ሳይማሩ ትምህርት ቤት የቆዩት ምን ያህል ዕውቀት ጨብጠው ይሆን  የሚለው አሳሳቢ ጥያቄ ይሆናል፡ ይህ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ በርካታ ችግሮች ያለበትሲሆን ዋና ዋናዎቹን እንደሚከተለው እንመልከት፤

  • ሁሉንም የትምህርት አይነቶች አንድ መምህር እያስተማረ 1ኛ ክፍል የተረከባቸውን ተማሪዎች ይዞ  ለ 4ዓመት መዝለቁ መምህሩ/ሯ/ በሁሉም የትምህርት አይነት በቂ እውቀት ክህሎትና ልምድ ካለመኖሩ ጋር ተያይዞ ለ4ዓመት ያህል ትምህርት ቤት የቆዩ ተማሪዎች ብዙዎቹ መሰረታዊ የሆኑትን ማንበብ፣ መጻፍ፣ ማስላት የማይችሉና የት/ቤት ደጃፍን ካረገጠው ወንድማቸው/እህታቸው ያልተሻሉ ሆነው ተገኝተዋል። ለዚህም ወላጆች 4ኛ ክፍል የደረሰው/ች/ ልጄ ትምህርትቤት ካልገባው/ ችው/ ምንም ልዩነት ስለሌለው /ላ ት/ ተመልሶ /ሳ/ 1ኛ ክፍል ይግባልኝ/ ትግባልኝ ሲሉ ይደመጣሉ።
  • በሁሉም የትምህርት ዘርፍ /አይነት/ ጥቂት ብቃቱ ያላቸው መምህራን ይኖራሉ ብለን ብንገምት እንዃን የተማሪ መምህራን ጥምርታው ሲታይ ከፍተኛ  መሆንና በአንድ ክፍል ውስጥ በርካታ ተማሪዎች በመኖራቸው አንዳንድ ከአደጉና አሃዳዊ የሆነ ትምህርት ከሚሰጡ ሀገራት አለማቀፋዊ የተማሪ መምህራን ጥምርታ መመዘኛ ጋር ሲነጣጠር ከ 5 ጊዜ በላይ እጥፍ ሆኖ መገኘቱ ተማሪዎችን ለማብቃት ከፍተኛ ጉድለት ይታይበታል።
  • በትምህርት ሂደት ውስጥ ዋና ተዋናይ የሆኑት መምህራን አምነውበት ሳይሆን በጫና ወደ ትግበራው የገቡበት በመሆኑ  በፍላጎትና በተነሳሽነት እውቀትና ክህሎትን በአግባቡ የማስረጽ ችግር ይታያል ።
  • ለመማር ማስተማሩ የሚያስፈልጉ ግብኣቶች አለመሟላት
  • ለመማር ማስተማሩ ሂደት ምቹ የትምህርት ቤት ሁኔታ ያለመኖር
  • የማስተማር ሥነ ዘዴና የመጸሃፍት ዝግጅት ጉድለት የሚታይበት
  • ክ1 እስከ 4ኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች በየክፍል ደረጃው የሚጠበቅባቸውን የማንበብ፣ የመጻፍ፣ የማስላትና አካባቢን የመረዳት /ማወቅ ክህሎታቸውን ሳያዳብሩ አመት እየቆጠሩ ከክፍል ወደ ክፍል እንዲሸጋገሩ/እንዲያልፉ ይደረጋል ።  ሁሉም እንዲያልፉ promotion policyው ያስገድዳል በዚህ የትምህርት እርከን ውስጥ መጣል ክልክል ነው የሚጥል መምህር ካጋጠመም ለምን ጣልክ ተብሎ ተገምግሞ  እንዲያሳልፍ ይገደዳል ።ይህ ሂደት እስከ አሁን ባለው የትምህርት ጥራት ላይ ሊሽር የማይችል ጠባሳ ጥሎ አልፏል ።
  • ባብዛኛው ተማሪዎች 4ኛ ክፍል ከደረሱ በኋላ በቆዩበት የጊዜ ቆይታ ልክ ማግኘት የሚገባችውን እውቀትና ክህሎት ባለማግኘታቸው ንጹህ የህጻናት አዕምሮ አቸው በባዶነት ተሞልቶ ሲያገኙት ትምህርትን መጥላትና ማቋረጥ ይጀምራሉ
  • አሃዳዊ የትምህርት አሠጣጥ ዘዴ ያስከተለው ችግር ከመሰናዶ እስከ ዩኒቨርስቲ የደረሱ ተማሪዎች ሳይቀር ስማቸውን በእንግሊዘኛ   ለመጻፍ ሲቸገሩ ታይተዋል።ለአብነት አብዛኞቹ የመሰናዶ ከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች ወደ ከፍተኛ ትምህርት መግቢያ ፈተና ለመውሰድ ፎርም በሚሞሉበት ወቅት ስማቸውን በእንግሊዘኛ  ለመጻፍ ሲችገሩና መምህራንና የተሻሉተማሪዎች ስማቸውን እንዲጽፉላቸው ሲያስቸግሩ ታዝቢያለሁኝ። ይህ በዩኒቨርስቲ ተማሪዎችም  ዘንድ በስፋት እንደሚታይ አንድ ምሁር ከዚህ በፊት በጽሁፋቸው አስፍረዋል። ለዚህ መንስዔ ደግሞ ገና ከጅምሩ የትምህርት ደጃፍ ሲረገጥ የሚሰጠው አሃዳዊ የትምህርት አሰጣጥ ስረዓት ችግር ነው
  • ይህ የትምህርት ስርአት ህብረተሰቡን መምህራንንና  የተለያዩ ምሁራንን ባግባቡ ያላሳተፈና አወንታን ያላገኘ  በመሆኑ በእምነት ይዞ ለስኬት በቅንጅት መስራት አይታይበትም
  • አሃዳዊ የትምህርት ስርአትን በሚከተሉ  ሃገራት የሚያስተምሩ መምህራን በተደራጀ  መልክ ስልጠና የወሰዱና ሁለገብ እውቀትና ክህሎት ያላችው በልምድ የተካኑ መምህራን ሲሆኑ በሃገራችን ግን በለብለብ ስልጠና /በቂ/ እውቀትና ልምድ በሌላችው መምህራን ትምህርቱ እየተሰጠ በመሆኑ የትምህርት ሂደቱን በጅጉ ጎድቶታል ።

ከዚህ በላይ የተጠቀሱትዋና ዋናዎች ሲሆኑ ካለኝ የረጅም ጊዜ  የማስተማር ልምድ ተነሥቸና የሙያው ባለቤት የሆኑት መምህራን እና ሌሎች ምሁራን፣  ወላጅ በተለያየ ጊዜ  በመፍትሄነት የሚያነሷቸውንና  የራሴን ሃሳብ በማጠናከር ከዚህ እንደሚከተለው የመፍትሄ ሃሳብ እጠቁማለሁ

  • አሃዳዊ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ በሚል ብሩህ የህጻናት አዕምሮን በአንድ መምህር ሁሉንም የትምህርት አይነት እያስተማረ  4ኛ  ክፍል ማድረስ የልጆቹ ሂይወት በመምህሩ /ሯ/ ብቃት ላይ የሚወሰን በመሆኑ አንድ መምህር ሁሉንም የትምህርት አይነት በእኩል እውቀትና ፍላጎት ስለማይተገብረው  አሃዳዊ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ ቀርቶ  መምህራን በችሎታቸውና በዝንባሌያቸው የሚያስተምሩበት የትምህርት ስርዓት መቀረጽ አለበት
  • መንግስት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ያለው በትምህርት ሽፋን ላይ ሲሆን ትምህርት ጥራት ያለው/ብቃት ያለው/ የሰው ሃይል ማፍራት ካልቻለ ፋይዳ ስለሌለው ለጥራት ትኩረት መሰጠት አለበት
  • መምህራን አንድን የትምህርት ስርአት ሳያምኑበት ወደ ትግበራ በጫና  ማስገባቱ ውጤቱ የዜሮ ብዜት ስለሚሆን መምህራንና  ወላጆች የሚያነሷቸው ጥያቄዎችና አስተያየቶች ተደማጭነት ማግኘት አለበት
  • ህጻናት የሚማሩባቸው ትምህርት ቤቶች ምቹና ሳቢ መሆን አለባቸው
  • ተማሪ ተኮር የማስተማር ስነ ዘዴ ላይ ትኩረት መደረግ አለበት
  • ከ1 እስከ 4ኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች በየክፍል ደረጃው የሚጠበቅባቸውን የማንበብ፣ የመጻፍ፣ የማስላት፣ ራሳቸውንና አካባቢያቸውን መግለጽ  ሳይችሉ ሲቀሩ በየክፍላቸው ደግመው እንዲማሩ መደረግ አለበት
  • በዚህ  የትምህርት ሳይክል ውስጥ የሚገኙ ህጻናት በአግባቡ ተቀርጸው መውጣት ካልቻሉ ነጸብራቁ እስከ ላይኛው የትምህርት እርከን የሚዘልቅና ሃገሪቱ በትምህርት ዘርፍ ልታስመዘግብ ያቀደችውን ግብ ልታሳካ ስለማትችል ለዚህ የትምህርት  እርከን ኢህአዴግ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል
  • ለመምህራን ስልጠና ልዩ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል

ማጠቃለያ_ የትምህርት ስርአቱ ጥራት ባለው ትምህርት እየተመራ የሩቁን ለማየት የሚያስችል አቅም መፍጠር አለበት ።

ለዚህ ደግሞ ስረአተ  ትምህርቱ ሲነደፍ የህብረተሰቡን ፍላጎት  የመሁራንንና የሙያው  ተዋናይ መምህራንን አስተያየት መሰረት ያደረገ መሆን ይገባዋል። ይሁንጂ ኢህአዴግ ከባለሙያና ከምሁራን የሚሰጡ አስተያየቶችን በግብአትነት ይዞ ከመጠቀም ይልቅ እኔ ብቻ ትክክል ነኝ  የሚል     ግትር ሃሳብ  በመያዝ  ለትምህርት ጥራት እየሰጠው ያለው ትኩረት አናሳ ሆኖ  ይታያል።በመሆኑም ከ1 እስከ 4ኛ ክፍል የሚሰጠው አሃዳዊ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ በርካታ ችግሮች ያሉበት   በመሆኑ ኢህአዴግ በሃገር ላይ ሊያመጣ  የሚችለውን ቀውስና ምስቅልቅል ችግር በፍጥነት ተረድቶ አፋጣኝ እርምት መውሰድ አለበት።

 

 

1 Comment

  1. ብርሃኔ የጻፍከው አርቲክል በሃገራችን አሃዳዊ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ የትምህርቱን ስርአት ምንያህል እንደጎዳው
    በግልጽ ያሳየ ነው። የተቀመጡትም የመፍትሄ ሃሳቦች ሰሚ ካገኙ በጣም አዋጭ ናችው ።

Comments are closed.

Previous Story

“ድህነታቸውን ህዝቡ ላይ አራግፈው ለራሳቸው ባለፎቆች ሆነዋል..” ስማቸው ያልተገለጸ እናት

Next Story

ለታማኝ ሚዲያ ታማኝ አምባሳደር

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop