አያስቅም! አጭር ወግ (ከክንፉ አሰፋ) ጋዜጠኛ

በብሄራዊ ትያትር አካባቢ አንዲት አነስተኛ ምግብ ቤት ነበረች። «ገሊላ ምግብ ቤት» ትባል ነበር። በአዲስ አበባ «ቁምራ» ከመግባቱ በፊት በአካባቢው ያሉ የመንግስት ሰራተኞች በምሳ ሰዓት ይህችን ምግብ ቤት ያጨናንቋት ነበር። ቁምራን የማታውቁ ካላችሁ፤ ለጽድቅ የሚደረግ መንፈሳዊ ጾም እንዳይመስላችሁ። እድገትና ትራንስፎርሜሽኑ ያመጣው አዲስ ክስተት ነው – ቁርስ ምሳና ራት በአንድ ጊዜ የመመገብ ዘዴ። «ኑሮ በዘዴ፣ ጾም በኩዳዴ» ይባል ነበር። ይህ አባባል አሁን መኖ በዘዴ በሚል ተቀይሯል። መቼም ሁሉም ነገር በነበር እየቀረ ነው።
ጋዜጠኛ አቤል አለማየሁ በቅርቡ ባሳተመው “የአዲስ አበባ ጉዶች” የሚል መጽሃፉ ላይ ስለዚህች ታሪካዊ ምግብ ቤትም ትንሽ ብሏል። የምግብ ቤትዋ ባለቤት “ገሊላ ምግብ ቤት” የሚለው ጽሁፍ በከፊል አጥፍተውታል። አሁን ምግብ ቤት የሚለው ተነስቶ “ገሊላ” የሚለው ብቻ ነው የቀረው። ጉዳዩ በህግ እንዳያስጠይቃቸውም ይመስላል ጽሁፉ ላይ ነጭ ቀለም ነው የደፉበት። የምግብ ቤቷ ትራንስፎርሜሽን መሆኑ ነው። የዚህ ትራንስፎርሜሽን ትርጉም የገባቸውም ሆነ ያልገባቸው ተስተናጋጆች ወደ ገሊላ (ምግብ ቤት) ጎራ ማለታቸው አልቀረም። የዚህች ቤት አዲሶቹ ደንበኞች በአነስተኛና ጥቃቅን የተደራጁ ወጣቶች ናቸው። እዚያ ሲገቡ ሰልፍ ይጠብቃቸዋል። ይህች ስፍራ ስፋትዋ ለምግብ ቤት በቂ ነበር። ለቀን አልጋ አገልግሎት ግን ትንሽ ስለጠበበች ነው ሰልፍ ሊከሰት ያቻለው። ተራ የደረሳቸው በመጀመርያ ሜኑ ይቀርብላቸዋል። የቀድሞው የምግብ ሜኑ በወይዛዝርት ፎቶ ተቀይሯል።….
ይህ ዘርፍ አሁን ከኮብልስቶንም የበለጠ አዋጭ እየሆነ በመምጣቱ፤ ምግብ ቤቶች የአገልግሎት አይነታቸውንና የሜኑ ደብተራቸውን እየቀየሩት መሆናቸው እውነት ነው።
የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ወሬ መሰማት ከተጀመረ ትንሽ ዘገየ። ይህ አዋጅ ከተሰማ በኋላ የእርሻ፣ የኢንዱስትሪና የሃይል አቅርቦቶች በሙሉ በአስር እጥፍ ነው ያደጉት። እድገታቸው ታዲያ ወደላይ ሳይሆን እንደባህር ዛፍ ወደታች ነው። በእርግጥ የለውጥ ምልክቶች በሀገሪቱ እየታዩ ነው ከተባለ የዝሙት ኢንደስትሪው በደንብ ለመጠቀስ ይችላል። ይህ ዘርፍ በተለይ ከአረብ ሃገር የበርካታ ቱሪስቶች መስህብ ሆኗል። በዚያን ሰሞን አንድ በአዲስ አበባ የሚታተም ጋዜጣ ድንግልና በአስር ሺህ ብር እንደሚሸጥ አስነብቦን ነበር። አንዲት ደናግል ለዚህ ጸያፍ ነገር ስትዳረግ ድህነትን ብቻ አይደለም የምትሰናበተው። የማንነትዋ መግለጫ የሆነው የሞራል ጉዳይም አብሮ ይሄዳል።
የአገልግሎት ክፍያው የሚከናወነው በዶላር መሆኑ ደግሞ በዚህ ዘርፍ ላይ የግሽበት ችግር አይደርስበትም። ኢንደስትሪው ለሃገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ምንጭም ስለሆነ ይመስላል ከመንግስት በኩል እየተበረታታ የመጣው። የውጭ ምንዛሪ በማስገኘቱም «ልማታዊ» ተግባር ተብሏል። መንግስት ከዚህ ሴክተር ምን ያህል እንደሚጠቀም በውል ባይታወቅም አገልግሎት ሰጭዎቹ (ደላሎቹ) ግን ሃብታም እንደሆኑ ይነገራል።
ወደ ጎተራ አካባቢ በተሰራው የኮንዶሚንየም መንደር ደግሞ ሌላ ታሪክ አለ። ይህ ኮንዶ «ፌስቡክ» የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል። ለምን ፌስቡክ እንደተባለ ለማወቅ ብዙም ግዜ አይፈጅም። የቆነጃጅት ኮረዳዎች ሁሉ መሰብሰቢያ ነው። ትምህርት አቋርጠው ወይንም ከቤተሰብ ተኮራርፈው የተሰወሩ የቤት ልጆችን ለማግኘት ወላጆች ወደ ፖሊስ ጣብያ መሄድ አቁመዋል። ወደ ጎተራው «ፌስቡክ» ብቅ ካሉ የጠፉትን ሁሉ እዚያ ያገኙዋቸዋል። ባለሃብቶች እና ባለግዜዎች ወጣት ሴቶችን እየወሰዱ እዚያ እንደ እቃ ያስቀምጧቸዋል። ይህን የሚያጫውቱኝ ወዳጆቼ እየሳቁ ነበር የነገሩኝ። ነገሩ ያሳዝናል እንጂ አያስቅም!
በዚህ ልማታዊ «ቢዝነስ» ውስጥ ጨቅላዋ ማሪቱም ገብታበታለች። የማሪቱን ነገር ማንሳቱ ብቻ ሁኔታውን በደንብ ይገልጸዋል።
ይህች ጨቅላ ጉብል በወግና በማዕረግ ያደገችበትን ቀዬ ለቃ ከወጣች አመታት አልፈዋል። በሃገሬው ሹሩባ ተጎንጉኖ የነበረው ያ ዞማ ጸጉርዋ በፈረስ ጸጉር ተተክቷል። እንደምንጭ ውሃ ጥርት ብለው የነበሩት አይኖችዋ በህብረቀለማት ኩል ተበርዘዋል። በአረንጓዴ ካኪ የተሰፋላት ሽንሽን ቀሚሷ ካላይዋ ላይ ተጥሎ በዘመናዊ ሚኒ-ስከርት ተቀይሯል። ኮንጎ ጫማዋም በሂል ተለውጦ ምቾትዋን ወስዶባታል። ማሪቱ አሁን አዲስ ዓለም ውስጥ ናት። እንደ አሻንጉሊት ሁለመናዋ ሰው-ሰራሽ ሆናለች። ስምዋም ተቀይሯል። አሁን ሜሪ ናት። ማሪቱን ሜሪ ለማድረግ ደላሎቹ ችግር የለባቸውም። ዘመናዊ ልብስ እንጂ ዘመናዊ ስም ወጪ አያስወጣም። ለማሪቱ ከሜሪ ይልቅ ማርታ ወይንም መስከረም ይቀርብ ነበር። እነዚህን ሁለት እርከኖች ዘልሎ ፈረንጅኛው ላይ መሄዱ፣ ምን ያህል ፈጣን የእድገት ጎዳና ላይ መሆናችንን ያሳየናል።
እርግጥ ነው። ማሪቱ በትምህርቷ ገፍታ ሰዎች የደረሱበት ለመድረስ ችሎታውና ፍላጎቱ እንጂ አቅሙ አልነበራትም። እድሜዋ ለአቅመ ሄዋን እንደደረሰ እንደከተሜ እኩዮችዋ ለኮሌጅ ትምህርት አልታደለችም። ወላጆችዋ ብዙም ቅሪት የላቸውም። ለችግር ግዜ አስቀምጠዋት የነበረችውን ገንዘብ ለ«ህዳሴው ግድብ» መዋጮና ቦንድ መግዣ አውለዋት በተስፋ መኖር ጀምረዋል። አዎ ተስፋቸውን ሁሉ በህዳሴው ላይ አድርገዋል። ግና ተስፋ የእለት ጉርስ አይሆንም።
ሜሪ ድህነትን ለማሸነፍ ስትል የማትወደውን ስራ የመስራት ውሳኔ ላይ ደርሳለች። በውሳኔዋ እንዳትጸጸት የሚያጽናናት ነገርም አለ። «ትምህርት ምን ያደርጋል? የተማረ የት ደረሰ?» የሚለው የወላጆችዋ አባባል በእምሮዋ ውስጥ ያቃጭል ነበር። ይህንን አባባል እንደ ጥቅስ እቤትዋ ላይ ሰቅላዋለች። ከህሊና ወቀሳ ለመሸሽ ስትፈልግ ቀና እያለች ይህንን ጥቅስ ታነብና ትጽናናለች። ታላቅ ወንድምዋ የኢንጅነሪንግ ምሩቅ ነው። የዩኒቨርሲቲ ትምህርቱን እንዳጠናቀቀ ከልጅነቱ ጀምሮ ይመኝ የነበረውን ስራ ሊያገኝ አልቻለም። ይህም፣ ወላጆቹ በትምህርት እና በእውቀት ላይ ተስፋ እንዲቆርጡ አድርጓቸው ነበር። የኋላ-ኋላ ግን የስራ አጡን ጎራ ለማምለጥ አዲስ ስልት ቀየሰ። የኢህአዴግ አባልነት ፎርም ሞልቶ በጥርነፋ መያዙ ግድ ሆነበት። ከዚያም በ«አነስተኛና ጥቃቅን» ዘርፍ ተደራጅቶ ኮብልስቶን ላይ ተሰማራ። ድንጋይ ሲፈልጥና ሲሸከም ለመዋል መስፈርቱ መብዛቱ ሜሪን አምርሯታል። በመጀመሪያ የዩኒቨርሲቲ ምሩቅ መሆን፣ ከዚያ የአባልነት ፎርም መሙላት፣ ከዚያ በአነስተኛና ጥቃቅን መደራጀት፣ ከዚያ መጠርነፍ…።
በደርግ ግዜ ኑሮ መሯቸው በሱዳን ድንበር ሊጠፉ የነበሩ ወጣቶች፤ ጠረፍ ላይ ሲደርሱ አንድ መፈክር አዩ። “ትግላችን መራራ፣ ጉዟችን እሩቅ፤ ግባችን ረጅም ነው!” የሚል መፈክር። ወጣቶቹ ተስፋ ቆርጠው ጉዟቸውን አቋረጡ። ከዚያም ጫካ ገቡ ይባላል። ያሁኑ ዘመን ጫካ «ቼቺንያ» የሚባለው መንደር ነው። ሜሪም ወንድሟ ያለፈበትን ረጅም መንገድና አስቸጋሪ መስፈርቶች ማሟላት ስለሚሳናት አጭሩን መንገድ መምረጥ ነበረባት።
በተለይ ከመካከለኛው ምስራቅር የሚመጡ ቱሪስቶች፣ አየር ባየር ነጋዴዎችና ባለስልጣናትም ጎራ እያሉ የሚዝናኑባቸው ማሳጅ ቤቶች እንደአሸን ነው የፈሉት። ከታይላንድ የዝሙት እንደስትሪ የተወረሱ “ሃፒ እንዲንግ” ተግባራት የሞራል ውድቀታችን ምን ያህል እንደወረደ ያሳየናል። እንደዚህ አይነቶቹ ነውር ነገሮች ሁሉ ገቢ እስካስገኙ ድረስ አዋጭ ስራዎች ናቸው። በልማታዊው መንግስታችንም ይበረታታሉ።
ሁሉን ነገር ተነጠቀን የቀረችን አንዲት ነገር ሞራል ብቻ ነበረች። የሞራል እሴቶቻን ግን እንዴት ነው እንዲህ የራቁን? መልካም ስነ-ምግባር፣ ጨዋነት፣ ግብረ-ገብነት እና ፈሪሃ እግዚአብሄር የጠፋበት ህብረተሰብ መጨረሻው ምን ሊሆን ይችላል? ሃገር ማለት መሬት ብቻ አይደለም። ሃገር ማለት ሕዝብና አንድ ሉዓላዊ አካል ብቻም አይደለም። መልካም ስርዓት እና የሞራል እሴት የሌለው ሃገር ከማፍያ ጉረኖ የተሻለ አይሆንም።
ሌት ተቀን የምንደኖቅርበት እድገትና ትራንስፎርሜሽም የሚመጣው በመጀመርያ ሃገር ስትኖር መሆኑን መገንዘብ ይበጃል። …. የሃይማኖት አባቶችስ ይህንን እያዩ ለምን ዝም አሉ? ስራቸው ፍትሃት ማድረግ እና እና ግብር መሰብሰብ ብቻ መሆን ነበረበት? ወይንስ እነሱንም ይኸው ልማታዊ አስተሳሰብ ተጸናወታቸው?

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ስብሰባ (ፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም)

1 Comment

  1. ክንፉ አሰፋ በፃፈ ቁጥር ሳላነበው ማለፍ የማልፈልገው ውድ ልጄ ነው:: በርታልኝ:: ደክሞኝ መፃፍ ባቆምም እንደኔ ያልደከማቸውና ምናልባትም የማዩክማቸው ወጣት የነብር ጣቶች አሉ:: ፈጣሪ ይባርካችሁ:: ሁሉም ቢሞት ዛፍና ቅጠሎች ስለእናት ሀገር ይናገራሉ_ እዉነቱን ይመሰክራሉ::
    ክንፉ ስለእዉነት ብለህ ይህችን ፅሁፍ ለመፄፍ ያወጣሃትን ሁለንተናዊ ወጪ አዉቃታለሁና ጌታ ይባርክህ_ የኔንም የዚችን ‘ኮሜንት’ የጊዜና የገንዘብ ወጪ ጭምር:: ይሁን:: ለበጎ ነው::

Comments are closed.

Share