የ”ብልጽግና” ጠቅላይ ገዥነት (totalitarian state) ከበላቸው ጌ

Totalitarian state ማለት ምን ማለት እንደሆነ መጀመሪያ ልግለጽ፡፡ Totalitarian state ማለት በእያንዳንዱ የአገሪቱ ህዝብ ህይዎት ዘርፍ ላይ ፍጹም ቁጥጥር ያለው የመንግስት አይነት ነው፡፡ የዚህ አይነት መንግስታዊ ቅርጽ ሁሉንም ኢኮኖሚያዊ፤ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ብቻ ሳይሆን የህዝቡን አመለካከት እሴት እና እምነት ለመቆጣጠር በመንግስትና እና ህብረተሰብ መካከል ያለው ልዩነት ያስወግዳል፡፡ ሃይማኖታዊ አምልኮዎችና ክንዋኔዎች እንኳ ሳይቀር ከመሪው አስተሳሰብና እምነት ጋር የማይጣጣሙ ከሆነ አይፈቀድላቸውም፡፡ በመጀመሪያዎቹ የስልጣን ዘመኑ  በፓርቲው ማዕከላዊ ኮሚቴ ውሳኔውች ይመራል፡፡ ሥልጣኑን ካደላደለ በኋላ  ሁሉምንም የአገሪቱ ጉዳዮች  በፓርቲው መሪ/ለቀመንበር ስር ይወድቃሉ፡፡ ሁከትና (violence)ና ሽብር (terror) አላማውን ለማሳካት እንደ ዋና ማስፈጸሚያ መሳሪያ ይጠቀምባቸዋል፡፡ አምባገነን መንግስት ሁከት እንዲፈጠር የሚያደርግበት ዋና አላማ በጠላት የፈረጃቸውን ቡድኖች ለማጥፋት፤ የተጎጅዎችን ንብረት ለመዝረፍና ተቃዋሚዎችን ለመቅጣትና ተስፋቸውን ለማጨለም ነው፡፡ በተመሳሳይ የሽብር ድርጊቶችን የሚፈጽመው በህዝቡ ዘንድ ከፍተኛ ፍራቻ ስሜት እንዲፈጠርና ተቃውሞችን ለማዳፈን ነው፡፡ሁከትና ሽብር ለመፈጸም በህቡእ የሚንቀሳቀስ ፖሊስና በደንብ የታጠቀ ሃይል በማደራጀት ይጠቀማል፡፡ ህዝቡን በማነቃነቅ የአገር ውስጥ ጠላት ናቸው በሚላቸው ላይ ጦርነት ያዘምታል፡፡

ሥለ Totalitarian state ይህን ያህል ካልኩ ስለ”ብልጽግና” ጠቅላይ ገዥነት (totalitarian state) መገለጫዎች የተወሰኑ ነገሮችን ላንሳ፡፡ እንደሚታወቀው አብይ መጀመሪያ ወደ ስልጣን ሲመጣ ትኩረት አድርጎ የሰራበት የሀይማኖት መሪዎች ጋር ከፍተኛ ቅርርቦሽ መፍጠር ነበር፡፡ የሁሉንም ሀይማኖት መሪዎች ቤተ-መንግስቱ እየጠራ በመካከላቸው ያሉ ልዩነቶችን እየፈቱ እንዲሰባሰቡ ማድረግ ነበር፡፡ ይባስ ብሎም ሀይማኖታዊ ስብከትም ይሰብክ ነበር፡፡ የሃይማኖት መሪዎች እውነት መስሏቸው፤ “እኛ  የሃይማኖት መሪዎች  ያልፈጸምነውን ይህን ተግባር በማድረግዎ ምስጋና ይገባዎታል” ብለውታል፡፡ በእርግጥ ሁሉም የሀይማኖት መሪዎች ሙሉ በሙሉ አላመኑትም፡፡ ለምሳሌ ነባሮቹ የወንጌላውያን አብያተ-ቤተክርስቲያናት አባቶች ሙሉ በሙሉ አካሄዱ ላይ ጥርጣሬና ችግር እንዳለበት በማህበራዊ  ሚዲያዎች በሚሰጡት መጠይቆች መረዳት ይቻል ነበር፡፡ በአለም ላይ እንዳለው የነባር ወንጌላዊያን አብያተ-ቤተክርስቲያናት ሁሉ የአብይን ብልጽግና ወንጌል አስተምሮ  መጽሐፍ ቅዱሳዊ አይደለም የሚል እምነት ስላላቸው ይመስለኛል፡፡ በዚህም የተነሳ በእሱ ግፊት በተቋቋመው ካውንስል አባል አልሆኑም፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ አባቶችና ምእመናን ግን የሰውየዉን ፍላጎት ያወቁት ዘግይተው በየቦታው በተከሰቱ የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሉና አማኞች መሳደድና ግድያ ሲፈጸም ነው፡፡ በኦሮሚያ በተለያዩ ጊዚያት በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያኖችና ምዕመናን ላይ የደረሰውን አደጋ ለማጣራትና እርምጃ ለመውሰድ ያደረገውም ጥረት የለም፡፡ በደረሰው ችግር እንኳ አንድ ቀንም አስተባብሎ አያውቅም፡፡ ይባስ ብሎም በግጭቱ የሞቱትን በብሄር እየቆጠረ በአማራና በኦረሞ መካከል የበለጠ መቃቃር እንዲፈጠር ይሰራ ነበር፡፡ ብዙ ሰዎች ይህ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትሩ እርምጃ ወይም የሀዘን መግለጫ የማያደርግበት ምክንያት መንግስታዊ መንበሩ ስላልጠና ነው የሚል አመለካከት ነበራቸው፡፡ ይህ ከሆነ ሞጣና ጎንደር ላይ መስጊዶች ሲቃጠሉና ሀይማኖታዊ ብጥብጥ ሲከሰት ለምን መግለጫ በማህበራዊ ትስስር ገጾቹ ሰጠ? መልሱ በማይወደው የአማራ ክልል ላይ ሁከትና ሽብር እንዲፈጠር ፍላጎት ስለነበረው ወይም የሽብር ድርጊቱን ራሱ ያስፈፅመው እንደነበር ወደሚል መላምት ይወስዳል፡፡ በአሁኑ ሰዓት የኦርቶዶክስ ክርስትናን ለማደከምና ወደ እሱ የሚፈልግው እምነት ለመውሰድ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ ለፍጹም አምባገነናዊነቱ ዋና መገለጫ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ሁሉም እምነቶች በእሱ እሳቤ መሰመር እንዲገቡ እንደሚያደርግ ሬኔ ለሆርት (2020) ና አንደሪው ዲኮርት (2022) የተባሉት ጸሀፊዎች በግልጽ አስቀምጠውታል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የስብሰባን ምንነት በተመለከተ በተለይ ለሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ

በእስልምና እምነት አባቶችና ተከታዮች በኩል የተለያዩ ሴክቶችን ወደ አንድ አምጥቷል በሚል እሳቤ ምንም እንኳ ዳሰሳ ጥናት ባልሰራም ለሰውየው  ያለቸው ድጋፍ የተሸለ መስሎ ይታየኛል፡፡ ይሁንና በቅርቡ በተካሄደውን የመጀሊስ ሹም ሽር የነባሩን እስልምና እምነት (ሱፊስት) ተከታዮች ዘንድ ቅሬታን የፈጠረ ይመስለኛል፡፡ በተቃራኒው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ድጋፍ እንደሰጣቸውና የመጅሊሱንም ስልጣን ያገኙት መሆኑን በማመን የሰለፊ ተከታዮች ድጋፍ ይሰጡታል፡፡ በእኔ እምነት ይህ የሰለፊ ተከታዮች ድጋፍ ዘላቂ ሊሆን ይችላል ብየ ጥያቄ ሳነሳ ጥርጣሬ ውስጥ እገባለሁ፡፡ሬኔ ልፎርት (2020) “Mind over matter: Abiy Ahmed’s aim to “Pentecostalize Ethiopian politics” በሚል በጻፈው ጽሁፍ የአብይ አላማ የፖሊቲካ ስልጣን በወንጌላዊያን በላይነት እንዲያዝና የፖለቲካ ስርዓቱም በብልጽግና ወንጌል አስተምሮ እንዲቃኝ ማድረግ ነው፡፡ የአንድ አገር የፖለቲካ ስልጣን ክፍፍል ብዝሐ-ሀይማኖትና ብሄር ባለበት አገር ፍትህአዊ ካልሆነ፡ የትም እንደማይሄድ ሌላ አገር ሳንሄድ የኛው ታሪክ ያስተምረናል፡፡ በአሁኑ ሠዓት ለጥቂት የሙስሊም ልሂቃን ስልጣን በመስጠት አጋር ለማደረግና ለማስመሰልም ጥረት እደረገ ቢሆንም የረዥም ጉዞው ግን የወንጌላዊያን ስልጣን ያውም የኦሮሞ የበላይነት እንዲረጋገጥ ማድረግ ነው፡፡ ስለሆነም አሁን ያለው ድጋፍ ይቀጥላል የሚል እምነት የለኝም፡፡

በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚስተዋሉ ሁከቶችና ሽብሮች ሌላኛው የአብይ መንግስት ጠቅላይ-ገዥነት (Totalitarianism) ማሳያ ናቸው፡፡ እንደሚታወቀው አብይ ወደ ስልጣን ከመጣበት ጀምሮ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ከፍተኛ ሁከቶችና ብጥብጦች ተከስተዋል፡፡ በመጀመሪያዎቹ አመታት የተከሰቱ ሁከቶች/ግጭቶች በህወሐትና በኦነግ እንደሚፈጸሙ መንግስትም ያሳብብ ነበር ህዝቡም ያምን ነበር፡፡ በእርግጥ የእኔም እምነት ነበር፡፡  በወቅቱ አብይ የደህንነትና የመከላከያ ሪፎርም ሲያደርግ ከፍተኛ ችግር እንደሚከሰት እምነቱ ነበረኝ፡፡ ለ27 ዓመት የተደራጀን ደህንነትና መከላከያ ወዴያውኑ አፍርሶ ሌላ መዋቅር መዘርጋት በራስ  አንገት ላይ እባብ እንደ መጠምጠም ይቆጠራል፡፡ ሠውየው “የመጀመሪያው ዙር የትግራይ ጦርነት” አበቅቷል፤ ብሎ ለፓርላማው በአወጀበት ወቅት የቀድሞው ደህንነትና መከላከያ መዋቅር በሙሉ ሃይሉ ህግን ለማስከበር መሰናክል ሆኖበት እንደነበር ገልጾታል፡፡ ይህን በከፊልም ቢሆን እጋረዋለሁ፡፡ ምክንያቱም የራሴ የሚለው ደህንነትና  መከላከያ  መዋቅር ሳያጠናክር ነባሩን ማፍረስ ዋጋ ያሳጣልና፡፡ የቱርኩ ፕሬዜደንት ኤርዶጋን ወደ ስልጣን ሲመጣ ቀደም ሲል የነበረውን አታ ተርክ establishment ሙሉ ለሙሉ ለመቀየር አላማ ነበረው፡፡ ነገር ግን የደህንነት፤ የፖሊስና መከላከያ መዋቅራዊ ለውጥ ወዲያውኑ አላካሄደም፡፡ ምክንያቱም በመንግስታዊ አስተዳሩ ላይ ከፍተኛ ስጋት እንደሚያስከትል ያውቃልና፡፡ የእነዚህን ተቋማት መዋቅራዊ ለውጦች የተገበረው ቀስበቀስ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች በደህንነትና መከላከያ ላይ አብይ ወዲያዉኑ መዋቅራዊ ለውጥ ባያካሂድ ኖሮ ለመንግስቱ አሰጊ ነበር ብለው ያምናሉ፡፡ ሰኔ 16 በነበረው የድጋፍ ሰልፍ ላይ የተከሰተውን ቦንብ ፍንዳታ ነባሩ ደህንነት ባለመወገዱ የተከሰተ ክስተት እንደሆነ ያምናሉ፡፡ በእኔ እምነት ይህ ክስተት የደህንነት መዋቅሩን ለመበታተን እንዲያስችለው በአብይና መዋቅሩ ሆን ተብሎ የተፈጸመ ይመስለኛል፡፡ ድርጊቱ በነባሩ ደህንነት የተፈጸመ ቢሆን ኖሮ የምርመራ ሂደቱና የፍርድ ቤት ውሳኔው በግልጽ ይቅርብ ነበር፡፡ እነ ጌታቸው አሰፋ ድርጊቱን ቢያስፈጽሙት ኖሮ ሰውየውን ለማስገደል የሚያቅታቸው ነገር አልነበረም፡፡ የቶታሊታሪያኒዝም ሜንታሊቲ ስላለው ሽብርን እንደመሳሪያ ስለሚጠቀምበት ነው፡፡

ከህወሐት ጋር የነበረውን ጦርነት አሸነፍኩ ካለ በኋላ  በሰሜን ሸዋ፤ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፤ በወለጋ ዞኖችና በሌሎች የኦሮሚያ ክልል ቦታዎች ብሄርና ሃይማኖትን መሰረት ያደረጉ ግጭቶች ለምን በባሰ ሁኔታ ቀጠሉ፡፡ በማህበራዊ ሚዲያዎችና በሌሎችም መገናኛ ዘዴዎች ሸኔ ብሎ የጠራውን ኦነግ ግድያዎችንና ግጭቶችን በኦሮሚያ ክልልና አጎራባች ክልሎች እንደሚፈጽም ይዘግባሉ፡፡ ለዚህ እኩይ ቡድንም ሽመልስ አብዲሳን ጨምሮ ሌሎች የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት ከፍተኛ ድጋፍ ያደርጋሉ ተብሎም ይዘገባል፡፡ የአብይ ድጋፊዎች አብይን ከደሙ ንጹህ እንደሆነ ያስተባብላሉ ወይም ሲከራከሩ ይሰማሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ የመነጨው የአብይን አምባገነናዊነት (totalitarianism)ና አታላይነት አለመረዳት ነው፡፡ ህዝቡ የሚፈለገውን በመሰበክ አገር ወዳዱን ዜጋ በእንቅልፍ ሰመመን ማስተኛቱ የሚታወስ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ይድረስ ለደባልቄ ቢተው   ( ዘ-ጌርሣም)

ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት totalitarian state ግጭት/ሁከትና ሽብር አላማውን ለማሳካት የሚጠቀምባቸው ዘዴዎች ናቸው፡፡ እነዚህን ለማስፈጸም ደግሞ በህቡእ የተደራጀ ሐይል ይጠቀማል፡፡ በእርግጠኝነት ኦነግ ሸኔ፤ አባቶርቤና ሌሎችም በህቡዐ የተደራጁ ቡድኖች የተቋቋሙት በአብይ መሪነትና ግድዎያዎችም የሚፈጸሙት በሱ እውቅናና ድጋፍ ወደ ሚል ድምዳሜ ይወስደኛል፡፡ እዚህ ድምዳሜ ላይ እንድደርስ ያደረጉኝ  ምክንያቶችን እንደሚከተለው ልዘርዝር፡፡

1. እነዚህ ታጣቂ ቡድኖች በነፍስ ወከፍ በሚባል ደረጃ የታጠቁት ዘመናዊ መሳሪያዎችን (ስናይፐር፤ ዲሽቃ፤ መትረየስና ሌሎችም) ነው ፡፡ ከደህንነት እይታ ውጭ ሁነው ነው እነዚህ መሳሪያችን እንዲታጠቁና አንድን ከተማ (አጣየን) 8 ጊዜ የማጥፋት እቅም  እንዲፈጥሩ ያደረጋቸው? ሌላ አካል ማን ሊሆን ይችላል?አብይ ሳያውቅ የሽመልስ ቡደን ብቻ? የአብይ መንግስት እጅ እንዳለበት የቀድም ኦነግ መሪዎች የሰጡት መረጃ እንደ ዋና ማስረጃ ሊወስድ ይችላል፡፡

2. የኦነግ ጦር ከኤርትራ እንደታጠቀ እንዲመጣ የተደረገበት ዋና አላማ ግጭቶችና ብጥብቶችን ማስፈጸሚያ መሳሪያ እንዲሆን ስለታሰበ ነው፡፡

3. በእየአመቱ በአማራ ክልል በሰሜን ሸዋ ዞንና ኦሮሞ ብሔረሰብ ዞን የተከሰቱ ከፍተኛ የሰው ሞትና የንብረት መውደም ምክንያቶችን በትክክል መርመሮ ለህዝብ ትክክለኛውን መረጃ ለማሳወቅና መፍትሔ ለማምጣት ፈቃደኛ አለመሆን፡፡ እንደሚታወቀው ቶታሊታሪያን መንግስት ጭር ሲል አልወድም የሚል ነው፡፡ ሁልግዜ የፖለቲካ አለመረጋጋት እንዲኖር ስለሚፈልግ ነው፡፡

4. በወለጋ ዞኖች ብሄርን መሰረት ያደረገ እልቂት ሲፈጸም አንድ ቀንም እንኳ ጸጸት ተስምቶት ስለማያውቅ ነው፡፡ ይልቁንስ ከ40 ዓመትና ከዚያ በፊት ከተላያዩ አማራ ክልል ቦታዎች በሰፈራ የሔዱ ሰዎች ከወለጋ ምድር እንዲጠፉ በህቡእ ያደራጀው የታጠቀ እኩይ ቡድን የማጽዳት ስራ እንዲሰራ ስለሚፈቅድ ነው፡፡

5. የሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያና የጀዋርን ተከበብኩ ጥሪ ተከትሎ በተለያዩ በኦሮሚያ ክፍሎች በተለይ ሻሸመኔ ብሄርንና ሃይማኖትን መሰረት ያደረጉ ዘግናኝ ጭፍጨፋዎችና የንብረት ወድመቶች የፈጸሙ አካላትን በማጣራትና እርምጃ እንዲወሰድ ቅንጣት ታክል ጥረት አለማድረጉ፡፡

የአገሪቱን ህዝብ በማነቃነቅ የአገር ውስጥ ጠላት ነው ከሚለው አሁን ሽርክና ለመፍጠር እየሞከረ ካለው ህወሐት ጋር ጦርነት ማድረጉ ሶስተኛው የአብይን መንግስት አምባገነን ጠቅላይነት (totalitarian state) መገለጫ ነው፡፡ በእርግጥ በብልጽግና መንግስትና በትህነግ መካከል ጦርነት የተከሰተው በአብይ ከፍተኛ ፍላጎት ብቻ ነው ለማለት አይደለም፡፡ የትህነግ የጦርነት ዝግጅትና ፉከራ ለአንድ አገር አንድነት ከልብ ለሚቆረቆር መንገስትም ወደ ጦርነት ማምራቱ አይቀርም፡፡ ምክንያቱም ህወሐት ጠንካራ ወታደርና መሳሪያ አለኝ በሚል እብሪት ጦርነት አውጇልና፡፡ ይህ እንደ ተጠበቀ አብይን በዚህ ረገድ ቶታሊተሪያን ነው ለማለት ያስደፈረኝ በሚከተሉት ምክንያቶች ነው፡፡

ህዝቡን ለጦርነት ለማነቃነቅ ይከተላቸው የነበሩ መንገዶች፡፡ አንደኛው መንገድ፡ ህወሐት ያደርግ የነበረውን የጦርነት ዝግጅትና ቅስቀሳ በመመልከት በሰሜን እዝ ላይ እርምጃ እንደሚዎስድ እየታወቀ ዝም ማለቱ ነው፡፡ ችግሩ እንደሚከሰት በመገመት በተጠንቀቅ እንዲቆም ማደረግ ሲገባ ሆን ተብሎ የተተው ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም የሰሜን እዝ መጠቃት ህዝብን ለማንቀሳቀስ ይረዳኛል የሚል እሳቤ ስለነበረው ነው፡፡ የወታደሩ መሞትና ተከትሎ የሚመጣው የህዝብ ስቀይ ለአምባገነን ጠቅላይ መሪ ምኑም አይደለም፡፡ ጦርነቱ ከተከሰተ በኋላ ህዝብን ወደ ጦርነት ለማነቃነቅ ይጠቀምባቸው የነበሩ ቅስቀሳዎች ሌላው ማሳያ ነው፡፡ ህዝቡ በተለይ የአማራ ህዝብ ለሃያ ሰባት አመት በህወሐት ይደርስበት የነበረውን መከራ በመኮርኮርና የጥላቻ ቃላትን (ጁንታ፤ የቀን ጅብና ሌሎችም)  በመጠቀም የብልጽግናው መንግስት ስልጣኑን በህወሐት እንዳይነጠቅ የሞት ሽረት አድርጓል፡፡ ይህን ስል ግን ህዝቡ ለጦርነቱ  የሚያስፈልግ ሎጅስቲክና ቀለብ ማቅረብ እንዲሁም በውጊያው ላይ የተሳተፈው በብልጽግና  መንግስት ቅስቀሳ ብቻ ነው ለማለት አይደለም፡፡ ከብልጽግና ቅስቀሳ ይልቅ የትህነግ በአማራ ላይ የምናወራርደው ሂሳብ አለን የሚል ፉከራና በአፋርና በአማራ ላይ የፈጸማቸውም ግፎች ለህዝቡ ንቅናቄ ትልቅ ድርሻ ነበራቸው፡፡ አብይ በጦርነት ወቅት ይጠቀምባቸው የነበሩ ቃላትና አጀንዳዎችና ከትህነግ ጋር የሰላም ስምምነት በኋላ የተናገራቸው ንግግሮች የአምባገነን ጠቅላይ ገዢነት ባህሪ መገለጫዎች ናቸው፡፡ በጦርነነት ወቅት የወልቃይት ጸገዴና ራያ ህዝብ አማራነት ሲያወራ እንደ ነበር ይታወሳል፡፡ የጦርነቱ ዋና አላማ ህወሐትን ከምደረገጽ ለማጥፋት እንደሆነም ይናገር ነበር፡፡ ከሰላም ስምምነቱ በኋላ ግን ከትህነግ ጋር ጦርነት የተዋጋነው ርስት ለማስመለስና ህወሐትን ለማጥፋት አይደለም  በማለት በመገናኛ ብዙሐን ደስኩሯል፡፡ እነዚህ የንግግር ዥዋዥዎች በትክክልም የቶታሊተሪያን መንግስትነት ባህሪን ያመለክታል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያ በታሪኳን እንደ ዐቢይ አሕመድ አይነት እቡይና ፍጹም አምባገነን አጋጥሟት አያውቅም! - አቻምየለህ ታምሩ

የመጨረሻው የሰውየው ቶታሊተሪይንነት መገለጫ በአገሪቱ ለአፍታም ቢሆን የተረጋጋ ፖለቲካ (political stability) እንዳይኖር ማድረጉ ነው፡፡ ከህወሐት ጋር የተደረገው ስምምነት ለአፍታም ቢሆን ረፍት ይሰጣል ተብሎ ሲጠበቅ ሀይማኖትን መሰረት አድርጎ ብጥብጥ እንዲነሳ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ በእርግጥ ይሄ ክስተት ቀደም ብሎ የታሰበበት ቢሆንም አሁን ላይ እንዲሆን የተደረገው ህወሐት የስልጣኑ ስጋት አለመሆኑን በማረጋገጡና ያለግጭት እንደማይኖር ስላአረጋገጠ ነው፡፡ የዚህ ሰሞን በኦርቶደክስ ክርስቲያን ዘግናኝ ግፎች እንዲፈጸሙ ሁለት ምክንያቶች ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡

  1. ከጦርነት በሗላ ልማት ላይ ትኩረት በማድረግ ውስብስብ የሆኑ የአገሪቱን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮች ለመፍታት መንግስቱ አቅም ስለሌለው ነው፡፡ እንደሚታወቀው ጠቅላይ ሚኒስተሩን ጨምሮ እስከ ታችኛው የመንግስት መዋቅር ድረስ የተሰገሰገው አብዛኛዉ ፖለቲከኞች የአገሪቱን ችግሮች ለመቅረፍ አቅም ያንሳቸዋል፡ ስለሆነም አማራጩ ግጭትን እየጠመቁ መኖር ነው፡፡
  2. የጽንፈኛ ኦሮሞችን ድጋፍ ለማግኘት ነው፡፡ እንደሚታወቀው አክራሪ የኦረሞ ብሔረተኞች የአብይን ወደ ስልጣን መምጣት በፍጹም አልተቀበሉትም፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያዊነትን ሲያቀነቅን እዉነት መስሏቸው ይጠሉታል፡፡ ሌላው ደግም በአንድ በኩል የአማራ ተወላጅ ነው በማለት ይፈርጁታል፡፡ የስልጣን ሽኩቻ በመካከላቸው መኖር ሌላኛው በሰውየው ላይ ጥላቻ እንዲኖራቸው ያደረገ ምክንያት ነው፡፡ የሰሞኑ የሰውየው እንቅስቃሴ የከረረ ስድብ ይሰድቡት የነበሩ ጽንፈኞች ድጋፍ እየሰጡት መሆኑን ከሚጠቀሙባቸው ማህበራዊ ሚዲያዎች መረዳት ይቻላል፡፡ ወደ ድጋፍ እንዲመጡ ያደረጋቸው ደግሞ ከልጅነታቸው ጀምሮ ኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት የአማራ ነው ተብለው የጥላቻ ቅስቀሳ ሲጋቱ በማደጋቸው ነው፡፡

በአጠቃላይ አብይ አገራዊ ራዕይ የሌለው ራሱን መሰረት አድርጎ የሚንቀሳቀስ በመሆኑ አገራቸን ለመፍረስ በመስቀለኛ መንገድ ላይ ትገኛለች፡፡ ስለሆነም ሁሉም ሰው የአብይን አስመሳይነትና አታላይነትን በመረዳት የአገሩን መፍረስ ለመታደግ ከምንጊዜውም በላይ ርብርብ ማድረግ አለበት፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share