ዉኃን ምን አጮኸዉ ቢሉ ድንጋይ አሉ !

 

ሁላችንም ሠዉ ሆነን የጠፈጠርን ኢትዮጵያዉያን በራሳችን አገር እና ወገን ለዕድሜ ልክ  አሳር እና እስር የዳረገን ምን እና ማን እንደሆነ እንኳን ማገናዘብ አጥቶን ኢትዮጵያ አገራችን ከረጂም ዓመታት ጀምሮ ለብዙኃን ኢትዮጵያ ጣራ አልቦ አሰር ቤትሆና ቆይታለች ፡፡

ይህም በጥቂቶች እና በጥላቻ በሰከሩ ስግብግቦች ማን አለብኝነት እና ንቀት የቀንድ አዉጣ ፖለቲካ ከዕዉነት መለየታቸዉን መስማት በማይፈልጉት የተወለደ የአገር እና ህዝብ መከራ ነዉ ፡፡

ኢህአዴግ ከ1983 ዓ.ም ጀምሮ የፖለቲካ ስርዓትን በመጠበቅ የጭቆና እና አድሎ ስርዓትን በማዘርጋት እና በማጥብቅ በዜጎች ላይ ወዳጂ እና ጠላት አድርጎ የመፈረጂ አባዜ ከራሱ ዉጭ አገሪቷ ችግር እና የዜጎች የመከራ ዘመን መራዘም እንደ ጊዜ መግዣ በማድረግ የሕዝቡን ዕሮሮ የቁራ ጩኸት እያለ ራሱን በራሱ ቁራ አድርጎ ይኸዉ አስከዛሬ ቀጥሏል፡፡

ዛሬ ላይ ስለ ሠላም አስፈላጊነት እና ጦርነት ክፋት ኢህአዴግ ሲናገር መስማት የተለመደ ቢሆንም ሌሎች ስለ ሠላም እና ጦርነት እንናገር የሚሉ ከየትኛዉም ቡድን፣ተቋም ሆነ ክፍል ሲናገሩ መስማት ግን እጂግ ያሳዝናል ፡፡

ለዚህም ኢህአዴግ የቀድሞዉን መንግስት ህዝባዊ መዋቅር በኢትዮጵያ ጠል አካላት ትብብር አፍርሶ ሽግግር መንግስት በሚል ሽግግረ -ኢህአዴግ ሲመሰርት የኢትዮጵያን ምሁራን ወክለዉ ከተገኙት ፕ/ር አስራት ወ/የስ እና መኮንን ቢሻዉ በቀር ያኔም ሆነ አሁን ያሉ እና የነበሩት እንደሚያወቁት  ትምክህተኛ ምሁር ተብለዋል፡፡

ይህም የሽግግር መንግስቱን ሲመሩ የነበሩት ሟች ያሉትን ይዞ ከላይ የተጠቀሱትና ሥራቸዉ ህያዉ ሆኖ የሚኖሩት ኢትዮጵያዉያን አገር ለማፍረስ ለመስማማት እና ሽግግር መንግስት ለመመስረት በለመስማማታቸዉ መድረክ ረግጠዉ እንደ ወጡ ስልጣንም ፣ጥቅምም ሆነ መኖር ሳያጓጓቸዉ ወደ ኋላ አለማለታቸዉን ታሪክ እና ትዉልድ አይዘነጋዉም ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ብን ብሎ የጠፋው የአብን አመራር ከወዴት ተገኘ?

እዚህ ላይ ሁላችንም መረዳት ያለብን ስለ ኢትዮጵያ አንድነት ፣አብሮነት ፣ ሠላም እና የጦርነት አስከፊነት ለመናገር የህሊናም ሆነ የህግ ልዕልና ያልነበራቸዉ ከዚያ አስካሁን ለአገር እና ለህዝብ ሳይሆን ለቡድን እና ለግል ጥቅም የፖለቲካ ስርዓት አምላኪ እና ተላላኪ ድርጂቶች፣ ተቋማት እና ግለሰቦች ዝም ብለዉ አገሪቷ እና ህዝቦች ከዚያ የሽግግር ጊዜ የኢትዮጵያ የጥልመት ዘመናት መባቻ ጀምሮ አስካሁን ያጨበጨቡ በአቋማቸዉ ቢቆሙ ይሻላል፡፡ በምንም መንገድ የሠላም እና የአንድነት ሀዋርያ ሊሆኑ አይችሉም ፡፡

ለዘመናት ዜጎች በተለይም ብዙኃኑ የኢትዮጵያ ህዝብ አካል የሆነዉ የዓማራ ህዝብ በትዉልድ አገሩ ለሶስት አሰርተ ዓመታት በስደት ፣በሞት እና በዘመናዊ ባርነት የበይ ተመልካች ሲሆን አንድም ዓለማዊ ሆነ ኃይማኖታዊ ድርጂት ድርጊቲቱን በስሙ ጠርቶ መሞገት ቀርቶ ጉዳዩን ፍትኃዊ እና ተፈጥሯዊ አድርጎታል፡፡

ሠዉ በሰዉነቱ እና በማንነቱ ሲሞት ሠዉ ሞተ ተብሎ ሳይሆን …….ብሄረሰብ ሞተ ከማለት ዉጭ አንድም በህዝብ እና በአገር ሀብት የሚንቀሳቀስ የመገኛኛ ብዙኃን አስከዚህ ሠኣት ለህዝብ ጆሮ አድርሶ አያዉቅም ፡፡

ሌላዉ ቀርቶ ለሠዉ ልጆች ሠባዊ መብት መከበር እንሰራለን የሚሉ እና ገለልተኛ ተቋማት እንኳ ከዚኅ በኋላ ተመጣጣኝ ግድያ፣መፈናቀል….ይሁን ሲሉ እንጂ ይህ ጉዳይ የዚህ ተጠያቂነት ነዉ ብለዉ ከዳር ሲደርሱ አይታወቅም ፡፡ ለአስረጂነት በጥቂቱ የትናንቱን የ17 ልጆች ፣ የመንገድ ላይ ተፍኖ የቀሩት ዜጎች ምንነት እና ደህንነት የት ደረሰ የሚል ካለ ህዝብ ፊት ይቁም ፡፡

ዜጎች ስለ ሠባዊ ክብራቸዉ ፣ ስለ አገራቸዉ ፣ ስለ ህዝባቸዉ ፣ ስለ ማንነታቸዉ፣ ስለ ዕምነታቸዉ …..ለዓመታት ሲሳደዱ ፣ ሲዋረዱ ፣ሲታረዱ ፣ሲሞቱ……ከህዝብ እና ከአገር መከራ ፊት የቆመ አይደለም ለምን ያለ የማህበረሰብ ፣የኃይማኖት እና የፖለቲካ ድርጂት መሰረታቸዉ አገር እና ህዝብ ሆኖ በምን ቸገረኝነት እና በአድር ባይነት ማየታቸዉ ዛሬ ለምንገኝበት ዝቅጠት ምክነያት ከመሆን በላይ እንኳን የመከራ ቀንበር ተሸካሚ ህዝብ ሰይጣን ዕምነቱን እንደሚነሳቸዉ አይጠረጠርም ፡፡ ለምን ለሚል ለራሱ አገር እና ሠዉ የማይሆን ሠባዊ ፍጡር ለአጋንት ሊሆን አይችልም ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  እንደ ቃየን፣ አንገዳደል! - ጆቢር ሔይኢ ከሁስተን ቴክሳስ

በድምሩ ዛሬ ስለ ሠላም ፣ ዕርቅ ፣ጦርነት የሚያወሩ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚያዉቃቸዉ እና የሰለቻቸዉ መሆኑን ዕልፍ አዕላፍ ማስረጃዎች መኖራቸዉ መጥቀስ ሳያስፈልግ በዚህች አገር ላይ ደካሞችም ብዙኃን እና አገሬ ብለዉ የሚኖሩ እና የሚጮሁ ስለሆነ ጩኸታቸዉን መስማት እና ራሳቸዉን ለይቅርታ እና ለተጠያቂነት ማዘጋጀት አለባቸዉ ፡፡ እነማን ነበሩ በሰላማዊ መንገድ ለአገራቸዉ እና ለህዝባቸዉ ሲሉ ሲታገሉ ሲያታግሉ ዕድሜ ዘመናቸዉን ሲሳደዱ ፣ሲዋረዱ ፣ሲታሰሩ ሲፈቱ ኖረዉ የሞቱ ፤የተንገላቱ …..? ይህን ለትዉልድ እና ለታሪክ መተዉ ነዉ ፡፡

ሁላችንም ባለችን አንዲት አገር ተከባብረን እና ተብረን ለመኖር ብቸኛዉ እና ወቅታዊ መድኃኒት ዕዉነት እና ዕዉነትን ለመናገር እና ለመተግበር ድፈረት እንጂ ስብከት እና ብልጣብልጥነት የቀንድ አዉጣ ፖለቲካ ነዉ እና በቃን ስሙን ፤ተቀበሉን ብሎ ፈሊጥ ለኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዉያን አይጠቅምም፡፡

ሁላችንም  ፍርኃትን፣አድር ባይነት ፣ክፋትን ፣ምቀኝነትን እና ስግብግብነትን  በድፍረት በቃን አለማለታችን  የመከራ ጊዜን ከማራዘም ዉጭ የአገሪቷንም ሆነ የህዝቧን የመከራ ቀንበር ያጠነክረዋል እንጂ አይሰብረዉም ፡፡

የኃይማኖት ተቋማት ታላቆችም ሠወችንም ሆነ ጥቅም ማጣትን በመፍራት ሆነ በማዳላት ዝምታን አስካሁን መምረጣቸዉ መቆም እና ለህዝብ እና ለአገር በሚበጂ ጉዳይ ላይ ያገባናል የሚሉበት ጊዜ አሁን ነዉ፡፡

አንድነት ኃይል ነዉ !

 

Allen!

 

1 Comment

  1. የእብድ ነገር ሃገሩን እያፈረሰ አትፈርስም የሚል የፓለቲካ ስብስብ ነው። ፓለቲካው ሁሉ ቢሉት ቢሉት ተመልሶ ያው ነው። ግን የህዝባችን መከራና ስቃይ፤ ረሃብና ሞት ያኔም ዛሬም ያው ነው። አሁን በአማራ ክልል በገጠርና በከተማ የሚደረገው ፍልሚያ ሁሉ ወዴት እንደሚወስደን የሚያውቅ አንድም ሰው የለም። ሰፈሩን እያቃጠለ፤ እያስደበደበ ቢፎከር፤ ቢጨፈር ዋጋ የለውም። በወያኔና በኦነግ የደረሰበት ግፍ አልበቃ ብሎ አሁን እንደገና በዚህ ህዝብ ላይ እሳት መለኮስ መታመም ነው። አሁን በየድህረ ገጽና በየሶሻል ሚዲያው በለው በይው የሚሉት ሁሉ ከንቱዎች ናቸው። ሲጀመር ጦርነት ለማንንም አይጠቅምም። ይህ ሲባል ኦነግ/ብልጽግና በአማራ ህዝብ ላይ ልክ እንደ ወያኔ የመከራ ዝናብ እያዘነበ አይደለም ማለቴ አይደለም። እንዲያውም ከወያኔ ዘመን በከፋ ሁኔታ የኦሮሞ ጠባብ የፓለቲካ ስብስቦች በአማራ ህዝብ ላይ ይህ ነው የማይባል በደል ፈጽመውበታል እየፈጸሙበትም ይገኛሉ። የእኔ ችግር ውጊያና ቀረርቶው በየሰው በራፍ ላይ መሆኑ ነው። ዓላማ ያለው ሰው ህዝባችን የሚያመሳቅሉትን ይፋለማል። አሁን ማን ይሙት ትላንት በአንድ የቀበሮ ጉድጓድ አብሮ ሃገር ተደፈረ በማለት የተዋጋው የአማራ ሚሊሻ/ልዪ ሃይልና ፋኖ ከኢትዮጵያ የመከላከያ ሰራዊት ጋር መዋጋት ነበረባቸው? ግን የሃበሻ ፓለቲካ እንደዚህ ነው። አጋሩንና የሚያስብለትን አይወድም። ጠላቱን አቅፎ፤ ጠላቱን ሸልሞ የሚያኖር ነው።
    ጠ/ሚሩና አማካሪዎቹ እንዲሁም የጦር አመራሮቹ ነገርን ሁሉ በጉልበት እቋጫለሁ ብለው መነሳታቸው ከአለፈው የሃገሪቱ የፓለቲካ እሰጣ ገባ ታሪክ አለመረዳት ነው። እብድ ፓለቲከኞች የሚታያቸው የራሳቸው ጥላ ብቻ ነው። ሲመከሩ አይሰሙ፤ ሲሸነፉ በቃኝ አይሉ፤ ብቻ ሁሌ አንዴ ከመታኝ ሁለት ጊዜ ልዥልጠው በሚል ፈሊጥ ሲፈነካከቱ መኖር ነው። አሁን እስቲ በትግራዪ ግጭትም ሆነ አሁን አማራ ላይ በሚነደው እሳት አትራፊው ማን ነው? የአማራ ህዝብ? በጭራሽ? መንገድ ተዘጋ፤ ይሄ ከተማ ተያዘ፤ ያ ፈረጠጠ እያሉ ማምታታት በሽታ ነው። ይህን ህዝብ ለረሃብና ለጠኔ እንዲሁም ሌሎች ከአሁኑ በላይ እንዲጨፍሩበት አዳክሞ ከማቅረብ ሌላ ፋይዳ የለውም። ወደ ልባችን ተመልሰን ልናስብ ይገባል። በፋኖም ሆነ በሲቪሉ ህዝብ ላይ አልፎ ተርፎም የሰራዊቱ ሞት የሃገር ሞት እንጂ በዘር የሚሰላ ነገር አይደለም። ከታጠቀ፤ ከሰለጠነ፤ ደጀን ካለው የሃገር ሰራዊት ጋር ተፋልሞ እዚህም እዚያም እደርሳለሁ ማለት ሃገሪቱን ሶሪያና የመን እንደሆኑት ለማድረግ ብቻ ነው። የሚራበው አማራ፤ የሚሞተው አማራ የጥይት በረዶ የሚዘንብበት የአማራ ምድር እንዴት ባለ ሁኔታ ነው ሰው ስለ ነጻነት የሚያወራው? ይህ ሸፋፋ የፓለቲካ እይታ ድሮም አልጠቀምም አሁንም አይጠቅምም። አሉ የሚባሉ የአማራ ልጆችን ለማስጨረስ እንጂ። የብልጽግናው መንግስት በዘፈቀደ ልክ በትግራይ ውጊያ ጊዜ እንዳደረገው ሰውን በዘሩና በቋንቋው እየለየ ማሰቃየትና ማሰሩ እድሜውን ያሳጥረዋል እንጂ አይረባውም። ግፍ በሌላ ግፈኛ እየተተካ እንሆ ዛሬ ላይ ደርሰናል። አያድርስ ነው ሌላ ምን ይባላል። ተው መገዳደል ይቁም። በህዋላ ይህ እንደ ሰደድ እሳት የተቀጣጠለው እሳት ማቆሚያ ያጣና ትርፍ አልባ አመድ ብቻ እንዳይቀረን እፈራለሁ። በዘሩ የተሳከረ የፓለቲካ ስብስብ ለሃገርም፤ ለራሱም አይጠቅምም። ዞሮ ተመልሶ እርስ በእርሱ ደግሞ ተከፋፍሎ ይፋለጣል። ጦርነት አፍራሽ ነው። በሩቅና በቅርብ አይዞአችሁ በለው የምትሉ ሁሉ መከራ ቤታቹሁን ሲያንኳኳ ያኔ ታርፋላችሁ። በዚህ ጦርነትም ሆነ በኦነግ በየስፍራው የሚፈጸመው ግጭት ለማንም የማይጠቅም ምድሪቱን ሰው አልባ የሚያደርግ ተግባር ነው። ዋ በህዋላ እኔ ነግሬአለሁ። የሚሳቅበት ሳይሆን የሚለቀስበት ሥፍራም እንዳናጣ። ይብቃን!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share