ይቺ ባንዲራ! – ከተመስገን ደሳለኝ (ጋዜጠኛ)

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ
የዘንድሮው የዘ-ሐበሻ አንባቢዎች ምርጥ ጋዜጠኛ አሸናፊ ነው።
‹‹ተከብረሽ የኖርሽው በአባቶቻችን ደም እናት ኢትዮጵያ የደፈረሽ ይውደም›› ማን ነበር ያቀነቀነው? …ብቻ ማንም ይሁን ማን፤ እኔም እደግመዋለሁ፡- ሀገሬን የደፈረ ይውደም!! …እነሆ ከፉከራው ወደ አጀንዳችን እንለፍ፡፡

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን፣ በሚቀጥለው ዓመት በብራዚል በሚካሄደው የዓለም የእግር ኳስ ዋንጫ ለመሳተፍ፣ ከናይጄሪያ ጋር የደርሶ መልስ ግጥሚያ ብቻ ቀርቶታል፡፡ በዛሬው ዕለትም የመጀመሪያውን ጨዋታ በአዲስ አበባ ያደርጋል፡፡ በዚህ ፅሁፍ የማነሳው ሃሳብም፣ ስለጨዋታው ሳይሆን፣ ጨዋታውን የሚያደምቀው ሰንደቅ-ዓላማን (ባንዲራን) በተመለከተ ይሆናል፡፡

ይቺ ባንዲራ!

ኢህአዴግ ከቀድሞ ጨቋኝ ገዥዎች የሚለየበት በርካታ መልክ ቢኖረውም፣ ዋናው ካነበረው ፌደራሊዝም ጋር ተያይዞ ‹በሀገር አንድነት ላይ ዳተኛ ነው› መባሉ እና የቀድሞ ሊቀ-መንበሩ መለስ ዜናውን ጨምሮ ጥቂት የአመራር አባላቱ ወደ ስልጣን በመጡ ዕለት ጎረቤት ሀገር ትሆን ዘንድ ከተባበሯት ኤርትራ የዘር ግንዳቸው መመዘዙም ነው፡፡ ይህም ይመስለኛል ዛሬም ድረስ እንደ ‹መናፍቅ› እንዲታዩ ያደረጋቸው፡፡

በአናቱም ሻዕቢያ ‹‹ነፃነት ወይስ ባርነት›› የሚል ፍትሐዊ ያልሆነ! ኢ-ዴሞክራሲ አማራጭ በማቅረብ ያካሄደውን ‹ህዝበ ውሳኔ› አይቶ እንዳላየ ማለፋቸው ክሱንና ጥርጣሬውን ያጠነክረዋል፤ በተለይም በወቅቱ የቀይ ባህር አፋሮች የራሳቸውን ዕድል በራሳቸው የመወሰን መብታቸውን የማስከበር ግዴታ የኢትዮጵያ መንግስት ኃላፊነት መሆኑ በግልፅ እየታወቀ፣ ኢህአዴግ ግን ይህንን ለማድረግ ፍቃደኛ አልነበረም፡፡ ሁነቱን ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም ‹‹አሰብ የማን ናት›› በሚል ርዕስ ባሳተመው መፅሀፉ፣ በጊዜው የአፋር ህዝብ መሪ ሱልጣን አሊ ሚራህ፣ ለጄነራል ጻድቃን የሚከተለውን ማለታቸውን ገልጿል፡-

‹‹በሽግግሩ ቻርተር ስብሰባ ላይ ለቀድሞው ቺፍ ኦቭ ስታፍ ሌተና ጄነራል ጻድቃን ገ/ትንሳኤ በሰጡት ቃለ-ምልልስ የቀይ ባህር አፋሮች የራሳቸውን ዕድል በራሳቸው እንዲወስኑ እንዲፈቀድላቸው ጠይቀው እንደነበረ ጄነራል አበበ በፅሁፋቸው ገልፀውታል፡፡›› (ገፅ 170)
እኚሁ ሱልጣን በተጠቀሰው ጉባኤ ላይ የኤርትራን መገንጠል የተቃወሙት ‹‹የአፋር ህዝብ ወሰን ቀይ ባህር ነው፡፡ ግመሎቻችንም እንኳን የኢትዮጵያን ባንዲራ ያውቁታል›› በማለት እንደነበረ ይታወሳል፡፡

አሰብም አንድም በወቅቱ ከኤርትራ ውጪ በራስ አስተዳደር (Autonomy) ስር መሆኗ፣ ሁለትም በእንዲህ አይነት አጋጣሚ ወደብን በተመለከተ ዓለም አቀፍ ህግ ኤርትራ ‹‹ምፅዋ››ን መጠቀም እስከቻለች ድረስ፣ ኢትዮጵያ ‹‹አሰብ››ን የማግኘት መብት እንደሚኖራት መደገፉ ቸል ተብሎ ሁለቱንም ወደቦች እንድትወስድ መፈቀዱ ለስርዓቱ ኤጴስ ቆጶሳት የ‹ሀገር ፍቅር› መፈተኛ ሆኗል (በነገራችን ላይ ኤርትራ፣ ከኢትዮጵያ መገንጠሏን ባበሰረው የሰኔ 1983ቱ ‹‹የሰላም ጉባኤ›› ከኢህአዴግ፣ ኦነግና በወቅቱ ከነበሩ ተቃዋሚዎች በተጨማሪ ኢሳያስ አፈወርቂ በታዛቢነት፣ ፕ/ር አስራት ወልደየስ ደግሞ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲን ወክለው ተገኝተው ነበር፡፡ እናም ፕሮፌሰሩ አሰብ የኢትዮጵያ መሆኗን ታሪክንና የዓለም አቀፍ ህግን እያጣቀሱ መከራከራቸው ያበሳጨው፣ የሻዕቢያው መሪ ኢሳያስ አፈወርቂ ከመጋረጃ ጀርባ ከህወሓት ጋር የሰራውን ድራማ ቃል-በቃል እንዲህ በማለት ነበር ያፈረጠው፡-

(የኢትዮጵያ ከሕዝብ ከብሄራዊ ቡድናችን ተጫዋቾች ጋር ባሮ 90 ደቂቃ መጫወት አለበት)‹‹ታሪክና ህግ የሚሉትን ዝባዝንኬ ለትምህርት ቤት ክፍል ይተዉት፡፡ ይህ ፖለቲካዊ ጉዳይ አስቀድሞ በጦር ሜዳ የተፈታ ስለሆነ ምንም አይነት ኃይል ሊለውጠው አይችልም››) በእነዚህና በሌሎች መሰል ቁጭቶችም ላይ የመለስ ዜናዊ ‹‹ባንዲራ ጨርቅ ነው›› ግልብ ትንተና ተጨምሮ ጥርጣሬውን በማናሩ ‹ነፃ አወጣንህ› የሚሉት ህዝብ፣ በግልባጩ ‹እነዚህ ሰዎች ቅንጣት ታህል የሀገር ፍቅር የሌላቸው ገዥዎች ናቸው› ወደሚል ጠርዝ ተገፍቷል፡፡

ኢህአዴግ ስልጣን ከተቆናጠጠበት ጊዜ አንስቶ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀዩ ባንዲራ በብሄራዊ የስፖርት ውድድሮች ላይ ከቀድሞ ዘመናት በላቀ መልኩ ሲውለበለብ የሚስተዋለው ‹ባንዲራችን የሀገር አንድነትና ክብር መገለጫ ነው› የሚል የጀግኖች አባቶቹን መልዕክትና አደራ ለስርዓቱ መሪዎች ማስተላለፍ በመፈለግ ይመስለኛል፡፡ በንጉሱም ሆነ በደርግ ዘመን በተመሳሳይ የስፖርት ወድድሮች ላይ ባንዲራ በዚህ ደረጃ በደጋፊዎች ሲውለበለብ ታይቶ አይታወቅም፡፡ ምናልባት የተመልካች ብዛት ከህዝብ ቁጥር መጨመር ጋር ተያይዞ በማደጉ ነው የሚል አመክንዮ እንዳይቀርብ፣ መጫወቻ ቦታው (ካምቦሎጆው) ዛሬም ያው አንድ ለእናቱ ነው፤ በአንድ ጊዜ ማስተናገድ የሚችለው የተመልካች ቁጥር ዛሬም ተመሳሳይ ነው፡፡ የአሸናፊነቱም ነገር ቢሆን በአፄው ‹‹3ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ››፤ በመንግስቱ ኃ/ማርያም ‹‹የ15ኛው የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ›› ድል ተገኝቷል፡፡
በወቅቱ (በ1980 ዓ.ም) ቡድናችን በሜዳው ለመጀመሪያ ጊዜ ዙምባብዌን አሸንፎ ይህንን ዋንጫ ሲያነሳ ስታዲየሙ ከአፍ እስከ ገደፉ ጢቅ ብሎ ሞልቶ ነበር፡፡ ኢቲቪ የጨዋታውን ፊልም ደጋግሞ ሲያስተላለፍ እንደተስተዋለውም ከሆነ ባንዲራ የያዘ ተመልካች ብዙም አይታይም ነበር፡፡ ይህ የሆነው ግን የዚያን ዘመን ተመልካች ለባንዲራው ፍቅር ሳይኖረው ቀርቶ አይደለም፤ ይልቁንም ደርግ የቱንም ያህል ጨፍጫፊ ቢሆንም፣ በብሔራዊ ጥቅም፣ በሀገር ልዑላዊነትና ዳር ድንበርን በማስከበር ጉዳይ ላይ ባለው ጠንካራ አቋም በጠላቶቹም ሳይቀር ፍፁም ተአማኒነትን በማትረፉ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህንን ጨዋታ መንግስቱ ኃ/ማርያም የተመለከተው ካምቦሎጆ
ተገኝቶ ለብሔራዊ ቡድኑ ድጋፍ በመስጠት ጭምር ነበር፡፡ በ1998 ዓ.ም በተመሳሳይ መልኩ የኢትዮጵያ ቡድን የብሩንዲ አቻውን አሸንፎ 29ኛውን ዋንጫ ሲያነሳ፣ መለስ ዜናዊ አዲስ አበባ ስታዲየም ድረስ ሄዶ ቡድኑን ሲደግፍ አልታየም፡፡ የሚገርመው ግን ከሰውየው ህልፈት በኋላ፣ ስርዓቱ የ2005ቱን የክለቦች ዓመታዊ ወድድር ‹‹ለእግር ኳሳችን ዕድገት የለፋ›› በሚል ዓይን ባወጣ የተጭበረበረ ፕሮፓጋንዳ ‹‹መለስ ፕሪምየር ሊግ›› ብሎ መሰየሙ ነው፡፡ የተኮረኮርን ያህል የምንሰቀው ግን መለስ በሥልጣን ዘመኑ ሙሉ አንዲትም ቀን የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ጨዋታን ካምቦሎጆ በመገኘት ተመልክቶ አለማወቁ ትዝ ሲለን ነው)

ተጨማሪ ያንብቡ:  ነገረ ህወሓት: ህወሓትና ‹‹ወያኔ›› ምንና ምን ናቸው? - ጌታቸው ሺፈራው (ጋዜጠኛ)

ይቺ ባንዲራ!

በአትሌቲክሱ ዘርፍ የተቀዳጀናቸው ብሔራዊ ድሎችም በዚሁ ማዕቀፍ ውስጥ የሚጠቃለሉ ናቸው፡፡ ደራርቱ ቱሉም ሆነች ኃይሌ ገ/ስላሴ እና ቀነኒሳ በቀለ በኦሎምፒክ ውድድሮች ላይ ባሸነፉ ቁጥር ባንዲራ ለብሰው ደስታቸውን የሚገልጡበት ምክንያት ይኸው ነው፡፡ በሽልማት ስነ-ስርዓቱ ላይም (የብሔራዊ መዝሙሩ አንድምታ ምንም ይሁን ምን) ባንዲራው በክብር ተሰቅሎ ከፍ ብሎ በሚውለበለብበት ወቅት ሳግ እየተናነቃቸው በእንባ የሚታጠቡበት ምስጢርም ‹‹ጨርቅ›› ተብሎ የተገፋው ባንዲራ ባሳደረባቸው ጥልቅ ቁጭት የተነሳ ነው፡፡ መቼም ኢትዮጵያዊያን ኦሎምፒክን ሲያሸንፉ እነዚህ አትሌቶች የመጀመሪያዎቹ አለመሆናቸው ይታወቃል፤
በንጉሱ ጊዜ አበበ ቢቂላ ከአንዴም ሁለቴ፣ በደርጉም ጊዜ ማሞ ወልዴ፣ ምሩፅ ይፍጠር እና ሌሎችም አትሌቶች የክብሩ ተቋዳሽ ነበሩ፡፡ ግና! እንዲህ እንደ ዛሬው ዘመን ባንዲራ ይዘው፣ ባንዲራ ለብሰው ሲዘሉ ሲቦርቁ አልተስተዋሉም፤ በህዝብ መዝሙር ታጅቦ ሲሰቀልም በቁጭት አላለቀሱም፤ ምክንያቱም መርቆ የሸኛቸው መንግስት የእነርሱን ያህል ለባንዲራው ክብር እንዳለው ያውቃሉና የሚያንገበግባቸው ጉዳይ አልነበረም፡፡

ከ1983 ዓ.ም ወዲህ ብቅ ያሉት ብርቱ አትሌቶች ግን አገዛዙ የናቀውን፣ አገዛዙ ያጣጣለውን፣ አገዛዙ ክብር የነሳውን… ባንዲራ በቁጭት ሳግ እየተናነቃቸው ከፍ አድርገው አውለብልበውታል፤ በቀለማቱ ውስጥም የማንነት አሻራን፣ የነፃነት ታሪክን አሻግረው ተመልክተውበታል፡፡ ቃል ሳይተነፍሱ (ግልፅ መልዕክትን ባዘለ ዝምታ) በዘመን ተጋሪዎቼ ዘንድ የሀገር ፍቅርን አስርፀዋል፡፡
ከብሔራዊው ይልቅ የክልል ባንዲራዎች በክብር በሚያዙበት፣ ስለ‹አንድ ሀገር፣ አንድ ሕዝብ!› ማቀንቀን ‹ትምክህተኛ›፣ ‹ነፍጠኛ›… በሚያስብልበትና እንደ ጠላት በሚያስፈርጅበት በዚህ አስጨናቂ ወቅት የባንዲራን ክብር በተግባር አሳይተውናል፡፡ ይህም ይመስለኛል የኦሎምፒክ ድል ለሀገሬ ሰው የማንነት፣ የአንድነት፣ የክብር፣ የታላቅ ህዝብ የባንዲራ ፍቅር… መገለጫ መድረክ የሆነበት ምስጢር፡፡ ጉዳዩ ከፖለቲካዊ አጀንዳም በላይ ነው፡፡ አንድ ጉልበታም ፓርቲንም ብቻ የሚመለከት አይደለም፤ እልፍ አዕላፍ አጥንታቸውን የከሰከሱበት፣ ደማቸውን ያፈሰሱበት፣ ትዳራቸውን በትነው፣ ጎጆአቸውን አፍርሰው፣ ሀገር አንፀው ለትውልድ ያስረከቡበት ጥልቅና
ታላቅ ምስጢር ይዟል፡፡ አፄ ቴዎድሮስም ሆኑ አፄ ዮሀንስ ህይወትን ያህል ነገር በቆራጥነት የከፈሉት ለባንዲራቸው ክብር፣ ለሀገራቸው ልዑላዊነት ሲሉ መሆኑን አትዘንጋ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከታሪክ ማኅደር: ዐድዋና አንድምታው (ኀይሌ ላሬቦ)

አፄ ምኒሊክ አድዋ ላይ ኢትዮጵያን የደፈረውን የጣሊያን ጦር ድል መተው ‹ከቀስተ ዳመና የሰረፀ› ያሉትን ባለአረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ቀለም ባንዲራ ማውለብለባቸውን ተከትሎ ከዓመታት በኋላ የተከሰተውንም ማንም አይስተውም፡፡ አዎን! በነጭ ቅኝ አገዛዝ ስር ይማቅቁ የነበሩ አፍሪካውያን ‹የማይደፈር› ይሉት የነበረውን የቅኝ ገዢ ኃይል ከመድፈርም አልፈው ያሸንፉት ዘንድ ብርታት ሆኗቸዋል፡ ፡ ከነፃነት በኋላም አብዛኛዎቹ የራሳቸውን ሀገር መለያ ባንዲራ ሲያዘጋጁ ከሀገሬ ባንዲራ ሦስት ቀለማት ጋር ያመሳሰሉበት ምስጢርም ይህ ነው-የትግሉን መሪ መፈክር ‹‹ኢትዮጵያኒዝም›› ታሪክ ሳይዘነጋው ማስቀጠል፡፡ ለእኛም ባንዲራችን ሀገራችንን ያፈቀርንበት፣ በአንድነታችን ልንፀና ቃለ-መሀላ የገባንበት፣ ከቶም ቢሆን ማንም ሊሽረው የማይችል ቁርኝት የፈፀምንበት እንደሆነ ይቀጥላል፡፡

እውነት እውነት እልሀለሁም፣ የ1960ዎቹም ሆነ የእኔ ትውልድ በሰላማዊ መንገድ የመንግስት ለውጥ ይመጣ ዘንድ፡-
‹‹አትነሳም ወይ፣ አትነሳም ወይ
ይሄ ባንዲራ፣ የአንተ አይደለም ወይ!›› በማለት የተቀሰቀሰበት ምክንያትም ህዝብ ባንዲራ ሲነካ ‹ሆ› ብሎ መነሳቱን ጠንቅቆ በመረዳቱ ነው፡፡

ይቺ ባንዲራ!

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ቡድን በታላላቅ አህጉራዊና አለም አቀፍ ውድድሮች ላይ መሳተፍ የሚችልበትን ብቃት እያካበተ መምጣት ጀምሯል፡፡ ባለፈው ዓመት በደቡብ አፍሪካ አዘጋጅነት በተካሄደው ሃያ ዘጠነኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ከአህጉሩ ምርጥ 16 ቡድኖች አንዱ መሆን ችሎ ነበር፡፡ የምድራችን ትልቁ በሚባለው ‹‹የዓለም ዋንጫ›› ላይም ለመሳተፍ የሚያስችለውን ድል ለመጎናፀፍ ምድቡን በበላይነት በማጠናቀቁ ከናይጄሪያ አቻው ጋር የደርሶ መልስ ጨዋታ ብቻ ቀርቶታል፡፡
ለዚህ አኩሪ ውጤት የህዝቡ ያላሰለሰ ድጋፍ የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳል፤ ደጋፊዎቹ ለፀሀይና ዝናብ መፈራረቅ ሳይንበረከኩ በሜዳው ያደረጋቸውን ግጥሚያዎች በሙሉ በአሸናፊነት ይወጣ ዘንድ ባንዲራ አንግበው፣ ባንዲራ ለብሰው፣ በአረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ቀለም ደምቀው፡-

‹‹ተከብረሽ የኖርሽው በአባቶቻችን ደም
እናት ኢትዮጵያ የደፈረሽ ይውደም›› በሚለው የክቡር ዶክተር አርቲስት ጥላሁን ገሰሰ ዜማ አበረታተውታል (መቼም ነፍስና ሀገሬን ካወኩ አንስቶ፣ ይህን ዜማ በሰማሁ ቁጥር ልቤ እንደሞቀ፣ ጉልበቴ እንደበረታ፣ ፊቴ በእንባ እንደታጠበ ነው)

ደጋፊዎቹ ጎሮሮአቸው እስኪዘጋ ‹‹አያሆሆ ማታ ነው ድሌ›› እያሉ በመጮኽ ጉልበትና ብርታት ሆነውታል፡፡ ይህም ነው የድሉ ምስጢር፤ የተጋድሎው ምርጥ ውጤት፡፡ ምንም እንኳ ጀግናው ኢህአዴግ ‹‹የመልካም አስተዳደር፣ የፖሊሲዬ እና የመለስ ራዕይ ውጤት ነው›› በማለት ድሉን በቆረጣ ሊጠልፈው ቢገዳደርም፡፡ መቼስ ኢህአዴግ ፖለቲካዊ ትርፍ የሚያስገኝለት እስከሆነ ድረስ ማንኛውንም ነገር ከማለትና ከማድረግ ወደኋላ እንደማይል ይህ የቅርብ ጊዜ አስረጅ ነው፤ በተለይ የ2005ቱ የ‹‹መለስ ፕሪምየር ሊግ›› ስያሜ ኢህአዴግ ምድራዊውን ቀርቶ ለፈጣሪ የሚቀርበውን ‹‹ፀሎትና ምስጋናም›› ሳይቀር ከመንጠቅ እንደማይመለስ ያየንበት ክስተት ነው፡፡

ከዚህ በተረፈ ሀገሪቱ እግር ኳሱን በሀቅና በብቃት የሚመራ ፌዴሬሽን ኖሯት አያውቅም፡፡ ሁሉም የፖለቲካ ተሿሚዎች ናቸው (በአንፃራዊነት በአንድ ወቅት ከሙገር ተወክለው የተሻለ ለመንቀሳቀስ ከሞከሩት ኢንጂነር ግዛው በቀር) በ1990ዎቹ አጋማሽ ሥልጣኑን ጨብጦ ፌዴሬሽኑን ሲያምሰው የነበረው ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስም ቢሆን ወደ ፓርላማ ገብቶ ያንጸባርቀውን አቋም ካስተዋልን በኋላ፣ ነገሩን ወደኋላ መለስ ብለን እንድናጤነው ግድ ብሎናል፡፡ በርግጥ ዶ/ሩ ከሀላፊነቱ የተሻረው በአምባገነንነቱ ‹‹ገንዘብ ካለ፣ በሰማይ መንገድ አለ››ን ብሂል የህይወታቸው መመሪያ ካደረጉት አላሙዲ እና ጓደኞቹ ጋር የገጠመው ‹የትከሻ ግፊያ› ሳይጠናቀቅ ነበር::
አሁን በሥልጣን ላይ ያለው የሳህሉ ገ/ወልድ አመራርም የ‹ኮሜዲ ቲያትር› እንደመሰለ ዛሬ ድረስ ቀጥሏል፤ ሲያሻው ቡድኑ በሜዳው ሀገራዊ ውድድር በሚያደርግበት ዕለት አበል ለማግኘት የሌላ ሀገር ቡድኖች ጨዋታ ‹ኮሚሽነር› ሆኖ ይሄዳል፤ ለምን ብሎ የሚጠይቀው የለም፡፡ በአናቱ በእርሱም ድክመትና እንዝላልነት ጭምር ቡድኑ ሁለት ቢጫ ያየ ተጫዋች አሰልፎ በማጫወቱ ሶስት ነጥብ በተቀጣበት ወቅት ‹‹ሥልጣን እለቃለሁ›› ብሎ ሲምል-ሲገዘት እንዳልነበረ ሁሉ፣ ሰሞኑን በአስተዛዛቢ ሁኔታ በቀጣይም ጊዜ ፌዴሬሽኑን ለመምራት በሚደረገው ምርጫ ተወዳዳሪ ሆኖ እንደሚቀርብ ሲነግረን ሀፍረት ብሎ ነገር አንደበቱን ሲያደነቃቅፈው አልተስተዋለም፡፡
በርግጥም ቡድኑ ለዝግጅት ይረዳው ዘንድ የአቋም መፈተሺያ ግጥሚያ ሳያደርግ ወደ ውድድር መግባቱ በራሱ፣ ኳሱ ‹አልቦ ፌዴሬሽን› ለመሆኑ ጠቋሚ ክስተት ነው፤ ይህም የአሰልጣኙና የቡድን መሪው ሥራ ነው ካልተባልን በቀር (በነገራችን ላይ ፌዴሬሽኑ ውስጥ የምናየው የአመራር ቀውስ፣ የስርዓቱ ብልሹ ገፅታ ማሳያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፤ በርካታ ሚሊዮን ብር ፈሶበት የተጠናቀቀ የመንገድ ሥራ ‹‹በስህተት ነው፤ የባቡር መሄጃ ስለሆነ ይፍረስ›› እንደተባለው አይነት ተጠያቂነት ያሌለበት አሰራር)፡፡ ሌላው ጉዳዩ አሰልጣኙ በውጤታማ ጉዞ ላይ እየገሰገሰ ቢሆንም፣ ፍፃሜውን ለማሳመር የአውሮፓን ተጫዋቾች ባህሪ፣ ድክመትና ጥንካሬ ጠንቅቆ
የሚያውቅ የቴክኒክ አማካሪ መቅጠርስ የማን ሥራ ነበር? መቼም አብዛኛዎቹ ተጋጣሚዎቻችን የሚያሰልፏቸው ተጨዋቾች ‹በአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች ላይ የሚሳተፉ መሆናቸውን አላወኩም ነበር› ሊል አይችልም፡፡ አንዱም ይህ ነው ውጤቱን የዚህች ባንዲራ ፍቅር እንድል ያስገደደኝ፡፡ …የፌዴሬሽኑ ሰዎችማ የገዥው ፓርቲና የሥልጣን እንጂ የሀገር፣ የባንዲራ ፍቅር የሚባል ነገር እንዳልፈጠረባቸው ደጋግመው አሳይተውናል፡፡ …ናይጄሪያንም ሆነ ሌሎች ተጋጣሚዎቻችንን ማሸነፍ፣ ለእኛ የእግር ኳስ ድል ብቻ አይደለም፤ የከፋፍለህ ግዛ አስተዳደርንም ደርቦ ማሸነፍ ነው፤ የተናጋውን አንድነት ማጥበቂያም ነው፡፡ እናም ነገም፣ ከነገ ወዲያም እያሸነፍን… ድል እየነሳን ‹‹አንድ ህዝብ፣ አንድ ሀገር››ን እናፀናለን!

ተጨማሪ ያንብቡ:  ውድ ወንድሞችና እህቶች - ሙሉጌታ በትረ ገብረማሪያም

ይቺ ባንዲራ!

ኢህአዴግ መንበረ ሥልጣን ላይ በተቀመጠ ማግስት ሀገሪቱን በብሔር መሸንሸኑ፣ የሥራ ቋንቋንም ሆነ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት በየብሔሩ ቋንቋ እንዲሆን ማድረጉ በደፈናው ‹ስህተት ነው› ባይባልም፣ የሀገር አንድነትን ማሳሳቱን እና የትምህርት ጥራትን ማዳከሙ ሊካድ የማይችል ሀቅ ነው፡፡ አልፎ ተርፎም በዘመናት የታሪክ ቅብብሎሽ ላይበጠስ የተቋጠረውን የብሔሮች ትስስር ለአደጋ ማጋለጡ ግልፅ ነው፡፡ መቼም እንደ መለስና ጓደኞቹ ህልም ቢሆን ኖሮ፣ ነገ በሚደረገው ግጥሚያ ላይ የሚገኙ ተመልካቾች አማራ የሆነ ተጫዋች ኳስ ሲይዝ-አማሮች፤ ትግሬውን-ትግሬዎች፤ ኦሮሞውን-ኦሮሞዎች… ብቻ ድጋፍ የሚሰጡበት ሁኔታ በተፈጠረ ነበር፡፡ ግና!
ይቺ ባንዲራ ‹‹17 ዓመት ታግዬ ከጨቋኝ አገዛዝ ነፃ አውጥቼሀለሁ›› የሚለውን የከፋፋይ አስተዳደር ሴራ ማክሸፏን አብስራለችና አንድነታችን ለዘላለሙ እንደሚቀጥል አምናለሁ፡፡

ይህንን ለመረዳት ስብሃት ገ/እግዚብሄር በእፍታ ቅፅ 4 መፅሀፍ ‹‹በአሉ ግርማን እንደማውቀው›› በሚል ርዕስ ካሰፈረው ፅሁፍ ላይ እንደሚከተለው ቀንጭቤ ላስነብባችሁ፡-

‹‹በአሉና ጓድ ሊቀ-መንበር መንግስቱ ቅርብ የስራ ግንኙነት ነበራቸው፡፡ ይግባቡ ነበር፡፡ ‹‹የዚያድባሬን ወራሪ ሰራዊት፣ የእኛ ሰራዊት እየነዳው ሄዶ ጅጅጋ ገባ፤ ትልቅ ድል ነበር፤ ጓድ ሊቀ-መንበር ለበአሉ ምስራቹን በስልክ ነገሩትና በመገናኛ ብዙሃን የሚነበብ ፅሁፍ እንዲያዘጋጅ አዘዙት፡፡ ‹‹ፃፈና አነበበላቸው ‹ጓድ በአሉ፣ ባንዲራችን ካራ ማራ ተራራ አናቱ ላይ ትውለበለባለች ብልሀል፡፡ እኛ እኮ የተከልናት ታች ነው፣ ጅጅጋ ውስጥ› አሉት፡፡ ‹ጓድ ሊቀ-መንበር ለእኔ የታየችኝ ተራራው ላይ ነው፡፡ አናውርዳት፡፡ እዚያው እኔ የተከልኳት ቦታ ትውለበልብ› ‹እሺ! እዚያው ትሁንልህ› አሉት ጓድ ሊቀ-መንበር እየሳቁ፡፡›› (ገፅ 515)

ከቀናት በኋላም ለበአሉ እንደታየው የኢትዮጵያ ሠራዊት ድል አድርጎ ባንዲራዋ በገሃድ ካራ ማራ ተራራ አናት ላይ ተውለብልባለች፡፡ በቃ! ለእኔ ባንዲራ ይህ ነው፤ ሌላ አይደለም፡፡ በየዘመኑ ነፃነትን፣ አንድነትን የምታበስር-የኖህ እርግብ፡፡ ነገም በሰላማዊው ፍልሚያ የሀገሬ ቡድን በናይጄሪያ አቻው ላይ የሚቀዳጀውን የድል ብስራት ባንዲራዋ ከፍ ብላ ተውለብልባ ታበስረኝ ዘንድ ተስፋ አለኝ፤ ክስተቱም የአገዛዙ ፖለቲካ መሸነፉ የሚረጋገጥበት እንደሚሆን አምናለሁ፡፡
ድል ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን!

ኢትዮሚድያ – Ethiomedia.com
October 12, 2013

4 Comments

  1. ye Tilahun Gesesse sayhon ye Muhamud Ahmed zefen neww….”tekebresh yenorshew babatochachen demm enat Ethiopia yedeferesh yiwdem…”

  2. A beautiful piece from a journalist exhibiting amazing maturity. Temesgen, you are a hero. Keep up your good work. The fact that we lost the game this afternoon should not in any way disappoint us. We Ethiopians are on a high moral ground. We shall crush the evil spirit of the serpent woyane through our unrelenting defiance to divide and rule. Ethiopia shall live forever.

  3. good job temsgen! bandawech and yebanda wolajoch hager bishetum, ethiopian begegnoch legocha tekebra tnoralech. mot lebanda lejoch.

Comments are closed.

Share