ወፏ ብዙ እየነገረችን ነው ። ሰማዩም ምድሩም የእርሶ ነውና ። መታወቂያ ፣ ፓሥፖርት ማን ይጠይቃታል ?

መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ 

” ልኡል ( Prince ) የማኬቬሌ የአመራር ጥበብን የሚያውጅ መፅሐፍ ነው ።ለእኛ ትውልድም የሚበጅ መልዕክትም አለው ። ሃሳቡን በጥልቀት ካየነው ። ለዚህ ላለንበት ቅጥ አንባሩ የጠፋበት የእውር ድንብር አመራር ዘመን አሪፍ ምክር እናገኝበታለን ። ውሥጡነሰ በሚገባ ከፈተሽነው ። አብሶ ለኢትዮጵያ የጠራ ና የጎለበተ አገረ መንግሥት ምሥረታ የራሱ የህነ ጠቃሚ ምክረ ሃሳብን ይዟል ። ” ተብሎም ይታመናል ። በፖለቲካ ምሁራን እና በአሣብያን ዘንድ ። መቼም በዚህ ዘመን ፈላስፋው ዘራያአቆብ መቄብርን ፈንቅሎ ወጥቶ ፣ የበዛ ሞራላዊ ምክር ቢለግሰን መልካም ቢሆንም ፤ የእኛን ፈላስፎችና ምሁራንን ከፍ ፣ ከፍ ለማድረግ ብቃቱ ያላቸው ምሁራን እስከሚነሱልን ጊዜ ድረስ ከነጋድራስ ገ/ህይወት ጋር ፣ በውጪ ፈላስፎች፣የፖለቲካ ሊቆችና የሥነ መንግሥት ተመራማሪዎችን ደምረን ሰው ከድንቁርና ተላቆ ሰው እንዲሆን መጣራችንን አናቆርጥም ።
ለአገረ ኢትይጵያ ታላቅነት እሥከ ቀኃሥ ( ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ) ያሉት ነገሥታት በበርታትና በትጋት መሥራታቸውንም በመመሥከር ፣ ዛሬ በ21 ኛው ክ/ዘ ያሉት የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ፣” ባዮሎጂ እንደሚገላቸው መዘንጋታቸውን እና -” ከራስ በላይ ነፋሥ ማለታቸውን የምን ታመጣላችሁ ድርጊታቸው እያሳበቀባቸው እንዳለ በትህትና እነግራቸዋለን ።
ማኬዬቬሊ፣ ከራሥ በላይ ነፋሥ ጋር በተያያዘ መልኩ ፣ ” ለምሣ ያሰቧችሁን ቁርስ አድርጓቸው ።” ከሚለው ምክሩ ” በሤራ እና በብልጠት ፤ በገዘፈ ጭካኔ ታግዞ … ሥልጣን ላይ መውጣት ቀላል ነው ። ” ከሚለው ምሣሌያዊ አስተምህሮቱ ውጪ ፤ ” ህዝብን በማክበር ፣ የህዝብን ሠላም ና ፀጥታ በማስከበር ፣ ህዝብን በእኩልነትና በፍትህ ላይ በተመሠረተ መንግሥታዊ ሥርዓት ማስተዳደር በዘላቂነት አገርን ለማስተዳደር ይበጃል ። ” የሚለው ምኩሩ ለዛሬው ዘመናዊ የአመራር ጥበብ እጅግ ጠቃሚ ምክር ለዓለም መንግሥታት እንደሚያገለግል ተገንዘቡ እንላለን ።
የአሜሪካን መንግስት በገደምዳሜ ፣ ( በዋሽግተን ፖሥት ጋዜጣው በኩል ) ከደብረፅዮን ይልቅ ጄነራል ፃድቃንን ለትግራይ የሽግግር መንግሥት መሪነት መምረጡ ከዚህ ፖለቲካዊ ሴራ አንፃር የሚታይ መሆኑን አሥምሩበት ።
ይሁን እንጂ ዛሬም የሤራ ፖለቲካና የእኔ አውቃለሁ ፣ እኔንን ብቻ ሥሙኝ ዳንኪራ በጉልህ እየተሰማ ነው ። ምንም በሤራ ፖለቲካ ባለሥልጣናቱ ፣ ለዜጎች በየጊዜው አሥደንጋጭ አጀንዳ እየሰጡ ቀናትን ቢሻገሩም ፣ ህዝብን ጎንበሥ ብሎ ይቅርታ የማይጠይቅና ከሥህተቱ የማይማር ገዢ ቢዘገይም በህዝብ መቀጣቱ እንደማይቀር ቆም ብለው ቢያሥታውሱ መልካም ነበር ።
ለመሆኑ ፤ በትግራይ ክልልም ሆነ ከትግራይ ክልል ውጪ የተፈፀመው የእርስ በእርስ እልቂት እጅግ አሣፋሪ አልነበረምን ? ይህንን የመጠፋፋት እሣት ፣ የቀኝና የግራ እግራቸውን የማያውቁ ጅሎች የለኮሱት እሣት ነበር ። አንዳችም ድል የማይገኝበት ማፈሪያና መሳቂያ ጦርነት በወንድማማቾች መካከል ተደርጎ አያሌ ወንድምና እህቶቻችንን ከንቱ መሰዋትነት ከፍለውበታል ። አካላቸውን ያጡ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ወገኖችም በመቀሌ ፣ በአዲሰሰ አበባ በባህር ዳር እና በአፋር አሉ ። ይኽ በእውነቱ እጅግ የሚያሲያዝን እና ከሆድ የማይወጣ ሐዘን በህዝብ ውስጥ እንደተከለ መረዳት እጅግ አሥፈላጊ ነበር ።
ሐዘኑ ከባድ እና ከሆድ የማይወጣ ከመህኑም በላይ ፣ ማፈሪያ ድርጊት እንደሆነ ዛሬ በዜጎች ሁሉ ታውቋል ። አሣፋሪና አንገት የሚያስደፋም ነው ። ይሁን እንጂ የትኛውም ባለሥልጣን ፣ ድርጊቱን ኮንኖ ራሱን በፀፀት ወቅሶ ፣ የተጎዳውን ህዝብ ፣ ያዘነውን ዜጋ ፣ ልባዊ ይቅርታ አልጠየቀም ። የአጎራባች ክልል ህዝቦችን ” ይቅር ለእግዛብሔር ” እንዲባባሉም መድረክ አልከፈተም ። ከባለሥልጣናት የመቀመጫ ሩጫ ( የዙፋን ሩጫ ) በፊት የሚቀድመው ” የህዝብ ይቅር ለፈጣሪ ” መባባል ነው ። ይሁን እንጂ ዜጎች ነገ ከትላንቱ በባሰ መልኩ እንዲተራረዱ ቢላዋ መሣሉ እነደቀጠለ ወፏ እየነገረችን ነው ።
ወፊቱ ፣ ” የአሜሪካ መንግሥት የዛሬ አቋም ፣ ከነገ ዘላቂ ጥቅሙ አንፃር ነው ። ” ትለናለች ። የአሜሪካ መንግሥት ተልዕኮ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለአሜሪካ መንግስት ማስገኘት ነው ። ኃያሉ አሜሪካ ፤ ለዘላቂ ጥቅሙ ደግሞ አሥተማማኝ ሠላም ይፈልጋል ።
የማንኛውም ኃያል መንግሥት ካፓኒዎች የሠላም ዋሥትና ማግኘት የሚችሉት የተረጋጋ መንግሥትና አገር ሲኖር እንደሆነ ያውቃሉ ። እናም መዋለ ነዋያቸውን ሊያፈሱ የሚችሉት የተረጋጋ አልጋ በኢትዮጵያ ሲኖር ብቻ እንደሆነ አሳምረው ያውቃሉ ።
አሜሪካም በአሜሪካ ርዕዮት የተጠመቀ ዙፋነ መንግሥት በኢትዮጵያ እንዲኖር ትፈልጋለች ። ሌሎች ኃያላንም ተመሣሣይ ሃሳብ ነው ያላቸው ። የራሳቸውን ርዕዮት ማሥረፅ ተቀዳሚ አላማቸው ነው ። ለፅድቅ የቆመ የመላዕክት ስብስብ የሆነ ኃያል መንግሥት በዓለም ከቶም የለም !
እናም ዘላቂ ሠላምን ለማዋለድ እና የኃያሏን አሜሪካ ዘላቂ ድጋፍ ለማግኘት ፣ ለምን መንግሥት ሑመራንና ወልቃይትን በፌደራል ሥር አድርጎ ራሳቸውን የቻሉ አሥተዳደሮች አያደርጋቸውም ? ” የሚል ምክረ ሃሳብ ያላቸው ምሁራን ከአሜሪካ ፖለቲካዊ ግብ አኳያ ብቅ እንዳሉ መገንዘብ ያሥፈልጋል ። “ ህዝቡም ልማትን እንጂ ድህነትን አይሻም ። እናም ለሁለቱም ዜጎቻችን የሥራ ዕድል በመፍጠር ችግርን እና ችጋርን ከሁለቱም ክልሎች ማሶገድ ይቻላል ። ያው ሰጥቶ መቀበል ። ነው ። “ ይሉናል ።
በተጨማሪም ፣ መንግሥት ቀጥሎ የተፃፈውን የማኬቬሌን ቲዎሪ ቢያሥተውል መልካም ነው ። ይሉናል ።
” Therefore, One Who Becomes A Prince Through The Favor Of The People Ought To Keep Them Friendly, And This He Can Easily Do Seeing They Only Ask Not To Be Oppressed By Him. But One Who, In Opposition To The People, Becomes A Prince By The Favor Of The Nobles, Ought, Above Everything, To Seek To Win The People Over To Himself, And This He May Easily Do If He Takes Them Under His Protection. Because Men, When They Receive Good From Him Of Whom They Were Expecting Evil, Are Bound More Closely To Their Benefactor; Thus The People Quickly Become More Devoted To Him Than If He Had Been Raised To The Principality By Their Favors; And The Prince Can Win Their Affections In Many Ways, But As These Vary According To The Circumstances One Cannot Give Fixed Rules, So I Omit Them; But, I Repeat, It Is Necessary For A Prince To Have The People Friendly, Otherwise He Has No Security In Adversity… ”
( ” THE PRINCE ” Nicolo Machiavelli Page 78 )
” በህዝብ ይሁንታ ለሥልጣን የበቃ የአገር መሪ ( ልኡል ) የሚጠበቅበት የህዝብ ፍቅር ግለቱን ሳይቀንስ እንዲቀጥል ፣ ከህዝብ ጋር ያለው ወዳጅነት የበለጠ እየጠበቀ እንዲሄድ ማድረግ ይኖርበታል ። ይህንን ማድረግ ደግሞ ቀላል ነው ። ህዝብ ጭቋኝ መንግስትን ስለሚጠላ የጭቆናን ቀምበር በህዝብ ትከሻ ላይ ለመጫን መቃጣት ፈፅሞ የለበትም ። በህዝብ ይሁንታ ወደ ሥልጣን የመጣ መሪ ከህዝብ ፍቃድ ውጪ እርምጃውን ካደረገ ከህዝብ ሥለሚነጠል ሥልጣኑንን በቀላሉ ያጣልና ማንኛውንም አርምጃውን ከህዝብ ፍላጎት ጋር ማድረግ ይጠበቅበታል ።
” ከህዝብ ይሁንታ ውጪ ፣ በሌሎች የፖለቲካ ኃይሎች ( መሣፍንቶች ) ድጋፍ ለሥልጣን የበቃ የአገር መሪ ( ልዑል ) ቢሆን እንኳን ፣ በሥልጣን ለመሰንበት ከፈለገ ፤ በአሸናፊነት በትረ ሥልጣኑንን እንደያዘ ፣ ፍቅደውም ሆነ ተገደው ከተሸናፊው መንግሥት ጎን ተሠልፈው ለነበሩት ሁሉ ምህረት ና ይቅርታ በማድረግ ፍቅራቸውን ማትረፍ ይኖርበታል ። ህዝቡ ከቀደመው ሥርዓት በተሻለ ነፃነት ኑሮውን እንዲመራና ህይወትን እንዲኖራት የማድረግ ድጋፉን በግልጽ መስጠት አለበት ። ህዝብ ጭቆና የሌለበትን ህይወት መሪ እንዲሆን ደግሞ የቀደመውን በኃይልና በፍርደ ገምድልነት የሚመራውን ቢሮክራሲ በመቀየር ተጨባጭ የሆነ የህዝብ ቅቡልነት ያለው ቢሮክራሲ በመላ አገሩ መዘርጋት ተቀዳሚ ሥራው መሆን አለበት ። ሽንገላ የሌለበት ፤ ያልተቀባባ ፤ አግላይ ያልሆነ የፖለቲካ ሥርዓትን ፤የሞራል ልልና ባላቸው ባለስልጣናቱ በአገሩ ካላሰፈነ ግን ፤ አልጋው ሊረጋለት አይችልም ። አልጋው የማይረጋለትም በመላ አገሩ “ በቢሮክራሲ ሥም “ በየቀያቸው እውነተኛ ፍትህን ሥለሚነፈጉ ፣ እውነተኛ ፍትህን አጥተው በባርነት ከሚኖሩ ለክብራቸውና ለነፃነታቸው ሲሉ በሥርዓቱ ላይ ማመፅ ስለሚጀምሩ ነው ። … “
እዚህ ላይ ፣” ህዝብ በጭቆና ሲሰቃይ ድንገት ደርሶለት ፣ ጨቋኝን ላሶገደለት ጉልበታም ልዑል (የፖለቲካ ፖርታ ና መሪ ) ሁሉ ፣ ድጋፉን በዩሉንታ እንደሚሰጥ ማሥተዋል መልካም ነው ። ግፉአን የተፈፀመባቸውን ግፍ ባይረሱትም ፣ ከአሰቃያቸው ገዢ ነፃ ያወጣቸውን ገዢ በውለታ ዕዳ ተይዘው ንግሥናውን በይሁንታ ይቀበላሉ ። ይኽ ደጋፋቸው የሚቀጥለው ግን አገዛዙ ጨቆኝ ያለመሆኑንን በየዕለቱ በተግባር እያረጋገጠ እስከሄደ ጊዜ ድረስ ብቻ ነው። ” ይለናል ማኬቬሊ ፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ፣ ማክቬሊ የፖለቲካ ሊቅነቱን በዛ ዘመን ባስመሰከረበት ልዑል በተሰኘ መፅሐፉ ፣ ለአገር መሪዎች የሚከተለውን ምክር ሰጥቷል ።
“ አንድ የመንግሥትን ሥልጣን የያዘ መሪ ( ልዑል ) በህዝብ ተወዳጅ ሆኖ ለመዝለቅ የሚችልበት የተለያዩ የአገዛዝ መንገዶች እንዳሉ ቢታወቅም ፤ ከህዝብ ላይ ጭቆናንን አስወግዶ ፣ ጠንካራ ተቋማትን ገንብቶ ፣ ፍትህን በመላው አገር እንዳሰፈነ አይነት ሥርዓተ መንግሥት ቅቡልነት ያለው በዓለም አይገኝም ። በአገዛዙ ሥርዓት ፍትሃዊነት ሰበብ ፣ የአጠቃላይ ህዝቡን ቅቡልነት ያገኘ መሪ ደግሞ ፤ የተደላደለ መንበር ይኖረዋል ። በጭቆና ፣ በኃይል ና በያዘው በትር ፣ ተቀናቃኙን ባሶገደበት መንገድ ህዝብን ቀጥቅጦ ና አንቀጥቅጦ ፤ በጭቆና ቀንበር ውስጥ አስገብቶ ፣ እየበዘበዘ ለመግዛት ቆርጦ የተነሳ መሪ ግን በመንበሩ ላይ አይሰነብትም ፡፡ ” በማለት ፡፡…
ጥቂት ሥለ ማኬቬሌ ላውሳና ፅሑፌን በምክር ልቋጭ
ኒኮሎ ማኪያቬሊ ፣ ወደ ኢጣላዊዋ ፣ፍሎራንሥ ምድር የመጣው እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ግንቦት 3 / 1969 ዓ/ም ሲሆን ፤ ነፍሱ ከሥጋው የተለየችው ደግሞ ሰኔ 21/ 1527 ( እኤአ ) እንደሆነ ዊኪፒዲያ ላይ ከተፃፈው የህይወት ታሪኩ መረዳት ይቻላል ። …
ሰውየው የተዋጣለት ጦረኛ ጀነራል ፣ ሥመጥር ዲፕሎማት ፣ የታሪክ አዋቂ ፣ ፈላስፋ ና የህዝብ አሥተዳደር ሊቅ ነበር ።
በዘመኑ ከሚታወቁ ሥመ ጥር ምሁራን ተርታ የሚሰለፈው ማኪያቬሊ፣ በጥልቅ አሳቢዎቹ በነ ሩሶ ና ስፔኖዛ የሚደናቅ የፖለቲካ አመለካከት ነበረው ።
በገሃዱ ዓለም የፖለቲካ እንቅሥቃሴ ውሥጥ የመንግሥት ሚና ምን መሆን እንዳለበት ከማኬቬሌ በላይ ያብራራ ሊቅ በዛን ዘመን አልነበረም ።
የጠንካራ መንግሥትን አወቃቀርና ሚናንን በተመለከተ ሉዑል ( The Prince ) በተሰኘ መፀሐፉ በጥልቀት አብራርቷል ። ለሥልጣን ሲባል በሴራ መግደልን ና የአገዳደሉን መንገድ የተለያዩ ልኡላን ወደ ሥልጣን የመጡበትን ታሪክ በመፀሐፉ በመጥቀስ ” በ ‘ ካሮት‘ ብቻ ሳይሆን ‘ በትርም ‘ አገር ለመግዛት እጅግ አሥፈላጊ ነው ። ” በማለቱ በጥቂት ምሁራን ውግዘት ና የእርኩሰት መምህር ( Teacher Of Evil ) እሥከመባል ቢደርሥም ፤ አውሮፓውያኑ ” ይኽ ከንቱ ወቀሳ ነው ፡፡ ” በማለት ” የእኛ የዘመናዊ፣ ፖለቲካ ፍልሥፍና እና የፖለቲካ ሳይንሥ አባት ማኬቬሊ ነው ፡፡ ( The Father Of Modern Political Philosophy And Political Science. ) ” በማለት በአስተምህሮቱ ዛሬም ድረስ ፣ከዘመኑ ጋር እየበረዙ ይጠቀሙበታል ፡፡
ማኬቬሊ በአርሱ ዘመን በልዩ፣ልዩ ግዛት በተከፋፈለችው ኢጣሊያ የፍሎረንሥ ግዛት ከፍተኛ ባለሥልጣን ከመሆኑም በላይ ወታደራዊውን ጉዳይ በበላይነት የሚመራ የጦር ጀነራልም ነበር ።
ማኬቬሊ ፣ የመንግሥት ሥልጣንን በቅጡ ለመጠቀም የግለሰብን የግል ሞራል ና የቡድንን ሞራል በሚገባ ማወቅ እንደሚያሥፈልግ ይመክራል ፡፡ በህዝብ መሐል ዝነኛ እና ቅቡልነት ያለው መሪ ለመሆን የአጠቃላይ ህዝቡን ሞራል እንጂ የግለሰቦችን ሞራል ለመጠበቀ መባዘን የለበትም ፡፡ ዜጎችን ሁሉ ድርጊት በመፈፀም ተወዳጅነቱን የሚጨምር ተግባር ሁሌም ለመከወን መጣር እንጂ በጥቂት ግለሰቦች ሞራል ግንባታ ላይ በማተኮር የብዙኃኑን ሞራል መጨፍለቅ ፣የራስን ውድቀት ያፋጥናል ባይ ነው ፡፡
ሥለሞራል አብዝቶ በመጨነቅ ፣ ፊት ለፊት የተደቀነን አውዳሚ አደጋን ችላ ማለት ና መሰናክሉን ገለል ከማድረግ መዘግየት ፤ ወይም መዘናጋት የኋላ ፣ ኋላ የማይቀለበስ አደጋ ሊያሥከትል እንደሚችል አጥብቆ ይመክራል ።
” ሥህተት ቢሆንም ቀድሞ የኃይል እርምጃ በመውሰድ አደጋ አዋላጁን ከማሶገድ መቆጠብ የሚያሥከፍለው አደጋ የማይቀለበስ ይሆናል ፡፡ ፊት ለፊት የመጣብህን አደጋ ሥለሞራል በመጨነቅ ልትመክተው ካቅማማህ የአደጋው ሰለባ ትሆናለህ ። ” በማለት ፣ ልዑላን ግልፅና በዲፕሎማሲያዊ መንገድ የማይቀለበሥ አደጋ ከፊታቸው ተደቅኖ በሞራል አመካኝተው እጃቸውን አጣምረው ቁጭ ካሉ ፣ ቁጭ ባሉበት እንደሚቀበሩ ፣ በበዙ ምሳሌዎች ያሳስባል ።
( አንባቢ ሆይ ፣ በዚኽ የማኬቬሊ ፍልስፍና መሠረት ኃያሏን ጃፖን በአንድ ጊዜ አቅመ ቢስ ያደረጋት የአሜሪካ አቶሚክ ቦንብ መሆኑንን አትዘንጋ ። ሄሮሽማና ናጋሳኪ የተባሉ ሁለት ከተሟችን እሥከነ ህዝባቸው እምሽክ ያደረገውን አውቶሚክ ቦንብ ፤ ግዙፉን እና ጀግናውን የጃፖን ጦር ከግዛት ማስፋፋት አላማው እንዳቀበውም አትዘንጋ !! የጀፓን ህዝብ በዚህ ሥቃይን በሚያበዛ ፣ ሰቅጣጭ ሞትን አሥከታይ አቶሚክ ቦንብ ከሚያልቅ ጦርነቱን ለማቆም መወሰኑ ተገቢ ነው ። …. )
በማኬቬሊ እምነት ፤ ” ማንኛውም አገዛዝ የበዛና የሠለጠነ ሠራዊት ኖሮት ፤ የሚያሥተዳድረውን ህዝብ በተደጋጋሚ ፣ ቅቡልነት የሌለው ሞራለ ቢስ ተግባር በመፈጸም የሚያሳዝነው ከሆነ ፤ የልኡሉ ወታደሮቹም ሥርዓት የሌላቸው ና ቀምቶ በይዎች ከሆኑ ፤ በጉልበተኛ ና በቀማኛ ወታደራዊ ኃይሉ መከታነት ብቻ በሥልጣን ላይ ለመሰንበት ከቶም አይችልም ። …”
እውነት ነው ። የአንድ አገር መንግሥት በሥልጣን ለመሰንበት ከፈለገ ፣ የሚያስተዳድረውን ህዝብ ልባዊ ፍቅር ማግኘት ይኖርበታል ። ከሚያስተዳድረው ህዝብ ፍቅር ለማግኘትም ዜጎች አለአድሎ እኩል ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ቅቡልነት ያለው ፍትሐዊ ሥርዓት መዘርጋት አለበት ።
ይህ ፍትሐዊ ሥርዓትም ለእያንዳንዱ ዜጋ እኩል አገልጋይነቱን በኢኮኖሚያዊ ፣ በሶሻል እና በፖለቲካዊ ሥርዓተ መዋቅሩ በተግባር የሚያረጋግጥ ሆኖ መቀረፅ ይኖርበታል ።
መንግሥታዊ ሥርዓቱም ፣ ዜጎችን በአንድ ዐይን በሚመለከት የሶሾ ፖለቲካል ኢኮኖሚ ሥርዓት ካልቀረፀ በስተቀር ህዝቡ የተረጋጋ ፤ አገርም ሰላም የሰፈነበት አይሆንም ።
መንግሥት በግጭት ላይ ያልተመሠረተ ቅብብሎሽ ፤ ህዝብም የሰከነ እና የጣመ ህይወት የሚኖረው መላው ዜጋ የሚተዳደርበት ሥርዓተ መንግሥት ለጠበበ የቡድን መብት ያላደለና ከፋፋይ የሆነ ህገ መንግሥትም ከሌለው ብቻ ነው ።
አንድ አገርን እና ዜጎቿን ለመጠበቅ ና ለማሥተዳደር የመሪው ወንበር ላይ የተቀመጠ መንግሥት እጅግ በመጥበበ ፤ በአይጠረቄነት በመስገብገብ ፤ በገዳይ በትር ፤ አንዳንዴም በሽንገላ እየደለልኩ ለረዢም ዓመት ሥልጣን ላይ እቆያለሁ ብሎ ካሰበ ፣ ማሥተዋልና ጥበብ በአይምሮው ስሌለለው ሥልጣኑን ከማሳጠር ውጪ የሚያተርፈው አንዳች ነገር የለም ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሥላሴዎች እርግማን፤ (አንድ) አዳክሞ ማደህየት (ከፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም)

1 Comment

  1. ( ማኬቬሌ ወደ እዚች ምድር የመጣው እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ግንቦት 3 / 1969 ዓ/ም ሲሆን …የሚለው በግንብት 3/1469 ዓም ተብሎ ይታረም ። )

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share