ጠላቱን የማያውቀው ታጋይና አታጋይ

መጸሃፍ ”—- በብብቱ እሳት ይዞ የማያቃጥለው ማነው?—–” በማለት  ይጠይቃል።
ታዲያ የዘመኑ የጎሳ ታጋይና አታጋይ ፤ እታገላለሁ የሚለው ”ብብቱ”  ውስጥ ከያዘው እሳት፤ አፍንጫው ሥር ካለው  የህዝብ ጠላት ጋር ሳይሆን አሻግሮ ‘ጣቱን  በመቀሰርና  አንዱ ህዝብ የሌላው  ህዝብ  ጠላት አድርጎ በመፈርጅ ነው።

የትግራይ ህዝብ ጠላት ወያኔ ነው። የኦሮሞ ህዝብ ጠላት በስሙ የተፈለፈሉ የጎሳ መንደርተኞች ናቸው። የአማራ  ህዝብ ጠላት ከማንም በላይና ዋናዎቹ  ከአብራኩ የተከፈሉት በምስለ ‘እኔ የሚገዙት  ሆድ- አደሮች ናቸው።የደቡቡም ሆነ የሌላው ህዝብ ጠላት ከ’ራሱ የሚወጡ ጎሰኞች ናቸው።

የኢትዮጵያ ህዝብ ጠላት  በጎሳና በመንደር የተደራጁ ከፍ ካለም በዜግነት ”ቦለቲካ” ስም የሚነግዱ  ሆድ -አደሮች ናቸው። ሁሉንም በጋራ አንድ የሚያደርጋቸው አንድና አንድ ነገር ቢኖር   ሥልጣን!።  ሥልጣን ደግሞ  ከድህነትና ከበታችነት ስሜት የሚያዎጣቸው የሚመሰላቸውን ገንዘብንና ኃይል ያሰገኝላቸዋል።  የመንፈስ ደሃ የሆነ ሰው ደግሞ የፈለገውን ዓይነት ሃብት ቢያከማችና የሥልጣን ማማ ላይ ቢወጣ፤   መጋቢ ሐዲስ እሸቱ ዓለማየሁ  እንደሚሉን –”በቁማቸው የሞቱ ፤ በኮትና በከረባት   ፤  በውድ መኪና እና በቢሯ’ቸው የተሸፈኑ ፣  በቪላ ቤት  በትልቅ አጥር  የተከለሉ ፤ ነገር ግን ማኅበረስቡና እድርተኛው ተሰብስቦ እድሩን ያላወጣላቸውና አልቅሶ ያልቀበራቸው ሬሳ ናቸው።—-“‘

እንግዲህ እነዚህ ናቸው ፤ የኢትዮጵያን ህዝብ   ከአፋ እየነጠቁ ለመዝረፍም ሆነ ሥልጣን ላይ ለመቆየትና  ከሚሰሩት ወንጀል  ተጠያቂ ላለመሆን ፤ በህዝብ መሃከል ጥላቻና በቀል እንዳለ አድረገው፤  የድንቁር እና የኋላ-ቀርነት ትርክት እንደ በቀቀን  ለእኛ ደጋግመው እየነገሩ፤  ትላንት በሚልዮን የሚቆጠር ህዝብ ጨርሰው ስላልበቃቸው፤  ዛሬ ደግሞ ለሌላ የሚሎዮኖች እልቂት  ጦርነት የጀመሩት።

ህዝብና ህዝብ ጠላት ሆኖ አያውቅም። ያውም የኢትዮጵያ ህዝብ፤ ለዘመናት በክፋም በደጉም ተሳስሮና ተከባብሮ የኖረው።  ነገር ግን ኋላ ቀሮች፣ ሰርተው መክበር፣ ተምረው ምሁር መሆን የማይችሉ  የበታችነት የተጠናዎታቸው ሰዎች  ፤ ክፍት የሥራ ቦታ በሆነው ”ቦለቲካ” እየተቧደኑ፤ የአንድን አገር ህዝብ በመከፋፈልና አንዱ በአብዱ ላይ እንዲነሳ  በጠላትነት በመፈረጅ ‘ርስ- በርስ እንዲገዳደልና  መተማመን እንዳይኖር ማደረግ ብቻ ሳይሆን ፤  ለዘመናት በደምና በተመክሮ በጋራ የተገነባን  እሴትንና ማንነትን በማፈረረስ  የአገርን ህልውና ለአደጋ አጋልጠዋል። የሰፊውን ህዝብ ህይወት አመሰቃቅለውታል።  በሰው ልጅ ታሪክ ተሰምቶና ታይቶ የማይታወቅ የጭካኔና የመከራ ዓይነት በመፈፀም ላይ ናቸው።

ያ -ትውልድ ለአገርችን ከአሰተዋወቀውና ትውልዱም የተካነበት  የሴራ ”ቦለቲካና” ችሎታ ”ጠላት ወይም ወዳጅ ”በሚል  ተከፋፍሎ  እስከ ቤተሰብ ድረስ የሚወርድ የመገዳደልና የመተላለቅ ብሂል  ነው።  የፈለጉትን ይቦትልኩና ይደስኩሩ ወይም ይድረሱ ፤  ከላይ ለመግልጽ እንደሞከርኩት ግባቸው  ስልጣንና ገንዘብ ነው።  ብሎም የገንዛ ወገናቸውን ሲያሰቃዩት የሚሰማቸው “ደስታ” ነው። ለዚህም ህዝብን ማገዶ አድርገው ያነዱታል። ከሬሳው ላይ ነጥቀው በዘረፋት ገንዘብ እነሱ “የአሳማ ” ኑሮ ይኖራሉ።

ህዝብን በጠላትነት ፈርጀውና ከፋፍለው የሚያቆራቁሱ  ቡድኖች ወይም መንደርተኞች የሚገዛ  ህዝብ   ደግሞ፤  ኋላ ቀር፣ እንድ አይነት ቋንቋ እየተነጋገረ የማይግባባ፣ ደሃ፣ ተመጽዋች፣ ምጻተኛ፤  ነጻነት የሌለው፤ እንኳን ነገን ሊገነባ፣ ትላንት የተገነባውንም በማፈረስ የተጠመደ፤ በየግዜው አጀንዳ እትየተፈበረከለት የሚናቆር ነው። እኛም  አሁን ያለንበት ሃቅ ይኽው ነው።

ጎሰኞች ወደ ሥልጣን ማማ ለመድረስና በአቋራጭ  የአገርን ገንዘብ ለመዝረፍ ፤ መጣንበት ያሉት ጎሳ የተጨቆነና፤ ጨቋኙ ደግሞ የራሱ ወገን መሆኑን ፤ የሃሰት ትርክት በመተረክ ከቢጤዎቻቸው ጋር ተቧድነው ለዓለፋት ሃምሳ ዓመታት የኢትዮጵያን ቤተ መንግሥት ለወመቆጣጠር በቅተው ፤ አገርን ወደ መቀመቅ ህዝብንም ወደ ማያባር እልቂት እየዳረጉት ይገኛሉ። —-

ተጨማሪ ያንብቡ:  ምነው -ፕ/ር ጌታቸው በዚህ ሰዐት- ወደ ጎሰኝነት - ይገረም አለሙ

– ሰላም የሁሉም ኢትዮጵያዊ ብቻ ሳይሆን የሰው ልጅ ፍላጎት ነው። ነገር ግን የኢትዮጵያን ህዝብ ከጦርነት እንዳይወጣ አድርገውታል።
-በልቶ ማደር የሁሉም ኢትዮጵያው ፈተና ነው። ነገር ግን የተመጸወተውን ስንዴና ዘይት  መዝረፍ ብቻ አይደለም ባህር ማዶ አሻግረው ይሸጡበታል።

-ሁሉም  የኢትዮጵያ ህዝብ መማርና ህክምናን ማግኘት ይፈልጋል። ነገር ግን እንኳንን ሊገነቡለት የተገነባውን ያስፈርሱበታል።
– ሁሉም ኢትዮጵያዊ  የተፈጥሮ ሰባአዊ መብቱ እንዲከበርለት ይፈልጋል፤ ነገር ግን እንደ አውሬ እያደኑ ያርዱታል፤ በየእስር-ቤቱ  እያጎሩ ፤  በላዩ ላይ ቤቱን እያፈረሱ ፤ ምድር ዓይታ የማታውቀውን ስቃይ  እሰከዚች ሰዓት ድረስ ይፈጽሙበታል።

– መከባበር የሁሉም  ኢትዮጵያዊ ፍላጎት ነው። ነገር ግን ጨቋኝና ተጨቋኝ  ፈጥረው  የመምናናቅና የጥላቻን መርዝ ይግቱታል።

አሁንም በሚገርም ሁኔታ በጎሳ ተቧድነው ከሚባሉትና ከሚያባሉት ድኩማኖች  ውጭ ፤ የኢትዮጵያ ህዝብ  በጠላትነት  ተያይቶ አያውቅም።
ዛሬ ላይ ሞኝ ቢያስመስልም ነገር ግን  ምንግዜም መነገርና መታወቅ ያለበት፤  ስለ ኢትዮጵያ ህዝብ  አንድነትና ትሥሥር  ከራሳችን አልፎ የታሪክ ተመራማሪዎች ብዙ ብለዋል። እንደ ምሳሌ  ዶናልድ ሌቪን ” ታላቋ ኢትዮጵያ” በተሰኜው መጸሃፍ ላይ  ምዕራፍ 4 እንዲህ ይላል፤

“—–ከብዙ ዘመናት በፊት የአሁኑን ገፅ የያዘው የኢትዮጵያ ህዝብ ጥልፍልፍ ልዩነት ስንመለከት ምን ዓይነት አንድነት ነው የምናይባቸው? የምንገነዘብላቸው? —
የታላቋ ኢትዮጵያ ታሪካዊ ተሞክሮ እንደ አንድ የተዋህዶ አንደምታ አድርጎ መናገር  ምን ትርጉም ይሠጣል?

የኢትዮጵያ የአንድነት ተሞክሮ በሁሉም ደረጃ የተመሰረተ በመላዋ በታላቋ ኢትዮጵያ በሰፊው ተንሰራፍተው በሚገኙ ሶስት ዋና ዋና ጉዳዮች ወይም ገፅዎች ላይ እንደሆነ አስባሁ፡-

1- በተለያዩ የኢትዮጵያ ህዝቦች መካከል ያለው ያልተቋጠ የመተሳሰርና የመስተጋብር ሂደት።

2-  በሁሉም የኢትዮጵያ ህዝቦች ዘንድ የተወሱ ባህላዊ መለያዎች መኖርና

3- ሁሉም የኢትዮጵያ ህዝቦች የተለየና ኢትዮጵያዊ የሆነ አቀባበል፤ አመለካከትና የሚሰጡት ምላሽ ናቸው፡፡

ልዩ ልዩ ባህላቸውን በመያዝ በጎሳ ከተከፋፈሉ በኃላ የታላቋ የኢትዮጵያ ህዝቦች በመራራቅና በተናጠል አልኖረም፡፡ ቢያንስ ላላፉት 2000 ዓመታት በንግድ፣በጦርነት፤ በሃይማኖት፣ በስደትና በሰፈራ፣ በጋብቻና በተለያዩ የማህበራዊ አገልግሎቶች ልውውጥ አማካኝነት ባልተቋረጠ ግንኙነትና መስተጋብር ኑረዋል፡፡

——-ይበልጥ አጉልተን ማውቅ ያለብንና የትኩረት መነጸርን ቁልጭ አድርጎ ሊንጻጸርበት የሚገባው ግን፤የታላቋ ኢትዮጵያ የተለያዩ ህዝቦች አብረው በመኖር በጋራ በሸመኑት የዝምድና  መረብ ላይ ነው፡፡ይህ የግንኙነትና የመተሳሰር መረብ፤ አንዳንድ ጊዜ ሲሳሳና ሲጠብ፤አንድ ጊዜ ሲደራጅና ስር ሲሰድ፤ ግን ምጊዜም የማይጠፋ የዝምድና መረብ ነው፡፡ ሰፊውን የኢትዮጵያ ታሪክ ለመጨበጥ ትክክለኛ መግቢውንና እውነተኛ አብነቱን የሚሰጠንም ይኽው ነው፡፡—-” እያለ ይቀጥላል።

ታዲያ ታላንትም ሆነ ዛሬ ያለው ” የቦለቲካ ” አሰላለፍና ጦርነት ፤ ተመሳሳይ ብቻ ሳይሆን፤  የኢትዮጵያ ህዝብ አንድነትና ትሥሥር  ለመናደና ፤   አሁን   ከምንግዜውም በከፋ ሁኔታ፤  ሁሉም በየመንደሩና በየጎሳው ” የንግሥና አክሊሊን” ይዞ ይዞራል።

ሻአቢያና ጀበሃ   የኤርትራን ህዝብ ከኢትዮጵያ ለመለያይተ የተጠቀመት ”ቦለቲካ”  ”ኤርትራ በኢትዮጵያ ቅኝ እየተገዛች ነው፤ ”አማህራይ”  ጠላታችን ነው።” የሚል ከጣሊያንና ከእንግሊዝ የተቀዳ  ነበር።  የሻአቢና ጀበሃ አባቶቻቸው  የእንግሊዝንና የጣልያንን መሰሪ ደባ የተረዱ ስለነበሩ ” ኢትዮጵያ ወይም ሞት” ብለው  ለምን አንድነትን እንደመረጡ እንኳን ለመረዳት የሚያስችል  ግንዛቤ እሰክ አሁን ድረስ በጥላቻ የታወረው አመለካከታቸው አልፈቀደላቸውም ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ቀባሪ ያጣው የወያኔ/ኢህአዴግ የአገዛዝ ስረአትና ባለቤት የሌላት ኢትዮጵያ

ታዲያ ለኤርትራ ህዝብ የተረፈው ነገር ቢኖር  ከኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር መለያየት ብቻ ሳይሆን፤ ስደት፣ ድህነትና በአምባገኖች መዳፍ ሥር መውደቅና የመከራ ህይወት መግፋት ነው። ለኤርትራ ህዝብ ከገዥዎቹ የበለጠ ጠላት የለውም። ይህም ስለሆነ ነው ዛሬም የኢትዮጵያና የኤርትራ ህዝብ ተለያይተው ያለተለያዩ መሆናቸውን በየግዜው የምናየው ሃቅ ነው።
ወያኔም ከሻአቢያ ከአባቱ ቀድቶ ”አማሃራን” በጠላትነት ፈርጆ፤ እሰክ አሁኗ ሰዓት ድረስ  በሚሊዮን የሚጠጉ የትግራይ  ወገኖቻችን ማግዶና ወላጆችን የወላድ መካን አድርጎ፡ ዘጠና በመቶው የሚሆነውን ህዝብ በተመጽዋችነት  እየገዛና በርሃብ እየጨረሰ፤   በአዲስ አበባው ብልጽግና አይዞህ ባይነት ለሌላ የእልቂት  ጦርነት እየተዘጋጀ ነው። ታዲያ ከዚህ ሁሉ እልቂት በኋላ እንኳን  የአማራ ህዝብ የትግራይ ህዝብ ጠላት ወይም የትግራይ ህዝብ የአማራ ህዝብ ጠላት ሲሆን አላየንም። የተረጋገጠው ሃቅ ለትግራይ ህዝብ   ከወያኔ የበለጠ ጠላት የለውም። ኑሮትም አያውቅም።

ኦሮሞ ነኝ የሚሉ ጎሰኞችም ትርክታቸው  ከማን አንሸ በሚል   የአማራንና ኢትዮጵያዊነትን በጠላትነት ፈርጀው፤ እነሱ የተደላቀቀ ኑሮና ዘረፋ ላይ ተጠምደው፤  በህዝቡ  ላይ ግን እየተፈራረቁና ስማቸውን እየቀያያሩ ከጦርነትና ከድህነት እንዳይወጣ ብቻ አይደለም፤  ከሌላው ወገኑ ጋር  ወደፊትም አብሮ እንዳይኖር የቻሉትን ሁሉ እያደረጉ ነው። በተለይም ዛሬ ”ግዜው የኛ ነው” በሚል በፍጹም ግብዝነት በኦሮሞ ስም  በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚፈጸመ ግፍ  አሁን ካላስቆምነው፤ በኋላ መጸሃፍ እንደሚለው”—ለቅሶና ጥርስ ማፋጨት—” ይሆናል።

ወደ አማራ ህዝብ ስንመጣ ትርክቱ ለየት ያለ ነው።  ከጣሊያን  ጀምሮ እስከ አገር ውስጥ ባንዳዎች ድረስ  የኢትዮጵያን ህዝብ ለመለያየት፤  አገር አልባና ”ርስ-በርስ ለማጫረስ   አማራ  ወይም ኢትዮጵያዊነት በጠላትነት ከተፈረጅና  እንዲጠፋ ከተወሰነበት ምዕት-ዓመታትን አሳልፏል። ታዲያ አማራውን እንወክላለን የሚሉት መለስ ዜናዊና ከኦነግ ጋር  አስምረው  የሰጧቸውን ክልል  የሙጥኝ ብለው ፤ ታላንት የወያኔ፤ ዛሬ ደግሞ የኦሮሙማ ብልጽግና ጉዳይ አስፈጻሚ ሆነው፤  በጠላትነት ከፈረጃቻቸው የጎሳ ቡድንም ሆነ ሥልጣን ወንበሩን ከያዙት በበለጠ የአማራ ጠላት  ከራሱ ከአማራ ህዝብ የወጡት  የባንዳ -ባንዳዎችና  በስሙ ተቃውሚ ፓርቲ አቋቁመው ፤ ከኦነጋዊ ብልጽግና ጋር ሥልጣን ተጋርተውና ሸንጎ ተሰይመው፤  ከቀበሌ እስከ ባህርዳርና ፤ በየመንግሥት መስራቤቱ የተሰገሰጉት ካድሪዎች ናቸው።

ጠቅለል ባለ መልኩ ስናየው፤   የኤርትራ ህዝብ ጠላት  ራሱ ሻአቢያ እንጅ ትላንት አማሃራ አሁን ደግሞ  የትግራይ ህዝብ አይደልም ፤ ሆኖም አያውቅም። የትግራይ ህዝብ ጠላት ወያኔ እንጅ የአማሃራ ወይም የኤርትራ ህዝብ አይደለም ሆኖም አያውቅም።
የአማራ ህዝብ  ቀንደኛ ጠላት ማንም  ሳይሆን ከአብራኩ የወጡት  የሌሎች ጉዳይ አስፈጻሚዎች   የሆኑት የትላንቶቹ ባአዴኖች የዛሬዎቹ የአማራ ብልጽግናዋችና ራሳቸውን አብን ብለው ይሚጠሩ የቀድሞው ዋና  የወይኔ ተላላኪ  የነበረው የአቶ በረከት ስማዖን ካድሪ የነበሩ  ናቸው።

የኦሮሞ ህዝብ ጠላት ማናም ሳይሆን ትላንትም ዛሬ በስሙ ተደራጅተው በስሙ የሚነግዱት ኦነግ፤ ኦነጋዊያንና ኦሮሙማ ናቸው። በሌላውም የጎሳ  ቡድንና ክልል ያለው እውነታ ተመሳሳይ ነው።

ስለዚህም  እውነትናኛ ነጻነትና እኩልነት፤ እንደ አንድ  ህዝብ፤ የህዝብ ፍላጎትና ጥቅም  ካስቀደምን ፤   የጋራ አገር እንዲኖረንና ከጦርነት አዙሪት ለመውጣት  መታገል  ከፈለግን  ቅድሚያ መስጠት ያለብን ጠላትን ማወቅ ነው።  ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት በኢትዮጵያ ህዝብ መሃከል ምንም አይነት ጠላትነት እንደሌለ  ትላንትም ሆነ ዛሬ  ታሪክ ያስተምረናል። እሰከ አሁንም እንደ አገር መቀጠል የቻልነው በኢትዮጵያ ህዝብ  አንድነት እንጅ፤ እንደ  ሻአቢያ፣ ወያኔና ኦነጋዊያን ቢሆን ኖሮ ከምድረ ገጽ በተፋቅን ነበር።
አሁንም አገራችን ለጎሰኞች አሳልፈን እስከ ሰጠን ድረስ የተፈራው  አገር አልባ የመሆን እድል እንደማይቀር ከምንግዜውም በበለጠ  አሁን ካለንበት ነባራዊ ሁኔታ ውጭ ማሰረጃ የለም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የእኛ “መንግስት” - ከተመስገን ደሳለኝ (ጋዜጠኛ)

በአገራችን በተለያዮ አካባቢዎች በገዥዎች ላይ  የሚደረገውን  ትግል  ስናይ በትክክለኛውና ፊት-ለፊት ባለው  የህዝብ ጠላት ላይ ሳይሆን ፤ በሁለተኛ ደረጃ  ልንታገለው በሚገባን ላይ   ነው።
ለምሳሌ  የገዥው ብልጽግና የኦሮሙማው አገዛዝ  ከወያኔ ጋር በመተባበር ” ህግ-ማስከበር” በሚል ሥም በጎንደር፤ በወሎ፡ በጎጃምና በሸዋ ህዝብ ላይ ጦርነት አውጇል። ነገር ግን ይኽን ጦርነት መንገድ የሚመሩትና እየጠቆሙ  ገዳማታ ሳይቀር በመድፍ የሚያስደብድቡት የአካባቢው  ተወላጆች ራሳቸውን ” የአማራ ብልጽግና” ብለው የሚጠሩት  የአዲስ አበባንና የመቀሌን ገዥዎች ጉዳይ የሚያስፈጽሙት ናቸው።   ይሁን እንጁ  እታገላለሁ ወይም አታግላለሁ የሚልው ቡድንም ሆነ  ግለሰብ እጣቱን የሚቀስረውና ተጠያቂ የሚያደርገው  በኦሮሞማው ብልጽግናና በወያኔ  ላይ ነው።

ተጨማሪ ምሳሌ  ወደ ኋላ ተመልስን ስንመለከት በኢጣሊያን የወረራ ዘመን፤ ከጣሊያን ወታደሮች በበለጠ ባንዳዎች አርበኞችንና ፋኖዎችን ይገሉና ለጠላት አስልፈው ይሰጡ ነበር።  በኋላ ላይ የኢትዮጵያ አርበኞችና ፋኖዎች ቅድሚያ የሰጡት ትግል   ባንዳውን ማደንና  መምታት  ነበር።  ሆደ-አድሩን ባንዳ መመታት   ሲጀምሩ፤ የጣሊያን ጦር  የመረጃ ቋቱ እየደረቀ፡ መንገድ መሪ እያጣ ሲሄድ  መፍረከረከ ጀመረ። መግቢያና መውጫ የሚያሳዩት ባንዳዎች እየተመናመኑ ሲመጡ፡፤  የኢትዮጵያ አርበኞችና ፋኖዎች ደግሞ በደፈጣ  ውጊያ ከዚያም ፊትለፊት እየተዋጉ  ነጻነታቸውንና አንድነታቸውን አስከበሩ።

አሁን በየቦታው የሚካሄደው ትግል ለድል እንዲበቃ ከተፈለገ ቅድሚያ   በአካባቢ ገዥዎችና ሆድ አደሮች ላይ ማተኮር አለበት። የአካባቢ ካድሪዎችንና ምስለ-እኔ  ገዥዎችን  ማሰውገድ ከተቻለ ፤ የአዲስ አበባው ብልጽግና አቅም እያጣ፣ በራሱ ሆድ – አደር ካድሪዎች እየተከዳ ከዚያም እየተፍረከረክ መምጣቱና ለኢትዮጵያ ህዝብ  እጅ መስጠቱ የማይቀር ነው።

አሁንም ቢሆን የኦሮሙማው ብልጽግና ዕድሜውን ለማራዘም የሚሞክረው  የጎሳ ቡድኖች ጋር በማበር በህዝብ ላይ ጦርንቱን በማስቀጠልና ወልቃይትንና ራያን ወያኔ እንዲወር በማድረግ የመሃል አገር ትግሉን አቃጣጫ በማሰቅወየስና አዳዲስ አጅንዳዎች በመፈብረክ ነው።  ከዚህም አልፎ በአገራችን  አንድም መርህና አቅድ ያለው ኢትዮጵያዊ ታጋይ  ድርጅት ያለመኖሩ ፤  ለብልጽግናና ለወያኔ  እድሜ መራዘም  ዋናው ምክንያት ነው፣፣

ሰለዚህም   አሁን በየቦታው የሚካሄደውን  የተበጣጠስና መሪና ተመሪ የማይታወቀውን ትግል
በማቀናጀትና ወደ አንድነት በማምጣት፤  አንድ ወጥ የሆነ  የትግል ድርጅትና የማህበራዊ መገናኛ በመፍጠር፣ባህር ማዶ የሚገኙ ኢትዮጵያኖችም  ልዩነታችውን አስወግደው በአንድነት በመቆምና ትግሉ የሚያስፈልገውን ድጋፍ በማድረግ ፤  ሁሉም ዜጋ ከጎሰኝነትና ከመንደርተኝነት ወ’ቶ   ለሁላችንም መዳኛ ለሆነው ለኢትዮጵያዊነትና ለኢትዮጵያ መታገል የግድ ይለናል።
በአንድነት ተደራጅቶ የታገል ህዝብ ደግሞ  ለድል እንደሚበቃና ለገዥዎቻችን ትምህርት እንደሚሰጥ ካለፈው የኢትዮጵያ ህዝብ ትግል መማር ይቻላል። ነገር ግን ያልተደራጅ ህዝብ ገዥዎችን ማስወገድ ቢችልም መልሶ የሚተከው ገዥዎችንና ጎሰኞችን መሆኑን አሁን  አገራችን ያለችበት ከበቂ በላይ ማስረጃ ነው። ስለዚህም  ጠላቶቻችን እንወቅ! እንደራጅ! በጽናትና በኢትዮጵያዊነት መንፈስ በአንደነት እንታገል።

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኖራለች!!!

———//——–ፊልጶስ
ሃምሌ 2015

E-mail: Philiposmw@hotmail.com

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share