እራሳቸው ቢነግሩንስ? – ጠገናው ጎሹ

ለዚህ አስተያየቴ መነሻ የሆነኝ ከሰሞኑ ከአየር መንገድ የቦርድ ሰብሳቢነት በአብይ አህመድ የአትፈለግም ድብዳቤ ተሰናብተው በአየር ሃይል አዛዡ ይልማ መርዳሳ ተተኩ የተባሉት የአቶ ግርማ ዋቄ ዜና እና በአንዳንድ ማህበራዊ ሚዲያዎች ሲንሸራሸሩ የሰማኋቸውና ያየኋቸው አስተያየቶች ናቸው። በዜናውና በአስተያየቶች ተገቢነት ላይ ጥያቄ ማንሳት ትክክል ያልሆነም ብቻ ሳይሆን ከባድ ድንቁርናም ነውና አስተያየቴም ለምን ይወራል ወይም ይተረካል የሚል አይደለም።

በአስተያየቴ ውስጥ የማነሳቸው ነጥቦች ከሚከተሉት ዋነኛ ጥያቄዎች የሚመነጩ ናቸው።

1) የመነጋገሪያችን ትልቁ (ዋናው) ትኩረት በፖለቲካ ወለድ ወንጀል የበሰበሰውና የከረፋው ሥርዓት ላይ ሳይሆን በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ (በካድሬነት ወይም የሥራ እድልን ላለማጣት) በሥርዓቱ ተቋማት ውስጥ የሚሠሩ ግለሰቦች በሚያጋጥማቸው ክስተት ላይ ለምንና እንዴት ይሽከረከራል?

2) ስለ ግለሰቦች መነጋገር ትክክለኛነት (ሥርዓት ያለ ግለሰቦች አይቆምምና) እንደ ተጠበቀ ሆኖ ስነነጋገር ግን አሻሻልናቸው የሚሏቸው ተቋማት ለጨካኝና ለዘራፊ ገዥ ቡድኖች ገቢ ምንጭነት (የምትታለብ ላምነት) እየዋሉ መሆኑን እያወቁ በሚሰጧቸው አስተያየቶችና ቃለ መጠይቆች ሁሉ ከደምሳሳና አድርባይነት ከተጠናወተው ዲስኩር ያለፈ አለመሆኑ (የአቶ ግርማን ቃለ መጠይቆች መታዘብ ይቻላል) አገርንና ህዝብን ከሚያስቀድም የመልጋም ዜግነት እሴት ጋር እንዴት ይታረቃል?

3) ስለ ሰሞኑ የሹም ሽር ጉዳይ ሿሚውም ሆነ ተሻሪው ከኢኮኖሚያዊ ጥቅም አልፎ ልዩ ብሄራዊ ምልክቴ ነው የሚለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዘራፊና ጎሰኛ ገዥ ቡድኖች ፍፁም ተቆጣጣሪነት ነፃ የሆነ የቢዝነስና የአስተዳደር ፍልስፍና እና አሠራር እንዲኖረው ለሚመኘው ህዝብ ግልፅና ግልፅ ለማድረግ ያልፈለጉት ለምንድን ነው?

4) እውን ይህ በቁራጭ ወረቀት (ደብዳቤ) ተሰናበቱ፣ ዓላማውም ግልፅ የሆነውን አየር መንገዱን በሸፍጠኛና ጨካኝ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ተረኞች ለማስያዝ ነው፣ ለዚህም የተተኪው ግለሰብ ጥሩ ማስረጃ ነው፣ ወዘተ በሚል የምንቀባበለውን ዜና እና ትንታኔ አቶ ግርማ ዋቄ ይጋሩታል እንዴቀደም ሲል በሰጧቸው ቃለ መጠይቆች ስለ አየር መንገዱ አገራዊነትና አገራዊ ኩራትነት የነገሩን አቶ ግርማ አሁን ዝምታን ለምን መረጡ?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለወልቃይት፤ ሐምሌ-05 ምስክር ትሁን! - በሙሉዓለም ገ/መድኀን

5) እውን እኛ እንደምናስበውና እንደምንመኘው ይጠርም ይርዘምም ወይም ቦግና ብልጭ ይበል በመንበረ ሥልጣን ላይ ከወጣው ሥርዓት ጋር ሁሉ ለመሥራት የፖለቲካ አመለካከት ችግር የሌለባቸው እንደ አቶ ግርማ ዋቄ አይነት ባለሙያወችና የረጅም ልምድ ባለቤቶች ከአሁኖች ገዥዎች ጋር በቅሬታ ተሰናበቱ ማለት ቢያንስ ጥያቄ አያስነሳም እንዴበግልፅ ራሳቸው እስካልነገሩን ድረስ ጥያቄው ጥያቄ ሆኖ ቢቀጥል ያስገርማል እንዴ?

የአቶ ግርማ ዋቄ ጉልህ አስተዋፅኦ በአየር መንገዱ አንፃራዊ የስኬታማነት ውጤቶች የታየና የሚታይ በመሆኑ በአግባቡ (በልኩ) ተገቢውን እውቅና እና አድናቆት የመስጠት አስፈላጊነት የሚያጠያይቅ አይመስለኝም።

የአቶ ግርማ ዋቄ በቀጥታ የአስከፊው ፖለቲካ ሥርዓት አስፈፃሚ ባለሙያ (ካድሬ) ላለመሆናቸውም ((ገዥዎች ከቀጥታ ካድሬነት ይልቅ በባለ ሙያነት ስም የሚያተርፉት ርካሽ የፖለቲካ ትርፍ የመኖሩ እውነታ ሳይዘነጋ) አንፃራዊ የሆነ አወንታዊ እውቅና መስጠት  አያስቸግርም ።

ይህ አይነት አንፃራዊ የግለሰቦች የሙያና የሞራል አቋምና ቁመና አየር መንገዱንም ሆነ ሌሎች ድርጅቶችን ወይም ተቋማትን አስከፊ በሆነና ማቆሚያ ባልተገኘለት ዝርፊያ፣ ሙስና፣ እጅግ አደገኛ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ቁማር ከበበሰበሰና ከከረፋ ሥርዓት ነፃ ከማውጣት አንፃር ሲታይ በእጅጉ ደብዛዛ ነው።

በሸፍጠኛ፣ ሴረና ጨካኝ  ፖለቲከኞች የማይገሰስ መልካም ፈቃድ ሹመትና ሥልጣን ተቀብሎ (ተቀብቶ) ነፃነት በተሞላበት የሙያና የሥራ ልምድ አንድን ድርጅት አጥጋቢነትና ዘለቄታነት ባለው አኳኋን ለውጠን የመላው ዜጋ (የአገር) መኩሪያና መበልፀጊያ እናደርገዋለን ማለት ከእኩያን ፖለቲከኞች ባልተናነሰ ህዝብን ማሳሳት (ማታለል) ነው የሚሆነው። ወደድንም ጠላንም የአቶ ግርማ ዋቄና ሌሎች መሰል ወገኖች ጉዳይም ከዚህ አይነት በእጅጉ ከበሰበሰና ከከረፋ የፖለቲካ ሥርዓት ሰለባነት ፈፅሞ ሊያመልጥ አልቻለም።አይችልምም። እንዲያውም አስተዋፅኦው በተቃራኒው ለእኩያን ገዥዎች የሥልጣን ማጠናከሪና ማራዘሚያ መሣሪያ መሆን ነው።

በፖለቲካ ወለድ ወንጀል ለበሰበሰውና ለከረፋው የሸፍጠኞች፣ የሴረኞች፣ የዘራፊዎችና የጨካኞች ገዥ ቡድን የምትታለብ ላም ለሆነው ተቋም በቁጥርና በአይነት የሚታይ መሻሻልን የሥርዓት ለውጥ የተካሄደ እስኪመስል ድረስ መተረክ ከትዝብት በስተቀር የሚያተርፈው ነገር የለም።

ይህንን እነርሱ (ባለሙያዎችና ባለ ብዙ ዘመን የሥራ ልምድ ባለቤቶች) በሚገባ ይረዱታል የሚል እምት አለኝ።

ይህንን እያወቁ የሹመት ቅብአቱን (ስጦታውን) ተቀብለው ሲገቡበት በነፃነትና በንፁህ ህሊና ሠርተን የእድገት ለውጥ ታሪክ እንሠራለን ብለው ከሆነ አለፍንበት የሚሉት ረጅሙ የሙያና የሥራ ተሞክሮ ከመሪሩ አገራዊ (የህዝብ) እውነታ ጋር ፈፅሞ አይገጥምም።

እያወራሁ ያለሁት ስለ አቶ ግርማ ዋቄ ወይም ሌሎች ግለሰቦች የግል ባህሪ፣ ህይወት፣ ሙያና ልምድ ፣ ወዘተ አይደለም። እያልኩ ያለሁት በፖለቲካ ወለድ ወንጀል በፅዕኑ በበሰበሰና በከረፋ ሥርዓት መልካም ፈቃድ የሚሾሙና የሚታዘዙ አንዳንድ ወገኖች (ግለሰቦች) ሊያሳዩት የሚችሉትን አንዳንድ የተናጠል “መሻሻል” እያሰላን ታሪክ ተሠራ እያልን እና ገዥዎች እነዚህኑ ግለሰቦች አትፈለጉም ሲሏቸው ደግሞ እንደ አዲስ ዜና እያራገብን እንኳንስ የሥርዓት ለውጥ ትርጉም ያለው ማስታገሻም ለመፍጠር ፈፅሞ አንችልም።

በዘመናት ጥረት የተሠሩ (የተዋቀሩ) ተቋማትና ግንባታዎች በእኩያን ገዥዎችና ፖለቲከኞች የሥልጣን ፉክክር ድምጥማጣቸው ሲጠፋ እያየን በሙያ የመሥራቱ ጉዳይ እንደ ተጠበቀ ሆኖ እውነተኛና ዘላቂ ለውጥ ወይም የተሠራን መልሶ የማያስፈርስ ሥርዓት ያስፈልገናል የሚል ሃሳብ ለመሠንዘር የፖለቲካና የሞራል ወኔ (political and moral gut) የሌለው የሙያና የተሞክሮ ባለቤት በሥልጣነ መንበር ላይ ለሚፈራረቁ ባለጌና ጨካኝ ገዥ ቡድኖች እድሚ ማራዘሚያ ከመሆን አያልፍም።

ለምን? ቢባል እንደ አብይ አህመድ አይነት እኩያን ገዥዎች ባለሙያዎችና በላብዙ ልምድ ባለቤቶች ነን የሚሉትን ግለሰቦች ተተኪ ካድሬዎቻቸውን (ከሥራ አስኪያጅ፧ ከቦርድ ሰብሳቢነት እስከ ታችኛው መዋቅር) እስከሚያዘጋጁ ይጠቀሙባቸውና “በሉ አሁን ከሁለት አንዱን ምረጡ ፡ የምንላችሁን አድርጉ ወይም ከነገ ጀምሮ እንዳትመጡ” ቢሏቸው ምኑ ይገርማል?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ቴዲ የኩዋስ ሜዳ ልጅ ነው - (ሄኖክ የሽጥላ -ገጣሚው)

የሰማነው ዜና ይዘት እውነት ከሆነ የአቶ ግርማ ዋቄ እጣ ፈንታስ ይኸው አይደለም እንዴ?  አቶ ግርማ ዋቄስ ይህንን መሪር ሃቅ ሳያውቁ ነበር እንዴ ቀደም ሲል ሥራ አሥኪያጅ እና “ከለውጡ” ወዲህ ደግሞ በቦርድ ሰብሳቢነት ሲሠሩ የቆዩት?

የአየር መንገዱን የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲከኞች ሰለባ መሆንና ይህ አይነት እጅግ አስቀያሚና አደገኛ የፖለቲካ ቁማር አየር መንገዱን ብቻ ሳይሆን ሌሎች ከኢኮኖሚ ጠቀሜታ አልፈው የአገራዊ ኩራት ምልክት (national symbols) የሆኑትን ተቋማት በእጅጉ እንደሚያጎሳቁል ግንዛቤው አልነበራቸውም እንዴ?

አገር ለንፁሃን ልጀቼ  በገፍ ተገድለው በቅጡ እንኳ አፈር የማይለብሱባት  የመፈናቀልና የቁም ሰቆቃ ምድር በሆነችበት  የበሽታና የግፈኞች ጨካኝ ጥይት ሰለባ የሆኑ ሚሊዮኖች በወቅቱ ቢታከሙ በህይወት መቆየት ሲችሉ በመጓጓዣ አለመኖር ምክንያት የሞት ሰለባ በሆኑባት ፣ እዚያው አየር መንዱ ጣቢያ ዙሪያ ቤታቸው (መጠለያቸው) በሌሊት ከልጆቻቸው ጋር በተኙበት እላያቸው ላይ እንዲፈርስ በተደረገባት  አየር መንገዱ ራሱ በጎሳ ጥላቻ ምክንያት ህሊናቸውን የተሰወሩ ካድሬዎች  የእኛ አይደለም/አይደለችም በሚሏቸው ወገኖች ላይ በሚያደርጉት ትዕግሥት አስጨራሽ ባህሪና ድርጊት በተበከለበት፣ ወዘተ እጅግ መሪር እውነታ ውስጥ የተሠራ የቢሮና የሆቴል፣ የተገዛ ወይም በኪራይ የተገኘ አውሮፕላን  እያሰሉ በእገሌ/በእገሊት ሥራ አስኪያጅነት ወይም ቦርድ ሰብሳቢነት ታሪክ ተሠራ የሚል የዜና እና የትንታኔ ጋጋታ የሚነግረን ከዘመን ጠገቡ ከክስተቶች ጋር በግልብ ስሜት የመጋለብ ክፉ አባዜ ለመውጣት ያለብን ፈተና በእጅጉ ከባድ መሆኑን ነው።

እናም የትኩረት አይናችንና ህሊናችን ለዘመናት በዘለቀውና ማነፃፀሪያ በሌለው የእኩያን ፖለቲከኞች ሥርዓት ላይ መሆን ሲገባው በሥርዓቱ ውስጥ የሚያገለግሉትን ግለሰቦች የሞላችና የጎደለች የሥራ ውጤት ዙሪያ እየተንከላወስን ወይም እየተርመጠመጥን እንኳንስ እውን የምናደርገው ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለዘመናት የመጣንበትን ፖለቲካ ወለድ መከራና ውርደት ማስታገስ አይቻለንምና ልብ ያለው ልብ ይበል!!!

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለአዲስ ዓመት ቅድመ ዝግጅት- በራሳችን ላይ እንዝመት፣- ይገረም አለሙ

June 11, 2023

 

1 Comment

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share