February 10, 2023
9 mins read

ዛሬም የሰሚ ያለህ! ዲያብሎስን ማመን የቀጠልነው መቼ በማተቡ ይጠናል ብለን ነው?

t558854949e9frrr 1

t558854949e9frrr 1በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)

ሳጥናኤል ወይም ዲያብሎስ ከመላእክት አንዱ ነበር፡፡ ዳሩ ግን ሳጥናኤል የክህደትን፣ የቅጥፈትን፣ የስርቆትን፣ ሕዝብን ከሕዝብ የማጋጨትንና የጭካኔን መንገድ ስለመረጠ ከቅዱሳን መላእክት የተለየ እርጉም ሆነ፡፡  በዚህ እርጉምነቱም በእባብ ተመስሎ አዳምና ሄዋንን ከእግዚአብሔር አለያዬ፡፡ በሰላሳ ዲናር የይሁዳን ጭንቅላት በርዞ ክርስቶስን አሰከዳና አሰቀለ፡፡ በይህ አድግ ተመስሎ የኢትዮጵያን ሕዝብ መርጦ ባልተወለደበት ዘር ጨፈጨፈ፤ አስጨፈጨፈ፡፡  በሌላ አነጋገር የእባብንና ይሁዳን ፈለግ የተከተለ ዲያብሎስን አመነ፡፡ የይህ አድግ ገዥዎችን ያመነም ዲያብሎስን አመነ፡፡

“ዓይኔን ግንባር ያርገው!” ብለን  የውሸት መሐላ ካልማልን በቀር ለሰላሳ ዓመታት ያየነው የይህ አድግ ገዥዎች በኢትዮጵያ የፈጠሙት በደል ሳጥናኤል እባብንና ይሁዳን ተጠቅሞ ተፈጠመው በደል እጅግ የከፋ ነው፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ አሁንም የይህ አድግ ገዥዎችን አምኖ የሚናገሩትን የሚሰማ፣ በቃላቸው ይጠናሉ ብሎ በድርድር፣ በሽምግልናና በእርቅ አንድ ነገር ጠብ ይላል በሚል የሚንዘላዘለው የትዬ ለኔ ነው፡፡  ዛሬ ተፈጠመ የተባለው የጳጳሳት ድርድርም የዚሁ ተሳጥናኤል የከፉትን የይህ አድግ ገዥዎችን የማመን ከንቱ አባዜ ነው፡፡ ይኸንን መንዘላዘልና ከሳጥናኤል የከፉትን የይህ አድግ ገዥዎችን ሰው ማመን የሚያቆመው መቼ ነው?

ጳጳሳትም ሆነ ሌላው ዘለዛላ ፍጡር ተዋህዶንና ኢትዮጵያን ለማጥፋት ቆርጠው የተነሱትን የሳጥናኤል መንገድ ተከታዮች አምነው “አግዚአብሔር ሰማን” እያሉ የተሰውትን ሰማእታት ዘንግተው ወደተለመደው ዓለማዊና የሆድ ኑሮ ማቅናታቸው የሚያሳየው አሁንም የሳጥናኤል የማታለያ ቁማር ገመድ አለመበጠሱንና የሰውም የመጃጃል ኪሳራ አለማለቁን ነው፡፡

ጳጳሳት ሆይ ለመሆኑ የሰሟችሁ እግዚአብሔርና ስማቸውን የተሸከማችሁት ቅዱሳን መላእክት ወይስ  የይህ አድግ አምበሎችና አጫፋሪዎች?

እስከምናውቀው ድረስ ለመጀመርያ ጊዜ ጳጳሳትን እንደ አሽከር ተቢሮ እየጠሩ  ትእዛዝና ተግፃፅ የሰጡ ከመንፈስ ልእልና፣ ከባህልም ሆነ ከሃይማኖት የራቁ የይህ አድግ አምበሎች ናቸው፡፡ የጳጳሳት ትርጉሙ ክርስቶስ የተሰቀለበትን መስቀል የተሸከሙ፣ የመንኩሰ ሞተን ምልክት ቆብን የደፉ፣ መንፈሳቸውን አጎልብተው ሥጋቸውን ያደቀቁ፣ እውነትን የሚሰብኩ፣ የእግዚአብሔር ትእዛዛት ፈጥመው በአርያነት የሚያስፈጥሙ፣ መሰዋእትነትን የሚከፍሉ የእግዚአብሔር አገልጋይዎች ማለት ነው፡፡ ጳጳሳትን በትእዛዝ የጠሩት ደሞ የይህ አድግ አምበሎች ናቸው ፡፡ ይህ አድግ ደሞ ሕዝብን መርጦ ባልተወለደብት ዘሩ ከፋፍሎ የሚያሽጨረግደው፣ በስልጣን ሽሚያ ሚሊዮኖችን ያሳጨደው፣ ዋሽቶና ቀጥፎ የማያባራው፣ ሰርቆና ዘርፎ የማይጠግበው፣ የሳይጣን መንገድ የተከተለው የዲያብሎስ ቀፎ ነው፡፡ ይህም ማለት የእግዚአብሔር አገልጋዮች ታዝዘው ወደ ሳጥናኤል አገልጋዮች ቢሮ ሄዱ ማለት ነው፡፡ ጳጳሳት በትእዛዝ የሄዱትና ተደራድረው የተመለሱት መቼውንም በማተባቸው ተማይገኙት የይህ አድግ ገዥዎች ወይም ወደ ሳጥናኤል ሰዎች ነው፡፡

በሳጥናኤል ተከታዮች ታዝዞ ለድርድር ቀርቦና እነሱን አምኖ “እግዚአብሔር ሰማን” ማለት እንኳን በእግዚአብሔር አንደ ብረት ባልዛገ የሰው ህሊናም መቀለድ ነው፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ በዘር በሽታ ሕዝብን እርሱ በርሱ የሚያባለውን፣ የእርጉዝ ሆድ የሚያሰነጥቀውን፣ የህፃን አንገት የሚያስቀላውን፣ አሩግን ተቤቱ እያፈናቀለ ሜዳ የሚጥለውን፣ የሕዝብ አጥምና አጥንት የተገነባ አገር እንደ ካብ የሚንደውን ይህ አድግን እንደ ቡትቶ ሽርክርክ አርጎ ይቀደው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ በክርስቶስ ሐዋርያት የተቆረቆረችና በስንት አባቶች የተገነባች ቤተክርስትያን የሚያጠፋውን ይህ አድግን እንደ ሰሃራ በርሃ ድርቅ ያደርገው ነበር፡፡እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ  ዘርፎና ሰርቆ የማይበቃውን፣ ዋሽቶና አታሎ የማይታክተውን ይህ አድግን እንደ ቀትር ጉም ብን አርጎ ያጠፋልን ነበር፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ የሰላማዊ ሕዝብ አንገት የሚያስቀነጡስትን የይህ አድግ ገዥዎችና ካድሬዎች እንደ ድንጋይ ሐውልት ድርቅ አድርጎ ባቆማቸው ነበር፡፡እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ የይህ አድግ ገዥዎችን እንደ ይሁዳ በፀፀት ራሳቸውን እዲሰቅሉ ባደረጋቸው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ ይህ አድግ በግፍ የጨፈጨፋቸው ዜጎች ፍትህን በተጎናፀፉ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ቢሰማንማ ኖሮ ለቃልቻ አምላኪው ፈርኦን የሚሰግዱ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ጋር የሚነጋገገሩ፣ ስቃይንና ሞትን የማይፈሩ እንደ ሙሴና እያሱ ያሉ የመንፈስም ሆነ ዓለማዊ መሪዎች በሰጠን ነበር፡፡

ስለዚህ ጳጳሳት ሆይ፡- የሰሟችሁ የመሰላችሁ ጉዶች ዶሮ ሳይጠባ ሺህ ጊዜ የሚክዷችሁ የይህ አድግ አምበሎች ወይም ዲያብሎሶች ናቸው፡፡ ይኸንንም ዶሮ ገና አንዴ ሳይጮህ የምታዩት ነው፡፡ የይህ አድግ አምበሎች ያዘዟችሁም አውግዛችሁ ተቤተ ክርስትያን ያባራራችሁቸውን ወሮ በሎች ተነገረ መለኮትና ቀኖና ውጭ ወደ ቅድስትና መቅደስ እንድትመልሱ ነው፡፡ ይኸንን ያዬ እግዚአብሔር ይታዘባል እንጅ የሚሰማን ምኑን ነው?

ዛሬም የሰሚ ያለህ! ዲያብሎስን ማመን የቀጠለው መቼ በማተቡ ይጠናል ብለን ነው?

 

የካቲት ሶስት ቀን ሁለት ሺ አስራ አምስት ዓ.ም.

 

 

 

 

 

 

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

326523168 1357697308311959 2053092809164446880 n 1
Previous Story

የነጭ ሽንኩርት የጤና ጥቅሞች

179650
Next Story

”ካህኖቻችን በአደባባይ በጥፊ ሲመቱ አይተናል. . .!” | የቅዱስ ሲኖዶስ መግለጫ | Ethiopia

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop