እግረ ሙቅ/እግር ብረት/ ዮሴፍ ሽፈራው(ጀርመን)

ዮሴፍ ሽፈራው(ጀርመን)

ከንጉሱ ዘመን ጀምሮ ዘውዳዊውን አገዛዝ በመቃወም የለውጥ መርህን አንግበው የተነሱትን የተማሪውን እና የሰራተኛውን ክፍል ወገኖች እንቅስቃሴ ለማኮላሸት እስር እንግልት እና ግድያ ሲፈፀም ቆይቷል።

በወቅቱ እንደ ከርቸሌ በመሳሰሉት እስር ቤቶች የታጎሩት ወገኖች በጠባብ ክፍል ከመወሰናቸውም በተጨማሪ በእግረ ሙቅ/እግር ብረት/ ታሰረው እንዲሰቃዩ ይደረግ ነበር።

ንጉሱን በሀይል በማሶገድ ወደ ስልጣን የመጣው ወታደራዊው ደርግ በስልጣን ዘመኑ የመብት ጥያቄ ያነሱትን ብርቅዬ የኢትዮጵያ ልጆች በጅምላ እያፈሰ ከማሰሩም በላይ የብዙዎቹን ህይወት ቀጥፋል።በዚህም አንድ ትውልድ ያጠፋ መንግስት በመባል ይታወቃል።

ደርግ እንደ ከርቸሌ ማዕከላዊ እና ደርግ ጽ/ቤት በመሳሰሉት እስር ቤቶች ባሰራቸው የፖለቲካ እስረኞች ላይ ለማመን የሚቸግር ዘግናኝ ድርጊት ሲፈጽምባቸው ቆይቷል።ስፍር ቁጥር የሌላቸውን ዜጐች በፖለቲካ አቋማቸው ብቻ በጊዜው በነበሩት ባለስልጣናት ይፈፅምባቸው ከነበረው ሰብዓዊ መብት ጥሰት ብዛት የተነሳ እዛው እስርቤት እያሉ ህይወታቸው ያልፋል።

ከ22 ዓመታት በፊት ወታደራዊውን ደርግ በመጣል ስልጣን የተቆናጠጠው ወያኔ/ኢህአዴግ/ የዜጐቹን የመብት ጥያቄ ከመመለስ ይልቅ ከቀደሙት የአገሪቷ መሪዎች በባሰ መልኩ እጅግ ከፍተኛ የፖለቲካ እስረኛ በአገሪቱ እንዲኖር አድርጓዋል።

በአቶ አሊ ሁሴን የሚመራው የኢትዮጵያ የፖለቲካ እስረኞች አንድነት ኮሚቴ /Solidarity Committee For Ethiopian Political Prisoners/  እንደዘገበው በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ በተለያዩ እስር ቤቶች ከ 37,000 በላይ የፖለቲካ እስረኞች ይገኛሉ።

ወያኔ/ኢህአዴግ/ እንደ ቅሊንጦ የመሳሰሉ በርካታ አዳዲስ እስር ቤቶች ለአፈና አላማው ሲል አስገንብቷል። ቀድሞ በነበሩት እንደ ቃሊቲና ዝዋይ ማረሚያ ቤቶች ውስጥ ደግሞ በአንድ ክፍል በርካታ እስረኞች በተጨናነቀ ሁኔታ እንዲኖሩ በማድረግ ጨካኝነቱን በተግባር እያሳየ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የጦቢያ ዘመን አቆጣጠር ከፈረንጅ ዘመን አቆጣጠር አንጻር - መስፍን አረጋ

የኢሳቱ ጋዜጠኞ ሲሳይ አጌና የእስር ዘመኑን ባስታወሰበት  ”የቃሊቲው መንግስት” በሚለው መፅሐፉ ምርጫ 97ን ተከትሎ የተነሳውን ህዝባዊ ዓመፅ በሀይል ያፈነው ወያኔ/ኢህአዴግ/ በቃሊቲ በአንድ አዳራሽ 250 እስረኞች እደሚታሰሩ አጋልጧል። ከነዚህም መካከል 6 የሚሆኑት የአህምሮ ህሙማን ነበሩ።ሁሉም እስረኞች ለበሽታና ለሞት ተጋላጭ እዲሆኑ ለማድረግ ሲባል ከ 50 ያላነሱት የሳነባ ነቀርሳ ተጠቂዎች አብረው ታስረዋል።

በአገሪቷ ያሉትን ማረሚያ ቤቶች የሚያሰተዳድሩት የፌደራል ፖሊስ አባላት ለገዥው ፓርቲ የወገኑ ከመሆናቸው በተጨማሪ በእስር ቤቶች ውስጥ በተገነቡ ድብቅ ማሰቃያ ቤቶች የፖለቲካ እስረኞችን በከፋ ሁኔታ ያሰቃያሉ።

የኢትዮጵያ  ህገመንግስት አንቀጽ 19 ቁጥር 3 የተያዙ ሰዎችን በተመለከተ “የተያዙ ሰዎች በአርባ ስምንት ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት መቅረብ አለባቸው”/Everyone shall have the right to be brought before a court of law within 48 hours after his arrest./  ይላል። ገዥው ፓርቲ ለዚህ ድንጋጌ ምንም ክብር የለውም።

በመሆኑም ምንም አይነት ክስ ሳይመሰረትባቸው ሁለት ዓመት እና ከዛ በላይ በእስር የቆዩ  በርካታ የፖለቲካ እስረኞች በአገሪቷ ባሉ እስር ቤቶች በብዛት ይገኛሉ።

ወያኔ/ኢህአዴግ/ የአገሪቷን ህገመንግስት ከማስከበር ይልቅ የተለያዩ ሀሰተኛ ክሶችን ለመመስረት የጠቀምበታል። ይህ ደግሞ ፍትሃዊ የሆነ የፖለቲካ እስረኞች አያያዝ እና ፍትሐዊ የፍርድ ሂደት በአገሪቷ እንዳይኖር ትልቅ እንቅፋት ሆኗል።

ዜጐች ህገመንግስቱ ያጎናጽፋቸውን የመናገር፣የመጻፉ፣የመሰብሰብ፣የመደራጀት፣ነፃ ሚዲያ፤ነፃ ምርጫ ቦድ፣ነፃ እና ገለልተኛ ፖሊስ፣ ነፃ እና ገለልተኛ መከላከያ ሰራዊት፣ፍትሃዊ ፍርድ ሂደት፣ የፈለጉትን ፓርቲ መደገፍ ፣መምረጥ፣መመረጥ፣የመማር፣የመስራት፣በአገራቸው ሀብት ማፍራት፣ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ፣ የሀይማኖት ነፃነት መከበር ይህንን እና መሰል ጥያቄዎችን አንግበው ከመቼውም በላይ ትግላቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አዟሪና አከፋፋዮች ለምን አንድ ለአምስት አይደራጁም? (ጽዮን ግርማ)

ይህ ትግል የወለዳቸው እንደ አንዱዓለም አራጌ፣በቀለ ገርባ፣ርዕዮት አለሙ፣የሱፍ ጌታቸው፣እስክንድር ነጋ፣ናትናኤል መኮንን፣ኦልባና ሌሊሳ፣አቡበከር አህመድ፣ውብሸት ታየና ሌሎች በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ዜጐች ዛሬም ድረስ በእስር ላይ ይገኛሉ።

በአሁኑ ወቅት ወያኔ/ኢህአዴግ/ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚያደርጉትን ብቻ ሳይሆን እያንዳንዱን ዜጋ በፍራቻ የሚያይና የሚያሳድድ ሆኗል። በዚህ ምክንያት ተማሪው፣ አሰተማሪው፣ነጋዴው፣ሰራተኛው ፣ገበሬው፣የሀይማኖት መሪውና ስራ አጡ እየተዋከበ ነው።አንድ ላምስት በሚል የአፈና መዋቅር /እግረ ሙቅ/ ታፍኖ ተይዞል።

አገሪቷም ከአገርነት ወደ ትልቅ እስር ቤት ተቀይራለች። የወያኔ የፖለቲካ ደባ ድንበር ተሻግሮ በሽርክና በሚሰራባቸው አገሮች እየታየ ነው።ከዚህ ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያን ዜጐች በፖለቲካ አቋማቸው ምክንያት ከሀገር ተሰደው በሚኖሩባቸው በኬንያ፣በሱዳን፣በግብጽ፣ደቡብ አፍሪካ፣በቱርክ፣እንዲሁም በሌሎች አገሮች እስር ቤቶች ውስጥ ይገኛሉ።

የወያኔ ግፍ ማቆሚያ የለውም።ማቆሚያ የሚኖረው ይህ አንባገነን መንግስት ተወግዶ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከታሰረበት እግረ ሙቅ/እግር ብረት/ ሲላቀቅ ብቻ ነው።ስለዚህ ሁላችንም የጋራ ክንዳችንን በማንሳት የተከበረች ሉአላዊት ኢትዮጵያ ዳግም እውን እንድትሆን የበኩላችንን አስተዋፆ እናድርግ።

ድል ለህሊና እስረኞች!!!

 

 

 

 

 

Share