ይድረስ ለግርማ ካሳና ለሌሎች እስክንድር ነጋ ጦር የለውም ባይ የዋሆች ወይም መሠሪወች

“እስክንድር ነጋ እመራዋለሁ የሚለው ያማራ ሕዝባዊ ሠራዊት የሚባል አለ ወይ?  ይህ ድርጅት በወረቀት እንጅ በተግባር ያለ አይመስለኝም።” (ግርማ ካሳ)  

#image_title

የጦቢያ ሕዝብ ጣልያንን አድዋ ላይ ድባቅ መ(ት)ቶ የነጭ ላዕልተኝነትን (white supremacism) መሠረተቢስ እምነት ፉርሽ በማድረግ ላፍሪቃ በጠቅላላው ደግሞ ለመላው ዓለም ጥቁሮች የማንነት ክብርና ኩራት ያጎናፀፈው፣ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ደግሞ የጥቁር አንበሳነት (የጥቁር ሕዝብ ሉዓላዊነትና ነጻነት) ተምሳሌት የሆነው፣ ነጭን ከመጤፍ የማይቆጥር፣ በማንነቱ የሚኮራ፣ ጦቢያዊነቱን የሚያስቀድም አማራዊ መሪ ምታ ነጋሪት፣ ክተት ሠራዊት ብሎ፣ ሁሉንም ጦቢያውያን ከሁሉም የጦቢያ ግዛቶች አሰባስቦ በጦቢያዊነት መንፈስ ባንድነት ስላዘመታቸው ብቻና ብቻ ነው።

ጎጠኝነት የተጠናወተው፣ ትግሬነቱ ወይም ኦሮሞነቱ ከጦቢያዊነቱ የሚበልጥበት የትግሬ ወይም የኦሮሞ ጎጠኛ መሪ፣ መሠረቱ ትግሬ ወይም ኦሮሞ ብቻ (ለዚያውም ፅንፈኛው ብቻ) ስለሚሆንና ሁሉንም ጦቢያውያን ባንድነት ማሰባሰብ ስለማይችል እንደ አጼ ምኒሊክ ምዕራባውያን በጦር ግንባር መፋለምና ድል ማድረግ ቀርቶ ያለ ምዕራባውያን ከፍተኛ ድጋፍ አንድም ቀን እንኳን በስልጣን መቆየት አይችልም።  መለስ ዜናዊ ያረጋገጠውና ጭራቅ አሕመድም እያረጋገጠ ያለው ይሄንኑ ሐቅ ነው።  ወያኔው መለስ ዜናዊ ያን ሁሉ መዓት ባማራ ሕዝብ ላይ ያወረደው፣ ኦነጉ ጭራቅ አሕመድ ደግሞ ይሄን ሁሉ መዓት ባማራ ሕዝብ ላይ እያወረደ ያለው በምዕራባውያን በተለይም ደግሞ ያማራ ሕዝብ መሠረታዊና ዘላለማዊ ጠላቶች በሆኑት ባሜሪቃና በንግሊዝ መንግስታት አይዞህ ባይነትና ሙሉ ድጋፍ ነው።

ስለዚህም ባንግሎሳክሶኖች (Anglo-Saxons) የሚመራውና ዋና ምንጩ መሠሪዋ እንግሊዝ የሆነችው ነጭ ላዕልተኛው (white supremacist) ያሜሪቃ አፄጌ (American Empire) ያማራን ሕዝብና ያማራ ሕዝብ ከራሱ አብልጦ የሚወዳትን ጦቢያን በተመለከት ያላቸው መቸም የማይለወጥ ቋሚ አጀንዳ እኩይ አጀንዳ መሆኑ ምንም አያስገርምም።  አጀንዳውም ጦቢያን በጎጥ በመከፋፈል የነጭ መጫወቻ ለማድረግ የተነሳሱት ነጭ አምላኪ የትግሬና የኦሮሞ ጎጠኞች ጦቢያዊነቱን በሚያስቀድመው ባማራ ሕዝብ ላይ ሙሉ የበላይነት እንዲይዙና ለዘላለም እንዲነግሱ ነው።  ያማራ ሕዝብ የራሱንና የጦቢያን ሕልውና ለማስጠበቅ ትግል ሲጀምር ደግሞ ትግሉን ቢችሉ በመቀልበስ ባይችሉ በመጥለፍ ባጭር ማስቀረት ነው።  ባፍሪቃ ቀንድ ያሜሪቃ አፄጌ (American Empire) ልዩ መልዕክተኛ የሚካኢል መዶሻ (Mike Hammer) ዋና ተልእኮና የፕሪቶሪያ ስምምነት ዋና አላማም ይሄውና ይሄው ብቻ ነው።  እስክንድር ጦር የለውም በሚለው የስም ማጥፋት ዘመቻ ላይ ከሚሳተፉት ውስጥ የተወሰኑት ደግሞ ከሚካኢል መዶሻ ጋር እየዶለቱ የሚመሳጠሩ ናቸው።  ስለዚህም ቁልፉ ጥያቄ ወያኔወችና ኦነጎች ነጭ አምላካቸውን አሜሪቃን ይዘው፣ ያማራ ሆዳደሮችንና ስልጣን ጥመኞችን ተመርኩዘው በፋኖ እስክንድር ነጋ ላይ የስም ማጥፋት ዘመቻ መክፈት ለምን አስፈለጋቸው የሚለው ነው።

 

“The United States participated as an observer in the African Union lead talks in Pretoria … We are very proud to have supported that effort … and now …deal with Amhara special forces and FANNO groups that are active in the area.”  (Michael A. Hammer, United States Special Envoy for the Horn of Africa as of 2022).

 

በሚካኢል መዶሻ ጥቅስ ላይ ቁልፉ ሐረግ “ባካባቢው የሚንቀሳቀሱ” (active in the area) የሚለው ነው።  የሐረጉ ዓላማ ደግሞ  ያማራ ፋኖወችን የሽብርተኝነት ቀለም ቀብቶ በፀርሽበርተኝነት ዘመቻ ለማጥፋት ነው።  ጭራቅ አሕመድ ደግሞ ሲጨንቀው ድረስልኝ ብሎ የተማፀነውን ፋኖን በሽብርተኝነት ፈርጆ ፋኖን የማጥፋት ዘርፈብዙ ዘመቻ የከፈተው፣ ሚካኢል መዶሻ ከላይ በተጠቀሰው ጥቅስ አረንጓዴ መብራት (green light) ካበራለት በኋላ ነበር።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የበሰለ ፣ የተረጋጋ እና በእውቀት የታገዘ ውጫዊ እና ውስጣዊ ትግል ለዘላቂ እና አፋጣኝ ድል

ከግማሽ ምዕተ ዓመት በሚበልጠው የእድሜ ዘመኑ፣ ጨለማን ተገን አድርጎ ተካላካይ የሌላቸውን ቤታደሮች (civilians) በተለይም ደግሞ ሕፃናትና አረጋውያንን ከማረድ በስተቀር ድል ማድረግ ቀርቶ መሳርያ ከታጠቀ ባላንጣ ጋር ፊት ለፊት ገጥሞ የማያውቀው የጭራቅ አሕመድ ኦነጋዊ ሠራዊት ደግሞ ፋኖን ተዋግቶ ማጥፋት ቀርቶ ከፋኖ ፊት መቆም አይችልም።  ስለዚህም ጭራቅ አሕመድ ፋኖን ማጥፋት የሚችለው በራሱ በፋኖ ብቻ ነው፣ እሾህን በሾህ እንዲሉ።  ፋኖን በፋኖ ማጥፋት የሚቻለው ደግሞ ፋኖን በመከፋፈል ነው።  ፋኖን መከፋፈል የሚቻለው ደግሞ ፋኖወችን አንድ አድርጎ የሚያሰባስባቸውን መሪ ከተቻለ በመግደል ካልተቻለ ደግሞ ስሙን በማጥፋት ተቀባይነት እንዳያገኝ በማድረግ ነው።  በፋኖ እስክንድር ነጋ ላይ እየተደረገ ያለውም ሌላ ምንም ሳይሆን ይሄውና ይሄው ብቻ ነው።

ባሁኑ ሰዓት ከትግሬና ከኦሮሞ ጎጠኞች በስተቀር ጦቢያውያንን ሙሉ በሙሉ ባንድነት በማሰባሰብ የሚችል መሪ አንድ ብቻ ሲሆን፣ እሱም አብዛኛው የጦቢያ ሕዝብ በሙሉ ልብ የሚያምነው፣ የእውነተኛነትየርተኧኛነት (ቀጥተኛነት)፣ የፍትኸኛነትየጽናትያይበገሬነት ተምሳሌት የሆነው ፋኖ እስክንድር ነጋ ነው።  የእስክንድርን ታማኝነት፣ ሰብዓዊነትና ጨዋነት እጅጉን የሚያጎላው ደግሞ ከኦሮሙማው መሪ ከጭራቅ አሕመድ ቀጣፊነት፣ አጭበርባሪነት፣ ባለጌነት፣ ጋጠወጥነትና አውሬነትና አረመኔነት አንጻር ሲታይ ነው።  ስለዚህም በእስክንድር ነጋ የሚመራ ያማራ ሕዝብ የሕልውና ትግል አማራ ያልሆኑ ኢትዮጵያውያንን በቀላሉ በዙርያው በማሰበሰብ የትግሉን ሜዳ አማራ ክልልን ብቻ ሳይሆን መላዋን ጦቢያን የሚያጠቃልል ሰፊ ሜዳ አድርጎ፣ የጭራቅ አሕመድን ኦነጋዊ መንግስት መግቢያ መውጫ በማሳጣት ውድቀቱን በከፍተኛ ፍጥነት እንደሚያቃርበው ሳይታለም የተፈታ ነው።

ፋኖ ዘመነ ካሴ ጭራቅ አሕመድን ለማስወገድ ከፍተኛ ሚና ሊጫወት ይችላል።  መላውን የጦቢያን ሕዝብ ቀርቶ መላውን ያማራን ሕዝብ በዙርያው ለማሰባሰብ ግን አይችልም ባይባልም እንኳን በጣም ያዳግተዋል፣ የእስክንድርን ያህል አይቀልለትም።  ሌሎቹም ፋኖወች (ምሬ ወዳጆ፣ መሳፍንት ተስፉ ወዘተ. ) እንደዚሁ።  ስለዚህም የጭራቅ አሕመድን ጭራቃዊ መንግስት ከሁሉም ፋኖወች በላይ ይበልጥ የሚያሰጋው ፋኖ እስክንድር ነጋ ነው።  የጭራቅ አሕመድ ጭራቃዊ መንግስት ቀንደኛ ደጋፊወች የሆኑት እነ ኦቦ ዮናስ ብሩ ሌሎቹን ፋኖወች እያሞገሱ በፋኖ በእስክንድር ነጋ ላይ ከፍተኛ የስም ማጥፋት ዘመቻ የከፈቱትም፣ ሌሎቹን ፋኖወች ወደዋቸው ሳይሆን ዋና ስጋታቸው ፋኖ እስክንድር ነጋ መሆኑን በደንብ ስለሚያውቁ ነው።

የስም ማጥፋቱ ዘመቻ ዋና አካል ደግሞ እስክንድር ጦር የለውም የሚባለውን ወሬ ማናፈስ ነው።  የእስክንድርን ስም በዚህ ወሬ ማጥፋት የተፈለገው ደግሞ ስሙን በሌላ ወሬ ማጥፋት የማይቻል ስለሆነ ብቻ ነው፣ እስክንድርን ባላዋቂነት፣ በሆዳደርነት፣ በነጭ አሽከርነት፣ በጎጠኝነት፣ በጠባብነት፣ በዘረኝነት፣ በፊሪነት፣ በሐይማኖት አክራሪነት፣ ባግላይነት፣ በውሸታምነት፣ ባስመሳይነትና በመሳሰሉት መክሰስ አይቻልምና። የእስክንድርን ስም በዚህ ወሬ በማጥፋት ዘመቻ ላይ የተሰማሩት ደግሞ ወያኔወችና ኦነጎች ብቻ ሳይሆኑ፣ ባማራ ሕዝብ ደም የስልጣን ጥማቸውን ለማርካት ያሰፈሰፉ፣ ያማራ ሕዝብ መሠረታዊና ዘላለማዊ ጠላት ከሆነው ካሜሪቃ መንግስት አመራሮች ጋር በተለይም ደግሞ ከሚካኢል መዶሻ (Mike Hammer) ጋር በየጊዜው እየተገናኙ በየጊዜው የሚዶልቱ፣ ስማቸውን መጥቀስ የማያስፈልግ፣ በይፋ የሚታወቁ የፋኖ ደጋፊወች ነን ባዮች ናቸው።

እስክንድር ጦር የለውም የሚሉ ሁሉ፣ ጦር ማለት ምን ማለት እንደሆነ የማያውቁ የዋሆች፣ ወይም ደግሞ እያወቁ እንዳላወቁ የሚሆኑ መሠረወች ናቸው።  የጦቢያን ሕዝብ ባንድነት በማሰባሰብ አራት ኪሎን ተቆጣጥሮ ያማራን ሕዝብ ኢትዮጵያዊ ትግል ከግብ ማድረስ የሚችለው፣ መነሻችን አማራ መድረሻችን ኢትዮጵያ ብሎ የተነሳው ፋኖ እስክንድር ነጋ ብቻ ነው።  ስለዚህም ዘመነ ካሴ፣ ምሬ ወዳጆ፣ መሳፍንት ተስፉና የቀሩት ሁሉም የፋኖ መሪወች እውነትም ያማራ ሕዝብ ኢትዮጵያዊ ትግል ከግብ እንዲደርስ የሚፈልጉ ከሆነ፣ ያላቸው ምርጫ አንድና እንድ ሲሆን፣ እሱም የአስክንድር ነጋ ጦር አባል መሆን ነው።  አለበለዚያ በየቀበሌያቸው ተወስነው ይቀራሉ።  ወያኔወችና ኦነጎች የሚፈልጉትም ይሄንኑ ነው።  በወኪሎቻቸው በነ ኦቦ ዮናስ ብሩ አማካኝነት የእስክንድርን ስም እያኮሰሱ የነ ዘመነ ካሴን ስም የሚያነግሱትም በዚሁ ምክኒያት እንጅ ፋኖን ደግፈው እንዳይደለ ያልተረዳ አማራ ካለ፣ ያልተረዳው የመረዳት ችሎታ ስሌለው ብቻ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ታገል ሰይፉ፡ ኢሕአዴግ ካምፕ ውስጥ ያደገው አውሬ

እስክንድርን በዚህ እይታ ስንመለከተው ከማናቸውም የፋኖ መሪ በላይ ጦር አለው።  በተጨማሪ ደግሞ ፋኖ የጭራቅ አሕመድን መንግስት መነቅነቅ የጀመረውና ለመጀመርያ ጊዜ ከተማ የተቆጣጠርው ዘመነ ካሴ፣ ምሬ ውዳጆ ወይም መሳፍንት ተስፉ በሚሞሩት ጦር ሳይሆን፣ እስክንድር ነጋ የጦር አዛዥ ባደረገው በኮሎኔል ፋንታሁን ሙሓባ አማካኝነት ዋድላ ደላንታ ላይ መሆኑን መርሳት አያስፈልግም።  በተጨማሪ ደግሞ መነሻችን አማራ መድረሻችን ጦቢያ የሚለውን አገር ወዳድ ጦብያውያንን ሁሉ ባንድነት ላንድ ዓላማ የሚያሰባስበውን መሪ መፈክር የፈጠረው ዘመነ ካሴ፣ ምሬ ወዳጆ፣ መሳፍንት ተስፉ ወይም ሌላ የፋኖ አመራር ሳይሆን ፋኖ እስክንድር ነጋ ነው።  ስለዚህም መነሻው አማራ መድረሻው ጦብያ ለሆነው ላማራ ሕዝብ ትግል ዋና ምልከቱ (symbol) ከሞላ ጎደል ሁሉም አገርወዳድ ኢትዮጵያዊ በሙሉ ልቡ የሚያምነው እስክንድር ነጋ ነው።  ስለዚህም እስክንድር ነጋ በስሙ ብቻ የሚፈታው የወያኔና የኦነግ ጦር፣ እነ ዘመነ ካሴ በጦርነት ከሚፈቱት የወያኔና የኦነግ ጦር እጅጉን የበለጠ ነው፣ ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው ነውና።

ማናቸውም ትግል የሚጠነክረው በሂደት ነው።  ጨቅላ ሕፃን በተወለደ ማግስት ቁሞ እንደማይሄድ ትግልም እንደዚሁ ነው።  ሻቢያ ጠንክሮ የወጣው ከጀብሃ ጋር ለረዥም ጊዜ ተዋግቶ አያሌ ኤርትሬወችን ሰውቶ ነው።  የስብሐት ነጋና የመለስ ዜናዊ ፀረጦቢያ ቡድን ሕውሐትን ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠረው ጦቢያወዳድ ትግሬወችን በየጊዜው ወደ ተከዜ በርሓ እየወሰደ በየጊዜው ረሽኖ ከጨረሰ በኋላ ነው።  ጨለማንና ውርማን ተገን አድርጎ ሰላማዊ ዜጎችን ከመጨፍጨፍ በስተቀረ መሣርያ ከታጠቀ ባላንጋራ ጋር አንድም ቀን ተፋልሞ የማያውቀው፣ እድሜው ካምሳ ዓመት የሚበልጠው ኦነግ ደግሞ አሁንም ድረስ ለሃያ አንጃወች እንደተከፋፈለ፣ አሁንም ድረስ እርስበርስ እንደተገዳደለ ነው።

በተቃራኒው ግን ያማራ ፋኖ የተለያዩ አደረጃጀቶች እንደ ወያኔና ኦነግ ርስበርሳቸው ደም ሳይፋሰሱ በሰለጠነ መንገድ በሚያስደንቅ ፍጥነት ወደ አንድ አደረጃጀት እያመሩ ነው።  አቦ ዮናስ ብሩና መሰሎቹ ቀንደኛ ኦሮሙሜወች ያማራ ፋኖን አሁኑኑ ለምን አላዋሃዱም እያሉ እስክንድር ነጋንና ሻለቃ ዳዊትን የሚወቅሱትና የሚከሱት ደግሞ የፋኖወች አለመዋሃድ አሳስቧቸው ሳይሆን፣ የፋኖወች የውሕደት ሂደት እየተከተለው ያለውን የሰለጠነ ፈር ለቆ ወጥቶ ፋኖወች እርስበርሳቸው እንዲጨፋጭፉ ስለሚፈልጉ ብቻ ነው።

ስለዚህም እስክንድር ነጋ ድክመት ካለበት ድክመቱን ለማስወገድ በውስጥ ንግግር ከመጣር ይልቅ፣ ያማራ ሕዝብ ቀንደኛ ጠላቶች ለሆኑት ለወያኔወችን ለኦነጎች ያማራን ሕዝብ ገመና የሚያወጡ ሁሉ፣ በቀጥታም ሆነ በተዛዋሪ የወያኔና የኦነግ ደጋፊወች ስለዚህም ያማራ ሕዝብ ጠላቶች መሆናቸውን ሊያውቁት፣ ካላወቁት ደግሞ እንዲያውቁት ሊነገራቸው ይገባል።   አቶ ግርማ ካሳም እስክንድር ጦር የለውም ብሎ ሲፅፍ፣ አስቦበትም ሆነ ሳያስበበት በቀጥታም ባይሆን በተዛዋሪ የወያኔና የኦነግ ደጋፊ ስለሆነም ያማራ ሕዝብ ጠላት እየሆነ መሆኑን በግልጽ ሊነገረው ይገባል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ግንጥል ጌጥ በማንም አያምርም - ይነጋል በላቸው

አቶ ግርማ ካሳ እስክንድር ጦር የለውም በማለት እስክንድርን ለወያኔወችና ለኦነጎች የስም ማጥፋት ዘመቻ አሳለፎ የሰጠው ጦር ማለት ምን ማለት እንደሆነ የማያውቅ የዋህ ወይም ደግሞ አውቆ እንዳላወቀ የሚሆን መሠሪ ወይም ደግሞ ባማራ ሕዝብ ደም የስልጣን ጥሙን ለማርካት ያማራ ሕዝብ መሠረታዊና ዘላለማዊ ጠላት ከሆነው ካሜሪቃ መንግስት ጋር በተለይም ደግሞ ከሚካኢል መዶሻ (Mike Hammer) ጋር የሚመሳጥር ተመሳጣሪ ስለሆነ ይሆናል፣ የተኛውን እንደሆነ በውል ባላውቅም።  የሆንውን ቢሆንም ግን የሰው ክብር የመንካት መብት ስለሌለው፣ መረን ለቆ፣ ቀይ መስመር አልፎ ለፍልሚያ (duel) በሚያነሳሳ ደረጃ ያገር ወዳዱን ያቶ ሽመልስ ለገሰን ክብር ሲነካ ሃይ ሊባል (አደብ ግዛ ሊባል) እና ለምን ተብሎ ሊጠየቅ ይገባል።

ስለዚህም አቶ ግርማ ካሳ ሆይ፣ አቶ ሽመልስ ለገሰን “የፖለቲካ ብስለት የሌለው፣ ምናልባት የጤና ችግር ያለበት፣ ሥራፈት ሰው ነው” በማለት ክብሩን ልትነካ የሞከርከው ጦር የለውም በማለት ልታንኳስሰው ለሞከርከው ለእስክንድር ነጋ ታማኝ በመሆኑ ነውን፣ ወይስ ከእስክንድር ነጋ ጋር ቀበሌ ለቀበሌ እየተንከራተተ በኦነግ ቤታቸው ለፈረሰባቸው አማሮች በጽናት በመታገሉ ነውን፣ ወይስ ለሰንደቃላማው ያለው ፍቅር ጥልቅ በመሆኑ ነውን?  ያማራን ሕፃናት የሚያርዱትንና ያሚያሳርዱትን የኦነጎና የወያኔ አውሬወች ኦቦ ምንትሴ፣ አቦይ ቅብጥርሴ በማለት በክብር እየጠራህ፣ ያማራን ሕዝብ ስቃይ የራሱ ስቃይ አድርጎ በመሰለውና በሚችለው መንገድ፣ ባለው አቅም ሁሉ የሚታገለውን አቶ ሽመልስ ለገሰን በዚህ ደረጃ ለመዘለፍ ምን አስፈለገህ?  የፖለቲካ በሳል ነኝ ለማለት ነውን?  የግል ቂምህን ለመወጣት ነውን?  እስክንድርን በቀጥታ መዘለፍ እንዳማያዋጣህና ባብዛኞቹ አገርወዳድ ጦቢያዊያን  እንቅሮ እንደሚያስተፋህ ስለምታውቅ በተዛዋሪ ወይም በተጓዳኝ (by association) እስክንድርን ለመዘለፍ ነውን?  እስክንድርን በተጓዳኝ ለመዘለፍ ከሆነስ፣ ለዝለፋ የተነሳሳኸው ከሚካኢል መዶሻ (Mike Hammer) ጋር በተማከርከው መሠረት ነውን?

እነዚህን ሁሉ ካልሆንክ ያማራን ሕዝብ የማጀት ሚስጥር እልፍኝ እያወጣህ፣ ያማራን ሕዝብ የቤት ጉዳይ አደባባይ እያሰጣህ፣ ያማራ ሕዝብ ጠላቶች መሳርያ አትሁን።  አለበለዚያ ደግሞ የወያኔና የኦነግ የጎጠኝነት በሽታ ተጋብቶብህ ያንዱን ክልል ፋኖ ከሌላው ክልል ፋኖ ለማስበለጥ እየሞከርክ ከሆነ፣ እንደ አቶ ሽመልስ ለገሰ ጀግና ሁንና ማንነትህን በግልጽ አሳይተህ እመሸበት እደር።  የጎጃምና የጎንደር ፋኖ ከቤታማራና ከሸዋ ፋኖ ይበልጥ የተጠናከሩ መስሎ ከታየህ ደግሞ፣ ከጎንደርና ከጎጃም ፋኖ መጠናከር ይልቅ ለጭራቅ አሕመድ መንግስት ይበልጥ የሚያሰጋው የቤታማራና የሸዋ ፋኖ መጠናከር በመሆኑ ሳቢያ፣ ጭራቅ አሕመድ ይበልጥ ትኩረቱን ያደረገው የቤታማራንና የሸዋን ፋኖ ጥንካሬ በማጨናገፍ ላይ በመሆኑ ብቻ መሆኑን ተረዳ።  የጎጃም ፋኖ የጠነከረውን ያህል የቤታማራና የሸዋ ፋኖ ጠንክረው ቢሆን ኖሮ፣ ጭራቅ አሕመድና ኦሮሙማ ከወራት በፊት ሙተው ተቀብረው እንደነበር ተገንዘብ።                 

እውነትም የቆምከው ያማራን ሕዝብ ሕልውና ለማስጠበቅና ጦቢያ ከመፈራረስ ለማዳን ከሆነ፣ እስክንድር ጦር የለውም እያልክ ያማራም የጦቢያም ቀንደኛ ጠላቶች የሆኑትን የወያኔወችንና የኦነጎችን ወሬ ከምታናፍስ ይልቅ፣ የእስክንድር ያለው ጦር በብዛትና በጥራት ይበልጥ ያድግና ይመነደግ ዘንድ በልምድ የሚዋጉት እነ ዘመነ ካሴ፣ ምሬ ወዳጆ፣ መሳፍንት ተስፉና መሰሎቻቸው ወታደራዊ ትምህርት በተማረው በኮለኔል ፈንታሁን ሙሐባ ሥር ሁነው በእስክንድር ነጋ ዙርያ እንዲሰባሰቡ ለማሳመን የበኩልህን ድርሻ ተወጣ፣ ያማራ ሕልውና የሚጠበቀው፣ ጦቢያም ከመፈራረስ የምትድነው በዚህና በዚህ መንገድ ብቻ ነውና?

 

መስፍን አረጋ

mesfin.arega@gmail.com

 

8 Comments

  1. ግርማ ካሳ በታጋይ እስክንድር ጉዳይ ያንተ ምልከታም ሆነ አስተያየት በጣም የወረደ መሆኑንን በክፉ ትርክት አምራ ነፍጠኛ በሚል በዘር የተደራጁ ቡድኖች ላላፉት አርባ አመታት የነበርኩበት ኢህአፓም ቀና ታጋዮቹ እነ ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ያለዘር ልዩነት ለኢትዮጲያ የተሰዉለት በጠማምውው ትርክት ተባባሪ በመሆን አማራይዜሽን በሚል የጥቃቱ ተባባሪ መሆኑ ይታወቃል:: ስለዚህ ፋኖ የለም የምትል ሰው ዛሬ ተመልሰህ ስለፋኖ ትግል ከምትገንረን የህዝብ ተወካይ በሃቅ ከሆንክ ለሚተረደው ህዝብ ሞግት:: ሸዋ ጎንደር ወሎ ጎጃም በሚል የምትከፋፍለውን የሚሰማ የለም:: የወያኔና የብልግናው ተልእኮህን ማስፈጸም ከሆነ በተበላ እቁብ ማለቅለቕን አቁም ግፈኛች ሲያርዱት አማራ ብለው እንጅ ጎንደሬ ወለዮ ጎጃሜ ሸዋ ብለው አይደለም አትከፋፍልያንተና የልደቱ አየነቶቹ የፓርላማ ማዳመቂያዎች ለህወቱ ሳይሳሳ በረሃ ወርዶ የሚታገለውን ታጋይ እስክንድር ለመተቸት ብቃት ሞራል የላችሁም::
    ታጋይ እስክንድርም በውጭ ያለነው ድጋፍን ባግባቡ ከሃገር ቤት የፋኖ ታጋዮች ጋር በማቀናጀት የውጭው ትግል ከፕሮፓጋንዳና ከፋይናንስ ውጭ በፋኖ በረሃ በሚዋደቀው የትግል ሂደት ጣልቃ ሳይገባ በአፍሪካ ምክር ቤትANC በተባበረ ዘይቤ ያለውን ዘረኛ ጸረ አማራ ጸረ ኢትዮጲያ ስርአት ከሁሉም የኢትዮጲያ ህዝቦች ጋር በማቀናጀት ይፋለሙ ዘንድ ምክሬን ሰጣለሁ::
    ጨቁዋኙን ፈርኦንን ባህር ያሰመጠ ትእቢተኛውን ናቡከደነጾርን ሳር ያሰበላ የግፉአን አምላክ ከሃዲውን አብይና ግፈኛውን ኦሮሙማ ተብዬ በኦሮሞ ወገናችን ስም የሚጨፈጭፈውን ግፈኛ ይፍረድበት::
    ፓስተርዲጎኔ ሞረቴው

  2. Prof. Mesfin, I don’t have words how to thank you. Please keep writing the truth. I was very disappointed by Girma Kassa whom I used to admire.

  3. አቶ ግርማ እስክንድር ጦር የለውም አለውም የሚልበት ምንም መረጃ የለውም። ከተማ ተቀምጦ ክትፎ እየበሉ በረሃ ያለውን ፍልሚያ መረዳት ይከብዳል። ግን አቶ ግርማ የሚሰማውን ለመጻፍ መብቱ ነው። ለዚህም ዘሃበሻ መድረኩን መስጠቱ ማለፊያ ነው። ችግራችን እኛን ያለመሰለ ሁሉ አይንህ ላፈር መባሉ ነው። ፈርቶ የተመለሰ ሁሉ ጠላት ነው የሚል አስተሳሰብ ሰውን በሽተኛ ያደርጋል። ፈሪ ለእናቱ ነውና! ያለንን እይታና ሃሳብ ለሌላው ለማድረስ ግን አንድ ላይ ጭቃ ሌላው ላይ ጥላሸት መቀባት አይጠበቅብንም። ይበልጡ የሃበሻ ፓለቲካና እሰጣ ገባ መረጃ አልባ በመሆኑ ነገርን አመሳክሮና አበጥሮ ለማቅረብ ይቸግራል። እስክንድር በዝምታ አፎን ዘግቶ በሰላም እንደ ቀረው ተሰዶ ወይም በሃገሩ ዝም ጭጭ ብሎ መኖር ይችል ነበር። የመረጠው ባመነበት መንገድ ከቤተሰብ ተለይቶ በረሃ ለበረሃ በመንከራተት ለወገኑ ጥብቅና መቆም ነው። ይህ ውሳኔው ብቻ ክብረት ያስገኝለታል። ሲጀመር የእስክንድር ጦሩ ብዕሩ ነበር። አምባገነኖች ግን የብዕርን ሥራ እንደ ጦር ስለሚፈሩ ዛሬ ወዳለበት የትጥቅ ትግል እንዲገባ ምክንያት ሆነዋል።
    ዛሬ በአዲስ አበባ አ ና ኡ የሚባልለት ግንባታ ሰው በሰውነቱ ተከብሮ በሰላም ወቶ በማይገባበት ምድር ላይ ምንም አይነት ድንቅ ሥራ ቢሰራ ዋጋ ይብሉን። ለዚህ ነው አዝማሪው – “ሃገሬን አጥቼ ከምሰለጥን እኔስ በነጻነት ባላገር ልሁን” በማለት የዘፈነው። በቅርቡ የቀዶ ጥገናው ባለሙያ ዶ/ር በሃይሉ ሃይሉ ለሩጫ ወጥቶ ሞቶ የተገኘው የስልት ግድያ ነው ወይስ የዝርፊያ ግድያ? ለምንስ የአዲስ አበባ ፓሊስ የማወቀው ነገር የለም አለ? ምድሪቱ የወሮበሎችና የዘረኞች ሆናለች። ያን ያህል የተማረና የስንት ሰዎችን ህይወት የሚጠግን ሰው በሚገደልባት ሃገር ስለ ሰላምና ብልጽግና ማውራት መጃጃል ነው። እንግዲህ በዚህና በሌሎች የሃገር ውስጥ ሴራዎችና ችግሮች፤ በሰዎች በየቀኑ መታፈንና የት እንደደረሱ በማይታወቅበት ምድር ላይ ስንት የሚጻፍና የሚነገር ነገር እያለ አቶ ግርማ ስለ እስክንድር ሰራዊት መኖርና አለመኖር መክተቡ ያስገርማል። ችግሩ ሰራዊት አለው የለውም የሚለው ሳይሆን ፍልሚያውን ማሳጠር ወይም በአሸናፊነት ተደራድሮ ማቆም የሚቻልበት መንገድ አለ ወይ ነው? እንደ ገና ዳቦ ከላይም ከታችም እየዘነበበት በሁለቱም በኩል የሚሞተው የአማራ ህዝብ ገና ከወያኔ የ 27 ዓመት መከራና የ 3 ጊዜ ወረራ አላገገመም። አሁንም ሃበሳው የበዛ ሆኗል። ባጭሩ የህዝባችን ሰቆቃ ማቆሚያው መቼ ነው? የእኔ ፍራቻ ፍልሚያ ይጓተትና ህዝባችን ወደ ድንጋይ ዘመን እንዳይመለስ እፈራለሁ። የተሰራው ከፈረሰ፤ የተማረው ከታሰረና ከተገደለ ማን ነው ለሃገሪቱ የወደፊት ተስፋ? ሞት በቃኝ አይል። ከዚህም ከዚያም ይሰበስባል? ግን መቼ ነው ህዝባችን እፎይ የሚለው? ያ ቀን ይመጣ ይሆን? አላውቅም!

  4. መስፍን አርጋ የተባልክ ዝባዝንኬ እውንተኛ ስምህ ሃጎስ ነው:: የበግ ለምድ የለበስ ተኩላ ማለት አንተ ነህ

  5. “እስክንድርን ባላዋቂነት፣ በሆዳደርነት፣ በነጭ አሽከርነት፣ በጎጠኝነት፣ በጠባብነት፣ በዘረኝነት፣ በፊሪነት፣ በሐይማኖት አክራሪነት፣ ባግላይነት፣ በውሸታምነት፣ ባስመሳይነትና በመሳሰሉት መክሰስ አይቻልምና።” ትክክል!

    በእስክንድር ነጋ ላይ ጣቱን የሚቀስር ሁሉ ህሊና አለው ለማለት ያስቸግራል፡፡ እስቲ በዚህ ዘመን እንደሱ ጥቅምንና ቤተሰቡን ብቻ ሳይሆን የተሞላቀቀና የተንደላቀቀ ኑሮን እርግፍ አርጎ ትቶ ለሕዝብ፣ ለአገርና ለፍትህ እድሜ ልኩን የታገለ ማን ነው? ፓትርያሪክና ጳጳሱ ሳይቀር የውሸት መሐላ እየማሉ የሌላ አገር ዜግነትን በውሸት እየሸመቱ አንዴ ተውጪ ሌላ ግዜ ከአገር ቤት ጥቅም ሲያሳድዱ ተንዳላቆ የኖረበትን አሜሪካ ትቶ ለሕዝብና ለአገር የመነነውን ሰማእት ባልተገራ ምላስ መግረፍ ምን ይባላል? እርሱ በርሃ ለበርሃ እየተንከራተተ የፈረንጅን ቅዝቃዛ ቢራ እየጨለጡ ስም ማጥፋት ምን ይባላል? እግዚኦ!

  6. ወንድም መስፍን፦
    ግርማ ካሣ፣ እንደ ዮናስ ብሩ፣ አፍራሽ ድርሰት እንዳቀረበልን ግልጽ ነው። ባሁኑ ወቅት፣ እስክንድር አሜሪካ ወይም አውሮጳ ውስጥ አይደለም። ያለው በአራቱ ክፍለ ሀገራት ውስጥ ያመነበትን ሥራ እየሠራ ነው። የመንደር፣ የሃይማኖት ወይም የሥልጣን ጥማት እንደሌለው ከቅንጅት ዘመን ጀምሮ ያየነው ነው። አብረውት በየክፍለ ሀገሩ የረጅም ዘመን የትግል ልምድ ያላቸው የኢትዮጵያ ምርጥ ልጆችም አሉ። እነሱን ማወዳደሩና ማበላለጡ፣ አማራን ብቸኛው የአገር አለኝታ የነበረና ዛሬም የሆነ አድርጎ ማቅረቡም ለአንድነቱ ጥረት ጎጂ ነው ። በቅርቡ ፋኖ ከጉሙዝ ጋር የትብብር ስምምነት አደረገ፣ ከኦነግም ጋር ለመነጋገር በቀጠሮ ላይ ናቸው ሲባል የሰማሁ መሰለኝ። ኢትዮጵያ የሁላችን አገር ናት፣ ስለሆነም ወደ ታላቂቱና ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ ፈጥነን ለመጓዝ ሁላችንም መሰባሰብ አለብን። መሰባሰቡ የአፄ ቴዎድሮስ፣ የአባ ዳኘው፣ የአባ ጠቅል ወሳኝ የሕልውና ትግል ውርስ መሣሪያ ነውና!

  7. ወንድም መስፍን አረጋ፦
    ግርማ ካሣ፣ እንደ ዮናስ ብሩ፣ አፍራሽ ድርሰት እንዳቀረበልን ግልጽ ነው። ባሁኑ ወቅት፣ እስክንድር አሜሪካ ወይም አውሮጳ ውስጥ አይደለም። ያለው በአራቱ ክፍለ ሀገራት ውስጥ ያመነበትን ሥራ እየሠራ ነው። የመንደር፣ የሃይማኖት ወይም የሥልጣን ጥማት እንደሌለው ከቅንጅት ዘመን ጀምሮ ያየነው ነው። አብረውት በየክፍለ ሀገሩ የረጅም ዘመን የትግል ልምድ ያላቸው የኢትዮጵያ ምርጥ ልጆችም አሉ። እነሱን ማወዳደሩና ማበላለጡ፣ አማራን ብቸኛው የአገር አለኝታ የነበረና ዛሬም የሆነ አድርጎ ማቅረቡም ለአንድነቱ ጥረት ጎጂ ነው ። በቅርቡ ፋኖ ከጉሙዝ ጋር የትብብር ስምምነት አደረገ፣ ከኦነግም ጋር ለመነጋገር በቀጠሮ ላይ ናቸው ሲባል የሰማሁ መሰለኝ። ኢትዮጵያ የሁላችን አገር ናት፣ ስለሆነም ወደ ታላቂቱና ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ ፈጥነን ለመጓዝ ሁላችንም መሰባሰብ አለብን። መሰባሰቡ የአፄ ቴዎድሮስ፣ የአባ ዳኘው፣ የአባ ጠቅል ወሳኝ የሕልውና ትግል ውርስ መሣሪያ ነውና!

  8. ፕሮፌሰር መስፍን እናመሰግናለን የፖለቲካን ብልት እየተከታተልክ በድፍረት እንዲህ ያለ ትንታኔ መስጠትህ በበኩሌ በፋኖ ስም ለተሰለፉ ሁሉ ትልቅ ክብር አለኝ ነገር ግን እስክንድር ነጋ ሊትመስ ቴስት የሚሉትን ያለፈ የኢትዮጵያ ህዝብ ዘረ ከጎሳ ከሃይማኖት ሳይለይ የሚያከብረው ድንቅ ኢትዮጵያዊ ነው ከባህር ማዶ የሚረባረቡበት ለፋኖ ያዘኑ መስለው እስክንድርን የሚወቅጡት እስክንድር ወደ አውሮፓና አሜሪካ ሂዶ ለመኖር እድሜ ልኩን ያልተቀበለው ውሳኔ መሆኑን ሊገነዘቡ ይገባል፡፡ እስክንድር ቤቱን ትዳሩን ለሌላ ለምንም ሳይሆን ለኢትዮጵያ ህዝብ የሰጠ ሲሆን የኢትዮጵያ ህዝብም ለእሱ የተለየ ከበሬታ አለው፡፡ አሁን እስክንድርን ከየአካባቢው የሚፈትኑ እስክንድርን ሳይሆን ኢትዮጵያንና የፋኖን አንድነት የሚፈትን ክፉ ስራ ከመሆኑም በላይ ኢትዮጵያን የማፍረስ ደባም ነው፡፡ ስለዚህ ረጋና ቀዝቀዝ በሉ በዚህ ሴራ ተጠቃሚ የሚሆነው ኦሮሙማ ነው፡፡ እስክንድር ከምሬ ወዳጆ፤ዘመነ ካሴና ከሌሎች ቤት ንብረታቸውን ጥለው ዱር ከወጡት ጋር ይስራ ተውት በየሶሻል ሚዲያ ፖለቲካ እንተንትን ብለው ነብስ ከስጋቸው የሚለየው መሃይማን ሲናገሩ መስማት እየሰቀቀን መጥቷል እረፍት ውስዱ በሉልን፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share