UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
ቁጥር፡ አንድነት/694/2ዐዐ5
ለጠ/ሚ ኃይለማሪያም ደሳለኝ
አዲስ አበባ
ጉዳዩ፡- በመላ ኢትዮጵያ በአባሎቻችን ላይ እየተፈፀመ ያለውን ህገ ወጥ እስርና እንግልት በተመለከተ
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲከበሩና የህግ የበላይነት እንዲጠበቅ ህገ መንግሥታዊ መብቱን በመጠቀም በሠላማዊ መንገድ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ ፓርቲያችን የፖለቲካ ስርዓቱ አካል እንደመሆኑ በሀገራችን በሚደረገው የዴሞክራሲ ግንባታ ሂደት የበኩሉን አስተዋፅኦ በማድረግ ላይ ነው፡፡ በዚህም መሠረት የሦስት ወር ህዝባዊ ንቅናቄ እቅድ በማውጣት በመላ ኢትዮጵያ የሚካሄድ ፍፁም ሠላማዊ የሆነ የተቃውሞ እንቅስቃሴ መርሃ-ግብር ይፋ አድርጓል፡፡
ይህ ህዝባዊ ንቅናቄያችን የቅስቀሳ ወረቀት መበተን፣ ፔቲሽን በማስፈረም፣ ህዝባዊ ስብሰባ በማካሄድና ሠላማዊ ሠልፍ በማድረግ የሚካሄድ ይሆናል፡፡ በዚህ ሠላማዊ እንቅስቃሴያችን ላይ ግን ፍፁም ህገ-ወጥ በሆነ መንገድ አባሎቻችን በአዲስ አባና ከአዲስ አበባ ውጭ እየታሰሩ ይገኛሉ፡፡ የድርጅታቸውን ወረቀት ስላሰራጩ ብቻ የታሰሩ አባሎቻችንም በርካታ ናቸው፡፡ ለአብነት ያህል በሰሜን ጎንደር ዞን በምዕራብ አርማጭሆ አብርሃ ጅራ ከተማ የፓርቲያችን አባላት የሆኑት አቶ አለልኝ አባይ፣ አቶ እንግዳው ዋኘው፣ አቶ አብርሃም ልጃለምና አቶ አንጋው ተገኝ የፓርቲውን የሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ ለምን በተናችሁ ተብለው ከሰኔ 22 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ እንዲሁም በጎንደር ከተማ አቶ ማሩ አሻገረ ከሰኔ 26 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ፣ አቶ አምደማሪያም እዝራ እና አቶ ስማቸው ዝምቤ ከሰኔ 25 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ በእስር ላይ ናቸው፡፡ እንዲሁም በወገራ አቶ ጀጃው ቡላዴ ሰኔ 25 ቀን 2005 ዓ.ም ታስሮ ተለቋል፡፡ አቶ ጋሻው ዘውዱ ላይ ጥይት በመተኮስ የመግደል ሙከራ የተደረገ ሲሆን ሮጦ ለማምለጥ ችሏል፡፡ በአልፋ ጣቁሳ ወረዳ መምህር አዋጁ ስዩም ከሰኔ 26 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ በእስር ላይ ሲሆን ሁሉም የታሰሩት ለምን ቀሰቀሳችሁና ወረቀት አሰራጫችሁ በሚል ነው፡፡ በተመሳሳይም በአዲስ አበባ አቶ ሙሉጌታ ተፈራ ፔቲሽን በማስፈረም እንቅስቃሴ ላይ እያሉ ሰኔ 30 ቀን 2005 ዓ.ም በህገ-ወጥ መንገድ ታስረው ይገኛሉ፡፡
ስለዚህ ይሄ ህገ-ወጥ እስር በአስቸኳይ እንዲቆም እየጠየቅን የታሰሩትም በአስቸኳይ እንዲፈቱ በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡
ከሠላምታ ጋር
ግልባጭ ነጋሶ ጊዳዳ (ዶ/ር)
ሊቀመንበር
- ለኢፊድሪ ፕሬዘዳንት
- ለሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት
- ለፌዴሬሽን ም/ቤት
- ለፌደራል ፖሊስ
- ለአዲስ አበባ ፖሊስ
- ለሰብዓዊ መብት ኮሚሽን
- ለሰብዓዊ መብት ጉዳይ
- ለእንባ ተባቂ ተቋም
- ለአማራ ክልል መስተዳድር
- ለሰሜን ጎንደር ዞን
- በአዲስ አበባ ለሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ
- ለመንግስትና የግል ሚዲያዎች