Sport: ዋሊያዎቹ ለቀጣዩ ጨዋታ ካለፈው ሽንፈት ምን ይማራሉ?

ከይርጋ አበበ
ቡድኑ ሊያስተካክል የሚገባው
በሜዳውና በደጋፊው ፊት የተጫወተው ብሄራዊ ቡድናችን በእንግዳው ቡድን ሁለት ለአንድ መሸነፉ ይታወቃል። የጨዋታ የበላይነቱን በውጤት የበላይነት እንዳይደግመው ምክንያቱ ምንድን ነው? ብለን መጠየቅ ይኖርብናል። ለዚህ ጥያቄ ደግሞ ጋዜጠኛው በእለቱ የተመለከታቸውን ድክመቶችና ስህተቶች በራሱ እይታ እንዲህ ያቀርባቸዋል።
የልምድ ማነስ
ኢትዮጵያን ለመግጠም ሃያ ሶስት አባላትን ይዞ ከአቡጃ የተነሳው የንስሮቹ ስብስብ አስራ ስምንቱን የቡድኑን አባላት ከአውሮፓ ነበር የጠራው። እነዚህ ከአውሮፓ ተጠርተው የመጡት ፕሮፌሽናል ተጫዋቾች ይዘውት የመጡት የካበተ ልምድ በዋሊያዎቹ ላይ የበላይ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል። በተለይ የተጋጣሚ ደጋፊዎች ስታዲየሙን ከአፍ እስከ ገደፉ ሞልተው እየዘመሩና እየጮሁ በእንግድነት ተጫውቶ ማሸነፍ እንዴት እንደሚቻል ልምዳቸው ሳይጠቅማቸው አልቀረም።
በመሀል ሜዳ የጨዋታ ብልጫ ተወስዶባቸውና የግብ መሪነቱ ተይዞባቸው ከመመራት ተነስተው ለማሸነፍ የቻሉትም ከልምድ የተነሳ እንጂ በጨዋታ በልጠው በመገኘት እንዳልሆነ ጨዋታውን በአካልም ሆነ በቴሌቪዥን የተመለከተ ሁሉ ሊመሰክር ይችላል።
በአንጻሩ የትልልቅ ውድድር ልምድ የሌለው ብሄራዊ ቡድናችን መሪነቱንና የሜዳ አድቫንቴጁን ሳይጠቀምበት የቀረው ከልምድ ማነስ መሆኑን ለመታዘብ ችያለሁ። በተጋጣሚ የግብ ክልል ውስጥ የተፈጠሩ የግብ ማግባት እድሎችን በአግባቡ ለመጠቀም የተቸገረው የአጥቂ መስመራችንም ሆነ በጨዋታው የመጨረሻ ደቂቃ ላይ ስህተት የሰራው የተከላካይ ክፍላችን ልምድ እንዳነሰው በጉልህ ታይቷል። ይህንን ችግር ለመቅረፍ ደግሞ አሠልጣኝ ሰውነት ቢሻው፣ የእግር ኳስ ፌዴሬሽንና የሚመለከተው አካል ሁሉ የወዳጅነት ጨዋታዎችን ለብሄራዊ ቡድናችን በማዘጋጀት ማስተካከል ይቻላል እላለሁ።
የአቀያየር ስህተት
አሠልጣኝ ሰውነት ቢሻው በመሃል ሜዳ ላይ የቼልሲውን አማካይ ተከላካይ ከጨዋታ ውጭ እንዲሆን ያደረገውን አማካያቸውን አዳነ ግርማን የቀየሩበት ክስተት ለእኔም ቢሆን ትክክለኛነቱ ሊታየኝ አልቻለም። በእርግጥ ግብ የማስቆጠር ፍላጎታቸውን ሳልረዳ ቀርቼ አልነበረም። ነገር ግን አዳነ ግርማ ሜዳ ለይ እንዲቆይ ቢደረግና አዲስ ህንጻ ቀደም ብሎ ቢገባ ኖሮ አዳነ እና ሳላሃዲን የፊት መስመር ጥምረት እንዲመሰርቱ ቢደረግ የተሻለ ነበር ብዬ አስባለሁ።
ለዚህ ደግሞ አጥቂው ሳላሃዲን ሰይድ በናይጄሪያ ተከላካዮች በቀላሉ ትኩረት ውስጥ እንዲገባ የተደረገው ከጎኑ የፊት መስመር ተጫዋች ባለመኖሩ ነው። በዚያ ላይ አዳነ ግርማ በተፈጥሮው አንድ ቦታ ላይ ብቻ ተወስኖ የሚጫወት ተጫዋች አይደለም። ለምሳሌ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ብሄራዊ ቡድናችን ከዛምቢያ አቻው ጋር ሲጫወት አዳነ ሙሉ ሜዳውን አካልሎ በመጫወት ቡድናችን ያስመዘገበውን ውጤት ማየት ይቻላል።
የጥንቃቄ ጉድለት
አሠልጣኝ ሰውነት ቢሻው መውሰድ ከሚገባቸው ርምጃዎች መካከል ተጫዋቾቻቸው ጠንቃቃና ዲሲፕሊን ያላቸው እንዲሆኑ ማድረግ አንዱ ነው። በእሁዱ ጨዋታ ላይ ወደ ሜዳ ከገቡት 14 ዋሊያዎቹ መካከል ስድስቱ የማስጠንቀቂያ ካርድ ሲመለከቱ በአንጻሩ የስቴፈን ኬሽ ስብስብ ሁለት ተጫዋቾቹ ብቻ ናቸው የቢጫ ካርድ ሊያዩ የቻሉት።
በእግር ኳስ ጨዋታ ዲሲፕሊን ዋናውን ቦታ ይይዛል። ከአንድ ወር በኋላ በናይጄሪያ በሚደረገው የመልስ ጨዋታ ዋሊያዎቹ የሚፈለገውን ውጤት እንዳያስመዘግቡ ተጫዋቾቻችን የተመለከቷቸው ቢጫ ካርዶች ተጽእኖ ይፈጥርባቸዋል። ምክንያቱም ልጆቹ ከተጽእኖ ነጻ ሆነው እንዳይጫወቱ ሁለተኛ ካርድ የመመልከት ስጋት ያድርባቸዋልና።
ካሁን በፊትም ቢሆን ከማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር በነበረብን የምድባችን የመጨረሻ ጨዋታ የብሄራዊ ቡድናችን ቁጥር አንድ ጀማል ጣሰው፣ ተከላካዩ አይናለም ሀይሌና አማካዩ አዲስ ህንጻ ወደ ኮንጎ ብራዛቢል ያልተጓዙት በተከታታይ የተመለከቷቸው ሁለት ቢጫ ካርዶቻቸው ስለከለከሏቸው ነበር።
ስለዚህ ለቀጣዩ ጨዋታ ብቻ ሳይሆን ለወደፊቱ ጉዟችንም ቢሆን ተጫዋቾቻችን ሜዳ ላይ የሚያሳዩት ዲሲፕሊን ወሳኝነት እንዳለው መታወቅ ይኖርበታል።
ዳኝነት ጉልህ ስህተት
ዳኞች በእግር ኳስ ጨዋታ ላይ ያላቸው ተፅእኖ ቀላል አይደለም። የሚያስተላልፏቸው ውሳኔዎች በጨዋታው እና በውጤቱ ላይ ያለው ተጽእኖ ከፍተኛ ነው። በአሉታዊ መልኩ ለማየት ስንሞክር በተለያዩ ጊዜያት እነዚሁ ዳኞች ሆን ብለውም ይሁን ሳያውቁት ተደጋጋሚ ስህተቶችን በመፍጠር የስፖርት ቤተሰቡን ሲያወዛግቡ ይገኛሉ።
ባሳለፍነው እሁድ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንና የናይጄሪያ አቻው ያካሄዱትን ጨዋታ በመሀል ደኝነት የመሩት ካሜሩናዊ ዳኛም በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ላይ የተለያዩ ስህተቶችን እንደፈጸሙ የተለያዩ የስፖርት ቤተሰቦች ሲናገሩ ይሰማል። የእለቱ ዋና ዳኛ ስህተት የበዛባቸው ውሳኔዎችን ሲያስተላልፉ ተስተውሏል።
በዳኝነት ስህተት ምክንያት በዓለማችን ላይ በርካታ ጨዋታዎች ውጤታቸው ተለውጧል። ለምሳሌ አርጄንቲና ከእንግሊዝ ጋር እኤአ 1986 ባደረገችው የዓለም ዋንጫ ጨዋታ ላይ አርጄን ቲናዊው ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና እንግሊዝ ላይ በእጁ ያስቆጠራትን ግብ ዳኛው አጽድቀዋታል። እንግሊዝም በታሪካዊ ተቀናቃኟ ተሸንፋ በሩብ ፍጻሜው ከዓለም ዋንጫ ውጭ ሆናለች።
የ2000 እኤአ የአፍሪካ ዋንጫን በጣምራ ያዘጋጁት ናይጄሪያና ካሜሩን ነበሩ። ለ120ደቂቃ የፈጀው የዋንጫ ፍፃሜ ጨዋታ ሁለት እኩል በመጠናቀቁ አሸናፊውን ለመለየት ወደ መለያ ምቶች ገብተዋል። ከመለያ ምቶቹ መካከል የናይጄሪያው አጥቂ ኢማኑኤል ኢኪፔባ የመታት ኳስ የግቡን መስመር ብታልፍም ዳኛው ግብ አይደለችም ሲሉ መሰከሩ። ናይጄሪያም ዋንጫውን ለካሜሩን አሳልፋ ሰጠች።
ክሮሽያና አውስትራሊያ፣ ጀርመንና እንግሊዝ፣ ቡርኪናፋሶና ጋና እንዲሁም ሌሎችም በዚህ በዳኝነት ስህተት ምክንያት አንዳቸው ለሌላኛቸው ውጤታቸውን አሳልፈው ለመስጠት መገደዳቸውን መጥቀስ ይቻላል።
በመጨረሻም ልጆቻችን ላሳያችሁት ተጋድሎና ላገኛችሁት ውጤት ሀገራችሁና ሕዝባችሁ ይኮሩባችኋል። ጨዋታው ደግሞ ገና 90 ደቂቃ የሚቀረው ስለሆነ ያሉባችሁን ስህተቶች አርማችሁ ከዚህ የተሻለ ውጤት እንድታመጡ ተጨማሪ አደራ ሀገራችሁ ትሰጣችኋለች።
መልካም ጊዜ ለእግር ኳሳችን !!!!

ተጨማሪ ያንብቡ:  6 ቅን ጥያቄዎች ለአውራምባው ዳዊት ከበደ
Share