በአዲስ አበባ፣ በወልቂጤ፣ በአፋር፣ በደሴና በአዳማ ሙስሊሞች ላይ መንግስት እርምጃ ወሰደ

(ዘ-ሐበሻ) ለኢድ ሶላት በወጡ ሙስሊሞች ላይ መንግስት ድብደባ መፈጸሙ ታወቀ። በአዲስ አበባ፣ በወልቂጤ፣ በአፋር፣ በደሴ፣ በአዳማና በሌሎችም ከተሞች ለኢድ ሶላት በወጡ ሙስሊሞች ላይ መንግስት ከአንድ ሳምንት በፊት በሰጠው ማስጠንቀቂያ መሠረት ዛሬ ድብደባውን ሲፈጽም በተለይም አዲስ አበባ የጥይት ድምጽ መሰማቱን እና አድማ በታኝ ፖሊሶችም አስለቃሽ ጭስ መጠቀማቸውን ከድምጻችን ይሰማ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የ1434ኛውን የኢድ አልፈጥር በዓል በዛሬው ዕለት በመላው ዓለም የሚገኙ ሙስሊሞች እያከበሩት ሲሆን በኢትዮጵያ የተከበረው በተቃውሞ፣ በእስር፣ በድብደባና በ እንግልት መሆኑ በርካታ ሙስሊሞችን እንዳስቆጣ ከተለያዩ የመረጃ ምንጮች ከምናገኛቸው የሕዝብ አስተያየቶች መረዳት ችለናል። በአዲስ አበባ የፌደራል ፖሊስ በወሰደው እርምጃ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሙስሊሞች ድብደባ የደረሰባችው ሲሆን የተደብዳቢ ሰዎችም ፎቶ ግራፍ ከነደማቸው በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ ተለቋል።
“የመንግስት ታጣቂዎች የዒድ ክብረ በዓልን ለመፈጸም የወጡ ሰላማዊ ዜጎች ላይ ከፍተኛ ኃይል የተቀላቀለበት ድብደባ ፈጽመዋል፡፡ መንግስት ለኢትዮጵያውያን ሙስሊም ዜጎቹ ያለውን ከልክ ያለፈ ጥላቻ በዛሬውም በኢድ በዓል ቀን አሳይቷል፡፡” ሲል ሁኔታውን የገለጸው ድምፃችን ይሰማ ፌዴራል ፖሊስ ሙስሊሞችን እስከቤታቸው ደጃፍ ድረስ እየተከተለ ጥቃት ሲዘነዝሩባቸው ውለዋል ብሏል።
በሙስሊሞቹ በዓል ላይ እንዲህ ያለው ተግባር ቢፈጸምም መንግስታዊ ሚዲያዎች ግን በዓሉ በሰላም መጠናቀቁን እየዘገቡ ነው። በተለይ የሕወሓት ራድዮ የሆነው ራድዮ ፋና የዛሬውን በዓል በማስመልከት የዘገበው የሚከተለውን ነው። “ሙስሊሙ ማህበረሰብም ከማለዳው ጀምሮ ወደ ስቴዲየም በማምራት በአሉን በሰላት ፣ በስግደት ተክቢራና ሌሎችንም ሀይማኖታዊ ስነ ስርአቶች በማካሄድ አክብሮታል። በበአሉ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሸህ ኪያር ሙሀመድ አማን እንዳሉት ፥ በረመዳን ሙስሊሙ ፈጣሪው ያዘዘውን መልካም ነገሮች ሁሉ ሲከውን መቆየቱን አንስተዋል። መልካም ነገሮች የሚደረጉት በረመዳን ብቻ ባለመሆኑ ሙስሊሙ ማህበረሰብ ከረመዳን በኋላም መልካም ነገሮችን ማድረጉን እንዲቀጥል አሳስበዋል። በሀይማኖት ስም አንዳንድ አክራሪዎች ሰላምን የሚነሳ ድርጊት እየፈጸሙ መሆኑን ጠቁመው ፥ ይህም መላው ሙስሊሙ በየመስጊዱ ጸሎቱን በአግባቡ እንዳይከውን እያደረገ ይገኛል ብለዋል። ይህን ተቀባይነት የሌለውን ድርጊትም ሙስሊሙ መታገል አለበት የሚሉት ፕሬዝዳንቱ ፥ በአሉን ካጡና ከተቸገሩ ወገኖች ጋር በጋራ ማክበር ይገባል ነው ያሉት።
የመንግስት ሚድያዎች በዓሉ በሰላም መጠናቀቁን ቢዘግቡም ድምፃችን ይሰማ ደግሞ ተቃውሞውን በቪድዮ ለአደባባይ በማብቃት የመንግስትን ውሸት እርቃኑን እንዳስቀረው ታዛቢዎች የሚናገሩት።
http://youtu.be/FoOADBjWeTc

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኮሜዲያን አዜብ መስፍን አዲስ ቀልድ (ቪድዮ)
Share