ዲሞክራሲ በምጽዋት ??!! ( አሥራደው ከካናዳ )

ምስሎች : ከባንክሲ የመንገድ ላይ የጥበብ ሥራዎች የተዋስኳቸው::

ማስታወሻ :

ይህ ጽሑፍ: ለህሊናቸው ለሚኖሩና፤ የሃገራቸው ፍቅር: በልባቸው የተዳፈነ ዜጎችን፤ እንደሚያንገጫግጭ ይገባኛል:: በአንፃሩ: ሆዳቸውን በፍርፋሪ ከሞሉ፤ ህሊናቸውን ለማይርበው፤ የሚያስቅ ቢሆንም፤ የዘርና የጎሣ ፖለቲካ ቁማርተኞችን ግን፤ እንቅልፍ እንደሚነሳ አልጠራጠርም::  ለማንኛውም: የማሰብ ነፃነቴን በመጠቀም፤ማለት የሚገባኝን በማለቴ፤ ሕሊናዬን እንደ አባ ጨንጓሬ አይኮሰኩሰውም:: በጽሁፌ: እራሴንም ከተወቃሹ ትውልድ ማከሌን፤ አንባቢ እንዲረዳልኝ እሻለሁ::

ያም ሆነ ይህ: በሃገራችን በኢትዮጵያ ጉዳይ፤ ከደሙ ንጹህ ነኝ ብሎ፤ እጆቹን እንደ ጲላጦስ፤ የሚታጠብ ካለ እሱ ውሸታም ነው::

መንደርደሪያ

  • « Je pense, donc je suis »  René Descartes

« አስባለሁ፤ እናም  እኔ ነኝ »  በግርድፉ  ሲተረጎም ::  

« ማሰብ መቻሌ፤ ሰው የመሆኔ ማረጋገጫ ነው » የፍልስፍና ዕሳቤው ሲጤን   (ሬኔ  ዴካርት)

 

  • « L’homme est né libre, et partout il est dans les fers » Jean-Jacques Rousseau

የሰው ልጅ በነፃነት ተወልዶ፤ ነገር ግን በየቦታው በሰንሰለት ታስሮ ይገናኛል ( ዣን ዣክ  ሩሶ )

 

  • « Ose savoir ! » Emmanuel Kant

« ለማወቅ ድፈሩ ! »  አማኑኤል ካንት

 

መግቢያ:

ሰው ትናንትን ነበር፤ ሰው ዛሬን ነው፤ ሰው ነገንም ይሆናል፤ በተለይ ከምድራዊ አፈር፤ የተድበለበለን የሰው ሥጋ፤ የህይወት እስትንፋስ የምትዘራበት ተስፋ ናት:: ትናንትን ለታሪክ ትቶ፤ ዛሬን እየኖረ፤ ነገን በተስፋ ለማለምለምና፤ የወደፊቱን ለመኖር፤ ውስጣዊ ትኩሳቱን በማንቦግቦግ፤ ለጉዞው የሚሆን ብርሃን እየፈነጠቀ፤ ያለፈውን ብቻ ሳይሆን፤ ዛሪንና የወደፊቱን ለመኖር ያልማል::

ታዲያ: ይህ የዲሞክራሲ ተመጽዋች የሆነ ትውልድ፤ ቀደም ብሎ ህወሃት: አሁን ደግሞ (የኦህዴድ/ኦነግ) ጥምር: ብልጽግና ተብዬ፤ የዘርና የጎሣ ፖለቲከኞች፤ ፍትህ: ዕኩልነት፤ ነፃነትና ዕድገትን፤ እንካ ብለው በምጽዋት ይሰጡት ይመስል፤ ዓይኖቹን እያቁለጨለጨና፤ እያንጋጠጥ አረፋ ይደፍቃል::

ተጨማሪ ያንብቡ:  ህ.ወ.ሓ.ት እና ኢትዮጵያ ( ገብረመድህን አርአያ)

በፍትህ ፍለጋ ስም፤ ቀደም ብሎ ከሃገሩ የተሰደደውም ቢሆን፤ ዲሞክራሲን በመቋመጥ በቁሙ እያንቀላፋ፤ መለኮታዊ ሃይል: የዲሞክራሲ ቄጠማ ቆርጦ፤ ሳር ጎዝጉዞና: አልጋ አንጥፎ፤ ወደ አገርቤት ና ብሎ ጠርቶ፤ በጉሮሮው የሚንቆረቆር ቂቤ: እስቲመግበው ድረስ፤ ተኝቶ የምኞት ቅዠቱን ይቃዣል::

ከፊሉም: የምዕራባውያን የሸቀጥና የባሕል ማራገፊያ፤ ከመሆኑም በላይ፤ የሰለጠነ መስሎት: ከተፈጥሮ ህግ በተቃርኖ፤ በግብረ ሶዶማዊነት በመጨማለቁ፤ በዘመኑ የወረርሽኝ የኤድስ (AIDS) በሽታ፤ እንደ ቅጠል ከመርገፉም በላይ፤ ለመብቱ መቆም የማይችል: ተልካሻ ዜጋ ሆኗል::

ሁሉን ከእግዚአብሔር ጠባቂ በመሆኑ፤ በአይምሮው ላያስብ፤ በዓይኑ ላያይ፤ በጆሮው ላይሰማ፤ በእጁ ላይሠራበት፤ በእግሩ ላይራመድ ወስኖ፤ የበረዶ ግግር እንደሆነ፤ በወቅቱ ያለው ሥርዓት የፈጠረበትን ችግር፤ እግዚአብሔር እንደፈጠረበት በመቁጠር፤ « እግዜር ያመጣውን እግዜር እስቲያሳልፈው » እያለ እራሱ ለፈጠረው ስንፍና፤ ተጠያቂው እግዚአብሔር እንደሆነ በማሳበብ፤ ተኝቶ ያንኮራፋል::

እግዚአብሔር ከመፍጠር በላይ፤ ምን ያድርገን ?! የፈጠረልንን ዕንቁ ጭንቅላት፤ በዘርና በጎሣ ፖለቲካ እንደ ዕንቁላል እያገማን፤ እግዜር የሰጠንን የአገራች ለም መሬት፤ በዘር ፖለቲከኞች ተነጥቀን: በርሃብ ስናልቅ፤ ይባስ ብለው: ከአንዴም ሁለት ሦስቴ: በለኮሱት ጦርነ ሲማግዱን፤ በርሃብ ሲያስፈጁን፤ ወግዱ አናንተ ማን ሆናችሁ?! በማለት፤ በላያችን ላይ የተንሰራፋውን የግፍ ሥርዓት አሽቀንጥረን መጣል  ካልቻልን፤ ሰው የመሆናችን ምሥጢሩ እምኑ ላይ ነው ??

እውነቱን ለመናገር፤ እግዚአብሔር የእኛ የኢትዮጵያውያን ጉዳይ ስልችት ብሎታል:: እናንተ ሰነፎች ከአሁን በኋላ የናንተን ጩኸት የምሰማበት ጆሮ የለኝም ብሎናል::

እሰይ ! እርፍ ! ወደ ማን ይለቀስ ይሆን ?! ወደ ማን ሊጮህ ?!

ወደ አሜሪካ ? ወደ አውሮፓ ? ወደ ዓለም ባንክ ? ወደ አራጣ አበዳሪው (IMF) ?

ሱሚ ነው ! እነሱ መች ትርፍና ኪሳራቸውን ሳያሰሉ፤ ጥቅማችውን በእጥፍ ሳያባዙ፤ ገንዘባቸውን ያፈሳሉ ? ምናቸው ነንና ?!

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሙስሊሙ መሪዎች የፍርድ ሂደት ለ10 ቀናት ተቋረጠ

እንዲያውም እቤታቸው ቁጭ ብለው፤ በርቀት ቁልፍ ( remote control) ለሚያዟቸው አምባ ገነን ገዢዎቻችን፤ ቀጭን ትዕዛዝ፤ በማስተላለፍ፤ ለሰው በላው የካፒታሊስት ስርዓታቸው ጠባቂነት፤ የእኛ ከሲታ ወታደሮች፤ በእነሱ ወታደሮች ፋንታ፤ በሽብርተኝነት ሰበብ በየቦታው በሚከፍቱት ጦርነት፤ በጥይት ይረግፉላቸዋል:: ( የሱማሌውንና የደቡብ ሱዳኑን ጦርነት በምሳሌነት ይጠቅሷል) ታዲያ ምን ገዷቸው: ከእኛ ጎን በመቆም: አገልጋዮቻቸውን የእኛ አምባ ገነኖችን ይቃወማሉ ?!

የሚገርመው ጥቂቶቻችን ደግሞ፤ እንደደላው ሻኛችንን አሳብጠን፤ በአይምሯችን ውስጥ የወሲብ ድር እያደራን፤ የጥንባሆና የሃሺሽ ጭሳችንን እያንቧለልን፤ ጫታችንን እያለፋጨቅን፤ የቅንዝር በትራችንን ገትረን እንጎማለላለን::

በትግላችን ሥርዓቱን በመለወጥ: ነፃነትን፤ ፍትህ፤ እኩልነትና ሠላምን ማዋለድ አይሆንልንም:: እንዲያውም: የዲሞክራሲ ወርቃማ ዕንቁላል የምትጥል ዶሮ፤ በኢትዮጵያ እስከምትረባ ተጋድመን እንጠባበቃለን::

ልንቡጡን ሳይሆን፤ ልቡን ከተገረዘ ትውልድ፤ የሚፈልቅ ድፍረትና ቆራጥነት ባለመኖሩ፤ ከልቡ የሕይወት ምንጭ ደም ሳይሆን የሚፈልቀው ውሃ ነው:: ውሃ ያውም የረጋ: የማይንቀሳቀስ! ክርፋት ክርፋት የሚሸት::  (በምሳሌነት የአዲስ አበባ ነዋሪዎችን ይጠቅሷል)::

ከታሪክ እንደምንረዳው፤ በዋና ከተማ የሚኖሩ: የማንኛውም አገር ህዝብ፤ ለአንባ ገነን ሥርዓቶች መንኮታኮት፤ ዋና መሪ ተዋናይ እንደሆኑ ይታወቃል:: የዘመኑ የአዲስ አበባ ነዋሪ፤ የዘርና የጎሣ ፖለቲከኞች፤ በኑሮ ውድነት አጉብጠው: እየረገጡ ሲገዙት ዝምታን መርጧል::

የጊዜ ሩጫ፤ የሳምንታት ፍጥነት፤ የዓመታት ኩለት፤ የማይለውጠው:: በነበር ላይ ነበርን እንጂ፤ ነውንና ይሆናልን የማይጨምር፤ ያለፈን እንጂ፤ የወደፊቱን ለመኖር፤ ከእሱነቱ ውስጥ አምጦ፤ ሕይወትን መውለድ የማይቻለው:: ዛሬን እያመነታ፤ ነገን እየተጠራጠረ፤ የሥርዓት ለውጥን ፈርቶ: በሚጣልለት ምጽዋትና ፍርፋሪ፤ አፉን ተሸብቦ፤ በኩበት ላይ ተቀምጦ፤ ኩበት ኩበት እንደሸተተ፤ የኩበት አመድ ሆኖ: የሚያልፍ፤ ብኩን ዜጋ! ብኩን ትውልድ ::

ታዲያ: ዘወትር ጥላውን እያየ ከሚሸሽና፤ ነብሱን በጨርቅ ከቋጠረ ትውልድ፤ በትግል: የአንባ ገነን ሥርዓትን አስወግዶ፤ ድልን በማብሰር፤ ነፃነትን እንዴት አድርጎ ማዋለድ ይቻለዋል ??!!

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያልተገታ ምላስ አማራውን ይጎዳዋል አክሎግ ቢራራ (ዶር)

ከፍርሃቱ የተነሳ፤ የዘር ፍሬውን በራሱ ትኩሳት አቅልጦ፤ እራሱን በማኮላሸት: ጫንቃውን አደንድኖ፤ የባርነት ቀንበር ለመሸከም፤ ለሃጩን ያዝረበርባል::

ነፃነትን: ካለፈው ትውልድ ተቀበለ እንጂ፤ እራሱ ወጥቶና ወርዶ፤ ወድቆና ተነስቶ፤ ሞቶና ቆስሎ፤ ስላላገኛት፤ ያላትን ክብር በማቅለል፤ ዛሬም ከሌሎች በምጽዋት ይጠብቃል:: ክስረት ይሏችኋል ይህ ነው!!

በልመና ስንዴ ተረግዞ፤ በልመና ስንዴ ያደገ ትውልድ፤ በኢትዮጵያ ምድር በጭራሽ ጤፍ የሚበቅል አይመስለውም::  ልመናን የለመደ: የልመናን ትውልድ፤ ከተረጂነት ለማውጣት: የልመና ከረጢቱን ካልነጠቁት በቀር፤ ክብሩንና ነፃነቱን ፍለጋ አይሰማራም:: የእጅ እባሽ ለምዶ ክብሩን ሸጧልና !!

ዘረኝነት ነግሶ፤ ህጋዊ ሌብነት ተንሰራፍቶ፤ ዓሣ ዓሣ የሚሸቱ: የዘርና የጎሣ ፖለቲካ ቁማርተኞች፤ ኢትዮጵያን በጦርነት ሲማግዱ፤ ልጆቿን ለስደት፤ ለባርነትና፤ ለረሃብ ሲዳርጉ፤ ህሊናችንን ሸጠን፤ ሆዳችንን በፈርፋሪ እየሞላን መኖሩ፤ ከሰውነት በታች ዝቅ ያደረገን: መሆኑ የገባን ስንቶቻችን ነን ??!!

  • አርቆ ለማስተዋል የሸፈነንን፤ የዘርና የጎሣ ፖለቲካ፤ ገርስሰን ለመጣል፤ ከተጠናወተን ፍርሃትና አድርባይነት፤ በመላቀቅ፤ በአገራችን ላይ የማይጠገን ስብራት ከመድረሱ በፊት በአንድነት የምንነሳበት ወቅቱ አሁን ነው !!
  • ዘረኝነት አንገፈገፈኝ፤ በደል በቃኝ የምንልበት ጊዜው አሁን ነው !
  • በጦርነትና በርሃብ አዙሪት አንማገድም በቃ ማለት አሁን ነው !
  • ማሰብ፤ መጻፍና መናገር ሰብዓዊ መብታችን እንጂ፤ ከአምባ ገነኖች በምጽዋት የምንጠይቀው ስጦታ አይደለም ማለት አሁን ነው !
  • ኢትዮጵያ ከአሁን በኋላ የምባ ገነኖቹ የህወሃትና፤ (የኦህዴ/ኦነግ ጥምር) የብልጽግና ተብዬ፤ የሌቦች ስብስብ መፈንጫ አትሆንም !!
  • የዘር ግምቡ ይፍረስ፤ ህጉም ይከለስ ወይም ይሰረዝ !!

 

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !!

በአዲስ ዓመት፤ በሥርዓት ለውጥ ወደ አዲስ ተስፋ !!

ነፃነት፤ እኩልነትና ወንድማማችነት ይለምልም !!

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ህዝቧን ይባርክ !!

ነሃሴ 30 ቀን 2015 ዓ.ም ( 05/09/2023 ) እኤአ

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share