(ዘ-ሐበሻ) አንድነት ፓርቲ ‘የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት’በሚል መርህ በደሴና በጎንደር የጠራው የተቃውሞ ሰልፍ ዛሬ ጁላይ 14 ቀን 2013 ዓ.ም በሰላም መጠናቀቁን ከስፍራው የተገኘው መረጃ አመለከተ።
በደሴ ከተማ ከአንድነት ፓርቲ ጽህፈት ቤት ተነስቶ እስከ ሆጤ ሜዳ ድረስ በቀጠለቀው በዚህ የተቃውሞ ሰልፍ በ50ሺዎች የሚቆጠሩ የአካባቢው ሰዎች በመገኘት ተቃውሟቸውን አሰምተዋል። ተቃውሞ ለወጣው ሕዝብም በፓርላማው ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ አባል አቶ ግርማ ሰይፉ እና አቶ ዳንኤል ተፈራ ንግግር አድርገዋል።
‘የ እምነት ነፃነትን መንግስት ያክብር’
‘ለኢሕ አዴግ የቅጥፈት ፕሮፓጋንዳ ጆሯችንን አንሰጥም’
‘መንግስት በሃይማኖት ጣልቃ መግባቱን ያቁም’
‘በአባይ ጉዳይ ወሳኙ የኢትዮጵያ ህዝብ እንጂ ግብጽ አይደለችም’
‘ዘርን መሠረት ያደረገ የቦታ መፈናቀል ባስቸኳይ ይቁም”
‘ሰላም አጣን በሀገራችን’
‘ወኔ የሌለው የሀገር ሸክም ነው’
‘የሸህ ኑሩ ድራማ ነው’
‘ራሱ ገዳይ ራሱ ከሳሽ’
‘ራሱ ገድሎ ገደሉ አለ’
‘ፍትህ እያሉ ቃሊቲ ገቡ’
‘በጥፊ በእርግጫ አይገዛም ሀገር’
የሚሉና ሌሎችንም መፈክሮችን የያዙት እነዚሁ ሰልፈኞች ከደሴ የአንድነት ጽ/ቤት ሲነሱ ቁጥራቸው በግምት 2 ሺህ የነበረ ቢሆንም በኋላ ግን መንገድ ላይ ብዙዎች ሰልፉን በመቀላቀል ቁጥራቸው ወደ 50 ሺህ ሊበልጥ ችሏል ሲሉ የዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች ተናገረዋል።
መንግስት ይህን የተቃውሞ ሰልፍ እንዳይካሄድ ሲያሰናክል እንደሰነበተ አንድነት ፓርቲ ሲከስ የነበረ መሆኑ ይታወቃል። በተለይም አንድነት በደሴ አካባቢ ከሚገኙ ከተሞች ወደ ከተማዋ የሚመጡ የሕዝብ ማመላለሻዎችን በስውር ትዕዛዝ እንዳይጭኑ በማድረግ ከሷል። ሆኖም ግን ሕዝቡ ይህን ሁሉ ተቋቁሞ በተለይም የገዢው ፓርቲ ተወካዮች በየሰፈሩ በመሄድ “ሰልፉ ተሰርዟል፤ ህጋዊ ፈቃድ የለውም” እያሉ ቢያዘናጉም ከ50 ሺህ ሰው በላይ በመውጣት ድምጹን ማሰማቱን ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመልክቷል።
(የደሴው ሰልፍ ሲጀመር የሚያሳይ ቪድዮ)
በሌላ በኩል መድረሻውን ጎንደር መስቀል አደባባይ ያደረገው የጎንደር ሰላማዊ ሰልፍም በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁን አንድነት ገለጸ። እንደድርጅቱ ገለጻ በዚህ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ከ40 ሺህ በላይ ህዝብ መገኘቱን የጠቆመው ድርጅቱ በመንግስት የሚደረገውን ከፍተኛ ጫና በመቋቋም ህዝቡ ድምጹን ለማሰማት መውጣቱ ድርጅቱን እንዳስደሰተው ገልጿል።
የደሴ ህዝብ ከያዘው መፈክር ጋር የሚመሳሰሉ መፈክሮችን እና “አትነሳም ወይ የመተማ መሬት ያንተ አደለም ወይ” ሲል ድምጹን ያሰማው የጎንደር ህዝብ የታሰሩት እንዲፈቱ፤ በኢትዮጵያ ሰብ አዊ መብት እንዲከበርና የዜጎች ተዘዋውሮ የመሥራትና የመኖር መብት እንዲከበር ጠይቀዋል።
የሚከተለውን የኢሳት ሰበር ዜና ቢመለከቱት ተጨማሪ መረጃ ያገኛሉ፦