በከፍተኛ ሌብነትና ሰብዓዊ መብት ጥሰት የተጠረጠሩ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር የማዋሉ ስራ መጠናከር የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስትና ህዝብ ፍላጎት ቢሆንም በሙስና እና የሰብኣዊ መብቶች ጥሰት ስም የትግራይን ህዝብ ለማንበርከክ ጥረት እያደረገ ነው ሲሉ የትግራይ ክልል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል አስታወቁ። ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል ይህንን ያስታወቁት ዛሬ ማለዳ ለክልሉ መገናኛ ብዙሃን በትግርኛ በሰጡት መግለጫ ነው።
“መንግስት በሙስና እና የሰብኣዊ መብቶች ጥሰት የጀመረው እንቅስቃሴ አቅጣጫውን ስቷል።” ያሉት ደብረፅዮን በድርጊቱን “የውጪ እጅ ጣልቃ ገብነት እንዳለበት እናምናለን – ስለሆነም አንቀበለው” ብለዋል። በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ማይክ ሰሞኑን መቀሌ ድረስ በመሄድ ከክልሉ ባለስልጣናት ጋር መምከራቸው ተሰምቷል።
በደህንነቱ ሃላፊ በአቶ ገታቸው አሰፋ፣ በሜ/ጀነራል ክንፈ ዳኘው እና በሜ/ጀነራል ተክለብርሃን ወልደ አረጋይ ላይ ያነጠጠረው የምርመራ ውጤት በም እራብያውያን ዲፕሎማቶች ዘንድ እንደደረሰም ይነገራል። የኢትዮጵያ መንግስት በጀመረው መጠነ ሰፊ የወንጀል ምርመራ ሂደት ውስጥ የአሜሪካው የምርመራ ተቋም፣ አፍ. ቢ. አይ. ተሳትፎበታል። የአምባሳደር ማይክ የመቀሌ ጉዞ ከተጠርጣሪዎቹ ጋር እንደሚያያዝ አንዳንድ ምንጮች ይተቁማሉ። መቀሌ ተጠርጣሪዎቹን አሳልፋ የማትሰጥ ከሆነ ችግሩ የከፋ እንደሚሆን በርካታ አስተያየት ሰጪዎች ይናገራል::
“በቁጥጥር ስር የማዋል ስራው አፈጻጸም የህግ ልእልናን በሚያስከብር መልኩ መከናወን አበት:: የትግራይ ህዝብ ለህግ ልእልና መረጋገጥ ከሌሎች አጋሮቹ ጋር ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈለና ጽኑ አቋም ያለው ነው። የህግ ልእልና ካልተረጋገጠ ግጭት ይሰፍናል” ያሉት ዶክተር ደብረጽዮን፣ “የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ ሌብነትና የሰብአዊ መብት ጥሰት ፈጽመዋል ብሎ የጠረጠራቸው አካላትን በቁጥጥር ስር ለማዋል በሜቴክና በብሄራዊ መረጃና ደህንነት መስሪያ ቤቶች የጀመረውን ስራ አጠናክሮ በሁሉም ተቋማት ሊቀጥልበት ይገባል” ብለዋል።
“የህግ ልእልና የማስከበር ስራው በተወሰኑ ተቋማት መታጠር የለበትም;; ጥፋት ፈጽመዋል የተባሉትን አካላት በቁጥጥር ስር የማዋል ስራ የህግ ልእልናን የሚያረጋግጥ እንጂ የፖሊቲካ መጠቀሚያና ቁማር ሊሆን አይገባም::” ብለዋል::
“ችግር ያለበት ሰው መጠየቅ አለበት:: ሁሉም ነገር በመረጃ ላይ መመስረት አለበት:: ቅጣቱም ሌሎችን የሚያስተምር መሆን አለበት” ሲሉ በመግለጫቸው ላይ የገለጹት ዶ/ር ደብረጺዮን በጥፋት የተጠረጠሩ አካላትን በቁጥጥር ስር የማዋሉ ስራ ግልጽና ከአድልዎ የጸዳ መሆን እንዳለበትና ወደ አንድ ወገን ያዘነበለ እንዳይሆን በጥንቃቄ ሊሰራ ይገባዋል ሲሉ አሳስበዋል::
“በቁጥጥር ስር እየዋሉ ያሉት አካላት በመገናኛ ብዙኃን ጥፋተኛና ወንጀለኛ ተደርገው እየቀረቡ መሆኑ የህግ ልእልና ጉዳዮችን ለማጣራትና ለመፍረድ የተቋቋሙትን ፍርድ ቤቶችና የፖሊስ ተቋማት ተግባር ያለአግባብ እየሰሩ መሆናቸውን ያሳያል” ያሉት ዶ/ሩ “ይሔም ፍትህን ከማስከበር እሳቤ ጋር የሚጣረስና የተጠርጣሪዎችን ሰብዓዊ መብት የሚጋፋ ነው:: አፈጻጸሙ ህግና ፖለቲካን በማቀላቀል ሳይሆን ሁለቱንም በመለያየት መሆን አለበት” ሲሉ አስጠንቅቀዋል::
ደብረፅዮን ከሳምንት በፊት በክልሉ የመሸጉ ተጠርጣሪ ወንጀለኞችን ለፌደራል መንግስት አሳልፈው እንደሚሰጡ መናገራቸው የሚታወስ ነው። አሁን ደግሞ ኢሕአዴታ በግምገማ ካስቀመጠው መርህ ውጪ እየተሠራ ነው ማለታቸው ብዙዎችን ግራ ቢያጋባም – ያለፈው ስርዓት ተጠቃሚ የነበሩ የትግራይ ብሎገሮች ተጽእኖ እንደፈጠሩባቸው ይሰማል።
በዚህ ጉዳይ ለዘ-ሐበሻ አስተያየቱን የሰጠው የኢኤም ኤፍ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ክንፉ አሰፋ “እየጠበቀ የመጣው የአስመራ ወዳጅነትም ህወሃቶች ላይ ከፍተኛ ስጋት እንደፈጠረ በግልጽ ይታያል። ደብረጽዮን ስለ ውጪ እጅ ጣልቃ ገብነት እየተናገሩ ያሉት፣ የዶ/ር ዐብይ አስተዳደር በነዚህ ሁለት ሃገራት ተጽዕኖ ውስጥ ገብቷል ለማለት ይመስላል።” ካለ በኋላ “መንግስት በትግራይ ሕዝብ ውስጥ የተሸሸጉ ተጠርጣሪዎችን ወደ ሕግ የማቅረብ ግዴታ አለበት። ይህ የውጪ ሃይሎች ፍላጎት ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ጥያቄ ነው።” ብሏል::
ክንፉ አክሉም “የክልሉ ባለስልጣናት የህግ የበላይነት እንዲከበርና በህግ ጠለላ የሚገኙ ተጠርጣሪዎች መብታቸው እንዲጠበቅ ማድረግ እንጂ አሳልፌ አልሰጥም ማለት ዋጋ ያስከፍላል። ድርጊቱ ፌደራል መንግስት በሚወስደው እርምጃ መላው የትግራይ ሕዝብን ተጠቂ ለማድረግ የታለመ እቅድ ይመስላል።” ካለ በኋላ “የህወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ በቅርቡ በሰጡት ቃለ-ምልልስ ጦርነት ላይ ነን ማለታቸው የሚታወስ ነው። የህወሃት ሰዎች ሁለት እና ሶስት ወንጀለኞችን አሳልፈን ከምንሰጥ እንዋጋለን ያሉ ይመስላል። ይህም በምስኪኑ የትግራይ ሕዝብ ስም ከኢትዮጵያ ጋር በውስጥ ጦርነት ማወጅ ያስመስላል” ሲል አስረድቷል::
https://www.youtube.com/watch?v=pXfWMmUXIks