“አማራን ማዳን ኢትዮጵያን ማዳን ነው” በሚል ሰብሳቢ መርህ አለም አቀፍ የአማረ ህብረት አቀፍ ጉባኤ እንዲሳተፋ ተጠርተዋል

ቀን–መስከረም 1ቀን 2019 ዓ.ም
ቁጥር—ዓአህ/08/001
ለተወደዱ—–ባሉበት
ጉዳዩ፤ አስቸኳይ ጉባኤ
በአማራው ሕዝብ ላይ የሚካሄደው ግፍና በደል እየተባባሰ ሂዷል። የዚህን ታላቅ ሕዝብ ህልውና አስጠብቆ ሕዝቡን ከእርስ በእርስ እልቂት እና እናት አገራችንን ከመበታተን ለመታደግ፤ “ አማራን ማዳን ኢትዮጵያን ማዳን ነው” በሚል ሰብሳቢ መርህ አለም አቀፍ የአማረ ህብረት ባዘጋጀው ሁሉን አቀፍ ጉባኤ እንዲሳተፋ ይህን የአገር አድን ጥሪ ለእርሰዎም ልከናል።
የሁለት ቀኑ ጉባኤ ዋና ዓላማ አዲስ ድርጅት ለመመስረት አይደለም። የአማራውን ሕዝብ በአንድ ጃንጥላ ስር በማስተባበር በኢኮኖሚያዊ፤ ማህበረሰባዊ፤ ፓለቲካዊ፤ ዲፕሎማሲያዊና በተዛመዱ ጉዳዮች ላይ ተመካክሮና ተናቦ፤ ውጤት የሚያስገኙ ተግባሮችን በተቀናጀና ስልት ባለው መልክ ስኬታማ ለማድረግ ነው። “ድር. ቢያብር አንበሳ ያስር” እንዲሉ ተባብሮ ከመስራት ውጭ ሌላ አማራጭ የለም።
ልዩ ልዩ የአማራ ማህበረሰባዊ፤ ፖለቲካዊ፤ መንፈሳዊና ሌሎች ድርጅቶች፤ በአዲስ አብሮና ተባብሮ የመስራት መንፈስ፤ አደረጃጀትና መመካከር ያሉትን ድርጅቶች ማጠናከር፤ አብረውና ተደጋግፈው እንዲሰሩ አንድ ወጥ የሆነ ማእከላዊነት እንዲመሰረትና በአማራው ላይ እየተካሄደ ያለውን ግፍና በደል፤ የፈጠራና የሃስት ትርክት ከሚጠቀሙ ኃይሎች የሚደርስበትን ድርብና ድርብርብ ጭቆና በአጭር ጊዜ ውስጥ መቋቋም ወሳኝ ነው። ለዚህም፤ አግባብ ባለው የአቅጣጫና የተግባር ፍኖተ ካርታ ላይ ስምምነት መደረግ አለበት።
በአማራው ላይ የተከሰተውን ችግር ለመወጣት የምንችለው በጋራ ስንሰራ ብቻ ነው። ለዚህም፤ አንድ አለም አቀፍ አስተባባሪ አካል መመስረቱ ከፍተኛ ጠቀሜታ ስላለው እርሰዎም ሆኑ ድርጅቶዎ በዚህ ጉባኤ ላይ በመገኘት ለአማራው ወገናችን ተቆርቋሪነተወን እንዲሳዩና ወገኖቻችን የማዳን ታሪካዊ ግዴታዎትን እንዲወጡ በማክበር ጠርተነወታል።
ከስላምታ ጋር
ዶ/ር አምባቸው ወረታ
የአለም ዓቀፍ አማራ ህብረት እስተባባሪ ሊቀመንበር
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ!
የስብስባ ቀን– መስከረም 14 እና 15
ቦታው- 2601 Evarts St. N.E Washington DC, Zip code 20018

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአፍሪካ መሪዎች ለምን ቶሎ ይሞታሉ? - በ6 ዓመት ውስጥ 10 የአፍሪካ መሪዎች ሞተዋል

1 Comment

  1. እኔ እንኳን አማራን ማዳን ኢትዮጵያን ማዳን ነው በሚለው ሃሳብ አልስማማም። አማራን ለማዳን ቢባል ይሻል ነበር። ሃሳባቹሁ ግን ይገባኛል። አማራው የዘር ማጥፋት በደል በወያኔና በመሰል ተለጣፊ ድርጅቶች የደረሰበት ሃገር ሃገር እያለ ቤቱን ሳይጠብቅ በመቅረቱ በየሜዳው በቋንጭራና በጥይት እየተደበደብ ሲሞት አይተናል። ዛሬም ቢሆን ከምድሩ የሚፈናቀለው፤ መጤ እየተባለ ቤቱ የሚፈርሰው፤ በህቡዕና በግልጽ ጥቃት የሚደርስበት የአማራ ህዝብ ነው። በቅርቡ በመፈንቅለ መንግሥት ሳቢያ የተገደሉትና በየከተማው እየታፈሱ እስር ቤት የገቡት ለአማራ ህዝብ የሚቆረቆሩ ናቸው። የሃበሻው ፓለቲካ ጅል ነው። በጠራራ ጸሃይ ተጨፈኑና ላሞኛቹሁ ይላል። የዘር ፓለቲካው በጣም ሥር የሰደደ ስለሆነ መልሶ ኢትዮጵያዊነትንና ኢትዮጵያን ለማጸባረቅ ከማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። ጣሊያን፤ ሻቢያና ወያኔ አሁን ደግሞ የኦሮሞ አክራሪ ሃይሎች ድብቅ አጀንዳቸውን በእምነት ተቋሞች ላይ ሳይቀር የውሸት ወሬ በማሰራጨት ሰውን ለማጫረስ እየሰሩ ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤ/ክርስቲያን አለቅጥ የበዛ ጥቃት የደረሰባትና የሚደርስባት የእነዚህ የጥፋት ሃይሎች ሰለባ በመሆኗ ነው። ኢትዮጵያዊነትን በማስቀደሟ ነው። አማራንና የኦርቶዶክስ ቤ/ክንን ጉልበት ማዳከም ዋና ዓላማቸው ከበፊትም ነበር አሁንም ነው።
    እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ዘርና ጎሳን ወይም ቋንቋን ተገን ሳያደርጉ አስቦ መግባቱ እየከበደ ከመጣ ቆይተናል። በየወገንህ ቢሉት “የመቶ ዓመት ቆዳ ገቢያ ወቶ ቆመ” እንዲሉ ነው። ዝብርቁ የወጣ የወያኔና የሻቢያ የፓለቲካ ምሾ! ቢለቀስ አልቃሽ የጠፋበት፤ አታሞ ለዘፈን ቢመታ ዘፋኝ የሌለበት። ሁሌ ጨለማ። ሁሌ ወደ ኋላ! የሃገራችን ፓለቲካ እንደ ሃገራችን የገበጣ ጫዋታ “ቢከፋኝ ብመለስ” አይነት ነው። ትላንት መገንጠላቸውን 99% ተቀባይነት አገኘ ያሉን ኤርትራዊያን ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ ተሰባጥረው ሲኖሩ ማየት የ 30 ዓመቱ መተላለቅ የውስልትና ፓለቲካ እንደ ነበር ለማየት ይረዳል። ስንት ንብረትና ህይወት ጠፋ! በጊዜው በሥፍራው ተገኝቶ የባድመን ጦርነት የተመለከተ አንድ የውጭ ጋዜጠኛ ስለጦርነቱ ተጠይቆ ሲናገር እንዲህ ብሎ ነበር። “ጦርነቱ የሞኞች እልቂት ነው አለና ባጭሩ ሁለት መላጣ ሰዎች ለማበጠሪያ እንደሚጣሉ አይነት ነው” ብሎን ነበር። ትርፍ የለሽ የፓለቲካ ግብግብ።
    ዛሬ ኢትዮጵያን ለማፈራረስና ኦሮሚያ የምትባል ሃገር ለመመስረት ደፋ ቀና የሚለው የጠባብ ብሄርተኞች ጥርቅም በሻቢያ በሽታ የተለከፈ፤ የወያኔን መሰሪ ክፋት የተላበሰ ቡድን ነው። ግን የሌላው ቤት ሲቃጠል የእኔ ቆሞ ይቀራል ብሎ የሚያምን ይህ የቋንቋና የድንበር ሰካራም ሁሉ የሚከተሉት ጠመዝማዛ የፓለቲካ መንገድ የት እንደሚያደርሳቸው አያውቁም። ፌርማታ እንደሌለው ባቡር ዝም ብሎ መጓዝ ነው። ዋ…ትንሽ እሳት ታላቅ ጫካን ታቃጥል። እሳቱ ሁሉን ላፍ እንዳያደርግ ልብ ያለው የብሄርና የቋንቋን ፓለቲካ ረጋ ብሎ ማጤን በተገባ ነበር። የአለም በተለይም የነጩ ዓለም መሳለቂያ ሆኖ መኖር የማያሳፍራቸው ውድቆች።
    በማጠቃለያው እንደ አንድ ወገን የአማራ ህዝብ ስፍር የሌለው ግፍ ተፈጽሞበታል እየተፈጸመበትም ነው። ገና ለገና አባታቸው አርበኛ ነበር ሰው ያስተባብራሉ ተብለው በወያኔ ታፍነው ተወስደው የት እንደ ገቡ የማይታወቁ በጎንደር፤ በጎጃም በሽዋ በወሎ በሃርር ቁጥራቸው ብዙ ነው። ወያኔና ሻቢያ በአማራው ላይ ያደረሱት ግፍ መስፈሪያ የለውም። የዛሬው ከሻቢያ ጋር መተቃቀፍ ደግሞ ዘላቂነት የሌለው ሌላ የውሸት ፓለቲካ ነው። ሻቢያ ለኢትዮጵያ መልካም አስቦ አያውቅም። ግን ወያኔ በጀርባው ስለወደቀ የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው በማለት በወያኔ ላይ አፈር ለመመለስ እንጂ ሻቢያ ዛሬም ለሃገራችን ደህንነት አስጊ ቡድን ነው። ይህን ጊዜ ያሳየናል። የአማራ ህዝብ ራሱን አደራጅቶ ሌላውን አክብሮ አንገቱን ቀና አርጎ በማንም እንደ እርድ ከብት ሳይጎተት የሚኖርበትን ብልሃት መትለም አለበት። እንዲሁ በየሜዳውና በየመድረኩ አካኪ ዘራፍ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለቱ ተገቢ አይደለም። ሙያ በልብ ነው። መደራጀት፤ ለመከራ ጊዜ ራስን ማሰናዳት፤ ለተፈናቀሉ ወገኖች ከመፈናቀላቸው በፊት በተጠንቀቅ ሆኖ አለኝታ መሆን ነው። ሌላው ሁሉ ቡራ ከረዮ ትርፉ ለጠላት መሳለቂያ መሆን ብቻ ነው!ስብሰባችሁ የተሳካ እንዲሆን እመኛለሁ።

Comments are closed.

Share