ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና ጋዜጣዊ መግለጫቸው (ከፋሲል ግርማ)

በፋሲል ግርማ

ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማሪያም ደሳለኝ ከአካላዊ እንቅስቃሴያቸው እና ድምፀታቸው ጀምሮ እስከ ሚቀልዷቸው ቀልዶች እና የሚያስተላልፏቸው መልዕክቶች በሙሉ የቀድሞውን ሟች ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በሚያስታውስ መልኩ ያካሄዱት ጋዜጣዊ መግለጫ ባብዛኛው ተቃርኖ የበዛበት ነው፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማሪያም በጋዜጣዊ መግለጫቸው ከጥያቄ እና መልሱ አስቀድመው በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መንግስት ያለውን መረጃ የተናገሩ ሲሆን እንዲሁ በደፈናው አሃዝ ሳይጠቅሱ የሃገሪቱ ምጣኔሃብት እያደገ መሆኑን፤ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ዘርፉ ካለፈው አመት የተሻለ መሆኑን እና በሰላም እና ጸጥታ ጉዳዮች ዙሪያ ከጎረቤት ሃገራት ጋር ኢትዮጵያ ያላትን ግንኙነት ለማብራራት ሞክረዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ከኤርትራ በስተቀር ከሌሎች ጎረቤት ሃገራት ጋር ያላት ግንኙነት ስትራቴጂካዊ መሆኑን ጠቅሰው፤ በተለይ የኢትዮጵያ መንግስት ከሶማሊያ መንግስት ጋር ያለውን ግንኙነት ዘርዝረዋል፡፡

እንደ እርሳቸው አገላለጽ የኢትዮጵያ መንግስት የሶማሊያ የፌዴራል መንግስት ከሃገሩ የክልል አስተዳደሮች ጋር ተስማምቶ እንዲሰራ ኢትዮጵያ የማደራደር ሚና እየተጫወተች እንደሆነ እና አልሸባብ የተባለውን አሸባሪ ሃይል ለማጥፋት በሶማሊያ ከሰፈረው የአፍሪካ ሰላም አስከባሪ ጦር ጋር በመተባበር ጥረት በማድግ ላይ ናት በማለት ሃገሪቱ በሶማሊያ ያላትን ዘርፈብዙ ጣልቃገብነት በሚያሳብቅ መልኩ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

ሃይለማሪያም እንዳሉት በኢትዮጵያ ብሎም ባጠቃላዩ ምስራቅ አፍሪካ ቀጠና የደህንነት ችግር አለ፤ ነገርግን የእርሳቸው አስተዳደር በሶማሊያ የሚያደርገው ጣልቃ ገብነት ለድህንነት ችግሩ መባባስ አንዱ ምክንያት እንደሆነ ማመን የፈለጉ አይመስልም፡፡

ኤርትራን በተመለከተ በተለይ የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቄ ከኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ሃይል የመግዛት እቅድ አለን ማለታቸውን አስመልክቶ ለቀረበላቸው ጥያቄ የኢትዮጵያ መንግስት ከዘጠኝ ዓመት በፊት ጀምሮ በሁለቱ ሃገራት መካከል ሰላም እንዲፈጠር ጽኑ አቋም እንደ ያዘ እና ጥረት እያደረገ ነው ያሉ ሲሆን፤ በኤርትራ በኩል ግን ይህ ዝግጁነት የለም ብለዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የመርገም አርማ የጥላቻ ዜማ! - ከቴዎድሮስ ሃይሌ

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ መብራት ከኢትዮጵያ እንገዛለን ማለታቸውን አስመልክቶ የራሳቸው ብቻ ፍላጎት ነው ያሉ ሲሆን፣ ምናልባትም አጣብቂኝ ውስጥ ስለሚገኝ ኑዛዜ ሊሆን ይችላል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት ከኤርትራ መንግስት ጋር ሰላም መፍጠር ይፈልጋል ብለው በተናገሩበት አንደበታቸው ጠቅላሚኒስትሩ የኤርትራ መንግስት ለራሱ ሳይሆን ሌሎችን ለመርዳት እየጣረ ይገኛል በሚል ለራሷ ክንፏ ተሰብሮ ሌላ ለመደገፍ እንደምትሄድ አሞራ መስለውታል፡፡

ሃገር ቤት ውስጥ ያሉ ተቃዋሚዎች የሚያካሂዱትን የተቃውሞ ሰልፍ በተመለከተም ለቀረበላቸው ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስላቅ የተቀላቀለበት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ እንደ ሃይለማሪያም ንግግር ሃገር ውስጥ የሚገኙ የተቃዋሚ ሃይሎች በየሳምቱ በሚያደርጓቸው ሰላማዊ ሰልፎች ተደጋጋሚ ጥያቄ ነው የሚያነሱት፡፡  እርሳቸው እንዳሉ ለጥያቄዎቹ መንግስት ቀደም ብሎ መልስ የሰጠባቸው ስለሆነ ተጨማሪ ከመንግስት የሚመጣ ነገር የለም፡፡

ሰልፎቹ በዚህ ሁኔታ የሚቀጥሉ ከሆነም የሆነ ግዜ መንግስት ሊያስቆመው እንደሚችል ፍንጭ ሰጥተዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሃገርቤት ተቃዋሚዎች የሚያሰሟቸው ጥያቄዎች የራሳቸው እንዳልሆኑ እና እንደ እርሳቸው አባባል በተለያዩ ሃገሮች ያሉ ሌሎች ሃይሎች የሰጧቸው የቤት ስራዎች ናቸው፡፡

በዚህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር፤ ለምሳሌ ሰማያዊ ፓርቲ እና አንድነት ፓርቲ የታሰሩ ጋዜጠኞች እና ፖለቲከኞች እንዲፈቱ፣ መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ላይ ጣልቃ እንዳይገባ፣ የኑሮ ውድነት የመሳሰሉት ጉዳዮች እንዲሻሻሉ ያቀረቧቸው ጥያቄዎች መልስ አያገኙም ማለት ነው፡፡

በውጭ ካሉ የተቃዋሚዎች እንቅስቃሴ በተመለከተ ግንቦት ሰባት የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ባጭሩ ህልም ነው፤ ማለም ይችላሉ ያሉ ሲሆን በፓርቲያቸው ውስጥ መሰንጠቅ ስለመኖሩም ለተነሳው ጥያቄ ምኞት ነው መመኘት ትችላላችሁ የሚል ድፍን ያለ መልስ ሰጥተዋል፡፡

ሌላው በተቃርኖ የታጀበው የጠቅላይ ሚኒስትሩ መልስ ሙስና እና ኢንቨስትመንትን በተመለከተ የቀረበላቸው ሲሆን መንግስታቸው የሙስና ቀዳዳን እያጠፋ ተወዳዳሪነት የሰፈነበት አንቨስትመንት እንዲኖር ያበረታታል ብለው የተናገሩ ሲሆን፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  አያ ጅቦ ሳታመሃኝ ብላኝ!!  (በአገሬ አዲስ)    

ሙስና ውስጥ የገቡ ባለሃብቶችን መንግስት እየተከታተለ እንደሆነ እና ሙስና ጋር ያልተነካኩ ባለሃብቶች ይህ ሊያሰጋቸው እንደማይገባ የገለፁ ቢሆንም በመቀጠል ደግሞ እስካሁን ስርቆት የፈፀሙ ባለሃብቶች ካሁን በኋላ ቢያቆሙ ጥሩ ነው በማለት ከዚህ ቀደም ለተፈጸሙ ዝርፊያዎች እውቅና ሰጥተዋል፡፡

እንዲሁም የቁጠባ ቤቶችን በተመለከተ የወጣው መመሪያ የቁጠባ ቤት ተመዝጋቢዎች በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ብቻ ነው መቆጠብ የሚችሉት መባሉ የሌሎች የግል ባንኮችን ተወዳዳሪነት ይቀንሳል መባሉ የተሳሳተ ትንተና የተካሄደበት ትችት ነው ያሉ ሲሆን ባንኩ ሰዎች ከሚቆጥቡት 20 በመቶ ገንዘብ ላይ 80 በመቶ ጨምሮ ስለሚያበድራቸው  ተጎጂ እንደሆነ ለማብራራት ሙከራ አድርገዋል፡፡

ነገርግን በዚህ መልሳቸው ባንኩ 80 በመቶ ብድር ሲሰጥ ጎን ለጎን በብቸኝነት ኢንቨስትመንት እያካሄደ ስለመሆኑ የሰጠውን ብድር መልሶ ከወለድ ጋር እንደሚያገኘው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዘነጉት ይመስላል፡፡

በመሰረተ ልማት ላይ ስለሚገኙ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለተጠየቁት ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማሪያም ከፖለቲካዊ ችሎታቸው ይልቅ የምህንድስና ሙያ እውቀታቸውን ተጠቅመው ለማብራራት ሙከራ ያደረጉ ሲሆን እዚህም ላይ ግራ አጋቢ መልሶች እና ማብራሪያዎች ሰጥተዋል፡፡

የተፋሰስ ችግር በመኖሩ የአስፋልት መንገዶችን እያበላሻቸው መሆኑን የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቀድሞ ነገር መንገዶቹ ሲሰሩ ተፋሰሱንም አብሮ መስራት ለምን እንዳልተቻለ አልጠቆሙም፡፡

በተመሳሳይ መልኩ የመብራት ችግር በተለይ በመኖሪያ አካባቢዎች መብራት የሚቋረጠው አዳዲስ ማሽን ቤቶች በብዛት ስለሚከፈቱ እና በየአካባቢው ያሉ ማከፋፋያዎች ለእነዚህ የሚሆን ሃይል የመሸከም አቅም ስለሌላቸው ነው በሚል ቴክኒካል መልስ የሰጡ ሲሆን እንደ ቃሊት አካባቢ ለሚገኙ የኢንዱስትሪ አካባቢ የሚባሉ አካባቢዎችም ችግሩ ተመሳሳይ እንደሆነ ነው ያብራሩት፡፡

የሞባይል ኔትዎርክ መጣበብ ችግርም ተጠቃሚ ከታቀደው በላይ ስለበዛ ነው ያሉ ሲሆን ይህ የእቅድ እና ነባራዊ ሁኔታ አለመጣጣም እንዲሁም በተደጋጋሚ የሚያነሱት የአፈጻፀም ችግር በቀድሞውም ጠቅላይ ሚኒስትር ሲሰጥ የነበረ ሲሆን ይህ የማቀድ እና የማስፈጸም ችግር ከመንግስት ብቃት ማነስ ጋር ስለመያያዙ ማንሳት የፈለጉ አይመስሉም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ስለመሬት መሸጥ መለወጥ -ተጨማሪ ማብራሪያ (ፋሲል የኔዓለም)

ባጠቃላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ  አስተዳደራቸውን ምዕሉ በኩለሄ አይነት አድርገው የሳሉት ሲሆን ለተፈጠሩ ችግሮች ሁሉ ሰበብ አስባብ ከመደርደር የዘለለ መልስ አልሰጡም፡፡

ከአጠቃላይ መግለጫው ግን አንድ ነገር በእርግጠኝነት እንድንገነዘብ አድርገውናል፤ ኢህአዴግ ሌላው ቢቀር የአቀራረብ ለውጥ እንኳ እንደማይኖረው፡፡

1 Comment

  1. ይሄ ሸምዳጅ ጠቅላይ ሚኒስትር ከወያኔ ትብታብ የሚላቀቀው መቼ ይሆን?

Comments are closed.

Share