የ 91 ሚሊዮን ህዝብን ድምፅ ያፈነው መንግስት! (ከገብርሃልሁ ተሰፋዬ)

እኔ እንኳን ብዙም ፀሐፊ ባልሆንም አንድ ወንድማችን የኢሳት የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ላይ በመገኘት አጠር ባለ ሁኔታ አፍሪካ ውስጥ ስላለው የነፃ ሚድያ ስርጭት የሰጠው አጭር ተጨባጭ ገለፃ ስላስደሰተኝ እኔ ደግሞ ለምን በፅሑፍ መለክ በአጭሩ ለአምባብያን አላቀርበውም ብዬ ነው ይሄን ፁሑፍ ለመፃፍ የተነሳሳውት:: በዚ ፅሑፌ ላይ የተወሰኑ የአፍሪካ አገራትን የነፃ ሚድያ ሽፋናችውን ለማየት የምሞክር ሲሆን ብዙውን መረጃም የወሰድኩት ከዊኪፒድያ ዌብ ሳይት ነው::

በመጀመሪያ ኢትዮጲያን እንመለከት፣ ኢትዮጲያ ከአፍሪካ በህዝብ ብዛት በሁለተኛ ደረጃ የምትገኝ ስትሆን የነፃ ሚድያ ስርጭት በምንመለከትበት ጊዜ የመጨረሻዎቹን ደረጃ ትይዛለች:: ለዚህ ምስክር በ 2013 እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር የወጣው የአለም የነፃ ሚድያ ሰንጠረዥ ነው:: ኢትዮጲያ አንድ ዋና የቴሌቨዥን ፕሮግራም ማሰራጫ ጣቢያ ሲኖራት በዛ ውስጥም ኢቲቪ ይሰራጫል የተቀሩት አዲስ ቲቪ ፣ ቲቪ ኦሮሚያ እና ድሬ ቲቪ ግን በክልል የተወሰኑ ናችው:: ሌላው ከአስር ብዙም የማይበልጡ የግል እና የመንግስት የሆኑ አጭር ሞገድ እና የኤኤም ራዲዮ ማሰራጫ ጣቢያወች አሉዋት::ነገር ግን ሁሉም የቴሌቨዥን እና የራድዮ ስርጭቶች በመንግስት ቁጥጥር ስር ናችው:: በግለሰብ ደረጃ ድምፃችውን ለማሰማት የሚሞክሩትን ደግሞ የእስር ቤት እራት ይሆናሉ:: በተቃራኒው እዚው ጎሮቤት ሀገር ኬንያን እንመልከት ፣ ኬንያ የኢትዮጵያን ግማሽ ያህል ህዝብ ሲኖራት የሚያስገርመው ግን ከ አስራ አምስት በላይ የግልና የመንግስት የቴሌቭዥን ፕሮግራም ማሰራጫ ጣቢያወች ሲኖሯት ከ ዘጠና በላይ የኤፍኤም ማሰራጫ ጣቢያወች አሉዋት::ቁጥራችውም በጣም ብዙ የሆኑ ጋዜጣና መፅሔቶች በየእለቱ ይታተማሉ::የመንግስት ሚድያወች በተወሰነ መልኩ የመንግስት ተፅህኖ ሲኖርባችው ሁሉም የግለሰብ ሚድያወች ግን ከመንግስት ገለልተኛ ናችው::በጣም ብዙ የሚሆኑ የግለሰብ ማሰራጫ ጣቢያወች ስራ ለመጀመር ዝግጅት ላይ ናችው:: ታዲያ ጎበዝ ይሄ ምን ያህል ድምፃችን እንደታፊነ አያሳይም? አዎ ያሳያል እስቲ ሌላዋን ጎሮቤት ሀገር ሱማሊያን እንመልከት፣ ሁላችሁም እንደምታቁት ሱማሊያ ከአያ አመታት በላይ የእርስ በእርስ ጦርነት ያሳለፈቸ ሀገር ስትሆን የውስጣዊ ችግሮቿ አሁንም እንደቀጠሉ ናችው:: ሆኖም ግን አንድ የመንግስት የቴሌቭዥን ፕሮግራም ማሰራጫ ጣቢያ ሲኖራችው(SNTV) ሌላ ደግም የሱማሊያ መሬት(SLNTV) የተባለ ክልላዊ ማሰራጫ ጣቢያ አላችው:: ከነዚህም በተጨማሪ ሁለት የግለሰብ ማሰራጫ ጣቢያወች ምስራቃዊ የቴሌቭዥን ኔትወርክ(ETNTV) እና የሱማሊያ የመገናኛ አንድነት(SBCTV) በ ቦሳሶ ይገኛሉ::መቀመጫችው ከሱምሊያ ውጪ የሆኑ ብዙ የማሰራጫ ጣቢያወችም አሉዋችው::

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከዛሬ ጀመሮ የዞን ዘጠኝ ኩሩ አባል መሆኔን አረጋግጣለሁ - ግርማ ካሳ

የድምፅ ስርጭትን በተመለከተ የተወሰኑ ማሰራጫ ጣቢያወች አላችው:: መገንዘብ ያለብን የሱማሊያ የህዝብ ብዛት የኢቶጲያን አንድ ስምንተኛ ሆኖ ሳለ እና ያለመንግስት ለብዙ አመት ስትመራ የነበረች ሀገር ይህን ያህል ድምፃችውን የሚያሰሙበት የማሰራጫ ጣቢያወች መኖራችው ምን ያህል የኢህአዴግ መንግስት ህዝባችንን ጨቁኖ እየገዛ እንዳለ ያሳየናል:: መቼስ ጎሮቤት ሀገር ስላቹ ኢትዮጲያን ከጅቡቲ እና ከኤርትራ ጋር አወዳድራት አትሉኝም! ምክንያቱም ኢትዮጲያ የጅቡቲን ዘጠና እጥፍ ስለምታክል ማነፃፅሩ ተገቢ አይመስለኝም ሌላው ኤርትራም ብትሆን ከኢትዮጲያ ጋር ስትወዳደር በጣም ትንሽ እና ወጣት አገር ናት::እስቲ ደግሞ ወደ ምዖራብ አፍሪካ እንሂድና ጋናን እንመልከት፣ ጋና በሚድያ ነፃነት የምትታወቅ ስትሆን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ 2007 ብቻ ሰባት የሚሆኑ የቴሌቨዥን ፕሮግራም ማሰራጫ እና ከ 85 በላይ የ ኤፍ ኤም እና 3 የ አጭር ሞገድ ማሰራጫ ጣቢያዎች ነበሩዋት::ከ 135 በላይ የተለያዩ ጋዜጦች ሲኖሩ 9ኙ በየቀኑ የሚታተሙ ናችው:: 16 ያህሉ ደግሞ ከመንግስት ገለልተኛ ሆነው የሚታተሙ ናችው::እንግዲህ ይሄ ሁሉ በነጮቹ አቆጣጠር በ 2007 የነበረ ነው:: አሁን ምን ያህል ደርሱዋል የሚለው ጥያቄ አስፈላጊ አይመስለኝም ምክንያቱም የኢትዮጲያን አንድ አራተኛ የሚያህል ህዝብ ይዘው ይህን ያህል ህዝቡ ድምፁን የሚያሰማበት ማሰራጫ ጣቢያወች መኖሩ በራሱ በጣም የሚያስደንቅ ነው::እንደዚህ እያልን የተለያዩ የአፍሪካ አገራትን መቃኘት ይቻላል ግን ለዛሬ እዚ ላይ ይብቃን::
ነፃ ሚድያ ስንል የህዝብ የመናገር መብት ሲከበር ማለት ነው:: የህዝብን ድምፅ ያላከበረ መንግስት ደግሞ ህዝብን እንደናቀና ሀገርን እንዳላከበረ ይቆጠራል:: የትኛውም አይነት መንግስት የህዝብን ድምፅ አፍኖ ዘላለም የገዛ የለም :: የትኛውም አይነት አመለካከት ያለው ሰው ይሄን የሚገነዘብ ይመስለኛል፣ አልገነዘብም የሚለው ደግሞ ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ ለጥቅሙ የሚሮጥ ነው:: ህዝባችን በሀገሩ ባዳ ሆኖ እየኖረ ያለ ሲሆን በአገራች ባዳ አንሆንም የመናገር መብታችንን እናስከብራለን ያሉት እንደ ጋዜጠኛ አንዱአለም አራጌ ፣ እርዮት አለሙ፣ እስክንድር ነጋ የመሳሰሉት በእስር ቤት ባላጠፉት ጥፋት ተወርውረው ይገኛሉ:: እነሱ እንደኢትዮጲያዊ የራሳችውን አስተዋጾ ያበረከቱ ሲሆን ሁላችንም ለመጭው ትውልድ በማሰብ በአንድነት ለመብታችን መቆም አለብን!
እኔ የምለው ሁላችንም በልባችን መናገር ውይም መግለፅ የምንፈልገው ነገር ብዙ እያለ በዚ አፋኝ መንግስት አማካኝነት ታምቆ መኖር ተገቢ አይደለም ኢትዮጲያ የአፍሪካ እናት የሆነች ሀገር ሆና ሳለ ለዚ ዋላ መቅረት ያበቃን የወያኔ አመራር ስለሆነ ይሄን ስረአት ለመስበር ሁላችንም የበኩላችንን አስተዋጾ ማድረግ አለብን:: ባጠቃላይ እዚ ፅሁፍ ውስጥ ለመግለፅ የፈለኩት ምን ያህል ሌላው የአፍሪካ ሀገራት በነፃው ሚድያ ዘርፍ ጥለውን እንደተራመዱ እና ከዚያም ተምረን በአንድነት የህዝባችንን የታመቀ ድምፅ የምናሰማበትን ነገር ለመፍጠር ወይም ያሉትን ለማበረታታት እንዲረዳን ነው::
ፍቅር ለኢትዮጲያ ህዝብ!!!!

ተጨማሪ ያንብቡ:  በኢትዮጵያ “የብሄር ፖለቲካ” ምንጩ፤ ያስከተለው ጉዳትና መፍትሄዉ (በዓቢዩ ብርሌ (ጌራ)
Share