በዛሬው የተቃውሞ ሰልፍ የኢቲቪ የሀሰት ዘገባ ሲጋለጥ

ከብስራት ወ/ገብርኤል

ዛሬ ሐምሌ 7 ቀን 2005ዓ.ም. ከጠዋቱ 3 ሰዓት ከአራዳ የአንድነት ፓርቲ ጽህፈት የጀመረው የአንድነት ፓርቲ የጠራው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በፒያሳ አድርጎ መዳረሻውን በሆጤ ስታዲየም በማድረግ ከቀኑ 6 ሰዓት በሰላም ተጠናቋል፡፡
የህዝቡም ጨዋነት እጅግ የሚያስገርም ሲሆን በሰልፉ ላይ የተገኙት ከደሴ ከተማ፣ ከሐይቅ ከተማ፣ ከኮምቦልቻ ከተማ እንዲሁም ከወረባቡ እና ኩታበር ወረዳ የመጡ ተሳታፊዎችንም ማግኘት ችለኛል፡፡ በሰልፉ መርሃ ግብር ፍፃሜ ላይም የአንድነት ፓርቲ የደቡብ ወሎ ዞን ሰብሳቢ አቶ ብስራት አቢ፣ የአንድነት ፓርቲ ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ እና የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት ግብረኃይል ሰብሳቢ አቶ ዳንኤል ተፈራ በመጨረሻም በፓርላማ ብቸኛው የህዝብ ተወካይና የአንድነት ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ግርማ ሰይፉ ንግግር ካደረጉ በኋላ መርሃ ግብሩ በሰላም ተጠናቋል፡፡

በመቀጠልም የሰልፉ ተሳታፊዎች የፀረ-ሽብር ህጉ እንዲሰረዝ የሚጠይቀውን ሰነድ ሲፈርሙ መታዘብ ችያለሁ፡፡ በሰልፉ ላይም በግምት ከ50ሺህ ሰው በላይ የተገኘ ሲሆን ከደሴ፣ከኮምቦልቻና ከሐይቅ ከተማ እንዲሁም ከወረባቡ እና ከኩታበር ወረዳ የመጡ እንደነበሩ አንዳንዶቹን ታዳሚዎች ባነጋገርኩበት ወቅት አረጋግጠውልኛል፡፡ የሰልፉ ታዳሚዎችም ሰላማዊ ሰልፉን ላዘጋጀው አንድነት ፓርቲ ምስጋና እና አድነቆት ሲቸሩም ተመልክቻለሁ፡፡

በሰላም የተጠናቀቀውን ሰለማዊ ሰልፍ ለመዘገብ የመጡ ከሀገር ውስጥ ሚዲያዎች መካከል ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ፣ኢቴቪ፣ የአማራ ክልል መገናኛ ብዙኃን፣ የፖሊስ ሚዲያ፣ ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል፣ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና ለጊዜው ከየትኛው ሚዲያ እንደመጡ ያላረጋገጥኳቸው የሀገር ውስጥና የውጭ ጋዜጠኞችን ማየት ችያለሁ፡፡
ይሁን እንጂ ኢቴቪ ሰላማዊ ሰልፉ ከተጠናቀቀ ከ 40 ደቂቃ በኋላ ተመርጠው የተዘጋጁ ግን በሰላማዊ ሰልፉ ላይ ያልተገኙ ሰዎችን ሰብስቦ በሰልፉ ላይ የተገኙትም ሆኑ አንድነት ፓርቲ ያላንፀባረቀውን ጥያቄ እንደተንፀባረቀ አድርጎ ጋዜጠኛው ቃለመጠይቅ ሲያደርግ እጅከፍንጅ በመያዝ እኛም የቀረበውን ቃለመጠይቅ ቀርፀናል፡፡ እኔ እንደሚገባኝ ከሆነ ኢቴቪ ሰላማዊ ሰልፉ ላይ የተንፀባረቀውን የህዝቡን ጥያቄ አንሻፎ በማቅረብ ሌላ የሀሰት ዘጋቢ ፊልም ሊያዘጋጅ መሆኑ ነው፡፡ ቃለመጠይቁን ጠያቂውንና ተጠያቂውን ምስላቸውን በ”Millions of voices for Freedom” ዩቲዩብ ላይ ለቀነዋል ተመልከቱ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰባዊነትንና ኢትዮጵያዊነትን እናንፀባርቅ - አልማዝ አሰፋ

በተጨማሪም ቃለመጠይቅ የተደረገላቸው አቶ ጌታቸው እባላለሁ ያሉን ግለሰብ የኢቴቪ ጋዜጠኛ ያቀረበሎት ጥያቄ ሰላማዊ ሰልፉ ላይ ተንፀባርቋል ወይ? ስል ላቀረብኩላቸው ጥያቄ መቅረፀ ድምፁን ዝጋውና ካሉ በኋላ እኔ በሰላማዊ ሰልፉ ላይ አልተገኘሁም የጠየቀኝን ነው የመለስኩት ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በምስሉ ላይ የምታገኙት ስሙን የማልገልፅላችሁ የኢቴቪ ጋዜጠኛንም በሰልፉ ላይ አንድነት ፓርቲም ሆነ ህዝቡ ያላንፀባረቁትን እንዴት እንዳንፀባረቁ አድርገህ ትጠይቃለህ? ስለው የሚመልሰው አጥቶ ሲንተባተብ ከቆየ በኋላ እንደማለቀው ሲያውቅ እኔ የሰማሁትን ነው በሚል ብቻ ጭንቀቱ ስለገባኝ በመቅረፀ ድምፅ ምላሹን አኑሬ ልገላገለው ችያለሁ፡፡

ያው እኔም ለህዝቡ፣ለሀሩና ለዓለም ይጠቅም ዘንድ እንደሰለጠነ ለእውነት እና ለሙያው እንደቆመ ነፃ ጋዜጠኛ ያየሁት ነግር አስገርሞኝ ከካሜራ ባለሙያ ባልደረባዬ ያሬድ ጋር ከምንሳፈርበት ታክሲ በፍጥነት ወርደን በመቅረፅ ኢቴቪ የተለመደውን የውሸት ዘገባና ዘጋቢ ፊልም ከማሰራጨቱ በፊት እውነታውን ህዝብ እንዲረዳ እንዲሁም የደሴ እና የአካባቢው ህዝብ ጥያቄ እንዳይዳፈን በማሰብ ለመልቀቅ ተገደናል፡፡

Share