ሕልምና የኢትዮጵያ ፖለቲካ በተቃራኒው ይተረጎማል

ከኤፍሬም እሸቴ

የሰሞኑ ትልቁ አገርኛ ዜና (ቢያንስ በዳያስጶራው ዓይን) የመንግሥት ባለሥልጣናት በሙስና ምክንያት መያዝና መታሰር እንዲሁም የባሕር ዳሩ ሰላማዊ ሰዎች ግድያ ጉዳይ ነው። አገር ቤት የማይነበቡት ድረ ገጾችና የጡመራ መድረኮች (ብሎጎች)፣ የአካባቢ ሬዲዮኖችና ማኅበራዊ ድረ ገጾች (ለምሳሌ ፌስቡክና ትዊተር) የሚያወሩት ስለዚሁ ነው።

አጀንዳ አንድ
የባሕር ዳሩ ግድያ ከወንጀልነቱ በላይ ትልቅ መወያያ ሆኖ የሰነበተው የገዳዩ ማንነት ጉዳይ ነው። ገዳዩ የፌዴራል ፖሊስ አባል መሆኑ የተለያዩ መላምቶችን፣ ግምቶችን፣ ትርጉሞችን እያሰጠ ሁሉም በፈለገው መልክ እንዲተችበት ዕድል ሰጥቶ ሰንብቷል። የፖለቲካ ልዩነቶች ብቻ ሳይሆኑ የብሔረሰብ ማንነቶችም እየተነሡ “ገዳዩ ከዚህ ብሔረሰብ ነው፤ ከዚያ ብሔረሰብ ነው” በሚል ጥሩም መጥፎም አስተያየቶች ሲሰነዘሩ ቆይተዋል። መንግሥትን እና መሠረቱን የሚደግፉት በአንድ በኩል፣ ተቃዋሚዎቹ እና በተለይም የዘር-ፖለቲካን አምርረን እንቃወማለን የሚሉት በሌላ በኩል የሐሳብ ጥይቶች ሲያስወነጭፉ ነበር።

ዝግ እና መተንፈሻ የሌለው ማኅበረሰብ እና ነጻ ማኅበረሰብ ተመሳሳይ አደጋዎችን የሚያስተናግድበት መንገድ እንዴት እንደሚራራቅ ጥሩ ማሳያ ሆኖልኛል። ዝግ እና መተንፈሻ የሌለው ማኅበረሰብ የሌለው ያልኩት ነጻ ሚዲያ የሌለበትን የኛን አገር መሆኑ ግልጽ ነው። ነጻ ማኅበረሰብ ያልኩት ነጻ ሚዲያዎች ያሉበትን እንደሆነው ሁሉ።

Christopher Jordan Dorner የተባለ የሎስ አንጀለስ ከተማ ፖሊስ እና የቀድሞ የጦር ሠራዊት ባልደረባ በሥራ ቦታው በገጠመው አለመግባባት ሰበብ አራት ሰዎችን ገድሎ ለሳምንት ያህል አካባቢውን ሲያሸብር ቆይቶ በመጨረሻ ራሱን እንዳጠፋ መቸም ሳትሰሙ አልቀራችሁም። ከጥር 26 – የካቲት 5/2005 ዓ.ም ድረስ አካባቢውን አሸብሮት ነበር። የታጠቀ ነው። ፖሊስ ብቻ ሳይሆን ወታደርም ነው። የሰለጠነ። በጠላት ላይ ማዞር ያለበትን ጠመንጃ ወደራሱ ዜጎች ሲያዞር እንዴት እንደሚዘገንን መገመት ይቻላል።

ግለሰቡ የሥራ ባልደረቦቹን ከገደለ በኋላ ተሰወረ። ሐሰሳ ተጀመረ። ሚዲያዎች ሰፊ ሽፋን ይሰጡ ነበር። ቀንም ሌሊትም ሲፈለግ ቆየና በሰዎች ጥቆማ ያለበት ተደረሰ። ከዚያም ራሱን አጠፋ። በቃ። ጉዳዩ በዚሁ አበቃ። ስለ ሰውየው ማንኛውንም ዓይነት ማብራሪያ ለሚፈልግ ሰው መረጃዎቹ በስፋት አሉ። ማነው? የት ተወለደ? አደገ? መቼ ወደ ጦሩ ተቀላቀለ? እንዴት ከዚያ ወጥቶ ፖሊስ ለመሆን በቃ? ከባልደረቦቹ ጋር ለምን ተጣላ? ለምን ወደዚህ ዓይነት ወንጀል ሊገባ ቻለ? ወዘተ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በደመ ነፍስ የምትነዳ ሀገር -

ባሕር ዳርስ? ባሕር ዳር ላይ አንድ የፌዴራል ፖሊስ አባል ብዙ ሰዎችን ገደለ። ከዚያ … ውዥንብር። ግማሹ 12 ሰው ተገደለ ይላል፣ ሌላው ደግሞ 18 ያደርሰዋል። ሰውየው ማን ነው? መቼ ፖሊስ ሆነ? ለምን ወደ መግደሉ ሊገባ ቻለ? ግድያውን በአጭሩ ማስቆም አይቻልም ነበር ወይ?

ችግሩ ምንድር ነው? ሚዲያ የለም፤ የግል ጋዜጣና ቴሌቪዥን የለም፣ የመንግሥቱም ቢሆን ለዚህ ዓይነቱ ነገር ዝግ ነው። … ነጻ ሚዲያ ሲጠፋና ትክክለኛ መረጃ ሲታጣ በመካከል ምን ይነግሣል? ግምት፣ ውሸት፣ ሽብር፣ ጥርጣሬ። ቢያንስ በዳያስጶራው ሚዲያዎች እና በማኅበራዊ ድረ ገጾች የነበረው እንደዚያ ነው። (‘ዳያስጶራ ልማዱ ነው’ ካልተባለ በስተቀር)።

እንዲህ ዓይነቱ አደጋ ሲከሰት የመጀመሪያው እንዳልሆነ የሚናገሩ ሰዎች አጋጥመውኛል። ሌላም ቦታ የተከሰተ ከነበረ ሊቀጥል እንደማይችል መተማመኛ ማግኘት ይከብዳል። አዕምሯቸው የተቃወሰ መሣሪያ የያዙ ሰዎች መኖር የየትኛውም አገር ችግር ይመስለኛል። ችግሩ ተመሳሳይ ከሆነ መፍትሔውም ከሌላ ትምህርት ሊወሰድበት የሚችል ነው ማለት ነው። በባሕር ዳሩ ጉዳይ እንዳየኹት ግን ዜጎችም ይሁኑ የመንግሥት ሰዎች ነገሮቹን የተመለከቱበት አቅጣጫ ከተለመደው ከዚያው አሰልቺ የአገራችን የዘር-ፖለቲካ አንጻር ብቻ መሆኑ ያሳፍራል።

ለምሳሌ የብዙ ሰው ጥያቄ የ“ፌዴራል ፖሊስ” አባል ከሆነ፣ እነዚህ ፖሊሶች ደግሞ የሰውን ሰብዓዊ መብት በመግፈፋቸው እንጂ ሰላም በማስከበራቸው የሚታወቁ ካልሆነ፣ ግድያው ከተለመደው የሰብዓዊ መብት ጥሰት አንጻር እንጂ ከወንጀልነቱ አንጻር የተሰጠው ግምት አናሳ ነበር። እንዲያውም ሆን ተብሎ የተፈጠረ የመንግሥት የማሳሳቻ ዘዴ ሆኖም ተተችቶበታል።

አጀንዳ ሁለት
በተመሳሳይ መልኩ የሰሞኑ ትልቅ አጀንዳ የሙስናው እና በሙስናው ምክንያት የተባረሩት ጎምቱ ባለሥልጣኖች ጉዳይ ነው። የባሕር ዳሩን ማስቀደሜ ከምንም ነገር በላይ ክቡሩን የሰው ሕይወትን መጥፋት የተመለከተው ዋነኛ በመሆኑ ነው። በተጨማሪም እንዲህ ዞር ያለበት “ቱቀማ” ሰው ተነሥቶ በየመንገዱ ሲገድል ቢያንስ በእኛ አገር የተለመደ ስላልሆነ ነው። (ቱቀማ (ኦሮምኛ)= ንክ (አማርኛ))።

ግንባራቸው የማይፈታው ብርሃን ኃይሉ በአቅም ማነሥ (የጉልበት ሥራ መሰለ አይደል?) ከሥልጣናቸው ሲባረሩ መልከ መልካሙ አቶ መላኩ ፈንታ (በሚኒስትር ማዕረግ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር)፣ ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ገብረ ዋሕድ ወልደ ጊዮርጊስና የባለሥልጣኑ ዋና ዓቃቤ ሕግ አቶ እሸቱ ወልደሰማያት በፀረ ሙስና ኮሚሽንና በብሔራዊ መረጃ ማዕከል ሰዎች መታሠራቸው ተነግሯል። በሙስና ምክንያት፤ ስኳሯ ላይ ተገኝተው ነው ተብሏል። በዝርዝር ምን እንደሆነና ምን እንደተደረገ የአደባባይ ምሥጢር ስለሆነ ደግሞ ማተቱ አንባቢን ማድከም፣ ቦታ ማበላሸት ነው። ጥያቄው እኛ ዜጎች ዜናውን እንዴት ነው የተቀበልነው የሚለው ላይ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያ ትውልድ፡ ሜይ ደይ'ና ዝክረ ሰማዕታት

በሙስና ምክንያት ተይዘው ከታሠሩት ከአቶ ታምራት ላይኔ ጀምሮ እስከአሁን ድረስ መንግሥት በሙስና አሰርኳቸው የሚላቸውን ሰዎች የታሰሩበት ምክንያት በርግጥም ሙስና ነው ብሎ የሚቀበል ብዙ ሰው አይደለም። ታምራት ላይኔም ሆኑ ስዬ አብርሃና ቤተሰቦቻቸው ብሎም እነ መላኩ ፈንታ ሙስና ውስጥ አልገቡም ብሎ የሚከራከር እንደሌለው ሁሉ ዋነኛ የመታሰራቸው ሰበቡ ግን ሙስናው ነው የሚል አይገኝም። በሙስና መታሰር ቢኖር እነ እንትና መቅደም አልነበረባቸውም ተብሎ ስም መጥራት ሲጀመር በአሳሪዎችና በታሳሪዎቹ መካከል ልዩነት ይጠፋል።

በሙስና ሰበብ ከማሰር የደርጉ “የፍየል ወጠጤ” ዘፈን ይሻላል?
ለመናገር ከመፍራት ካልሆነ በስተቀር የኢሕአዴግ መንግሥት ተቃዋሚዎቹን የማስወገጃ ዘዴ ሕጋዊ የሚመስሉ ሕገወጥ ተግባሮች ናቸው። ለምሳሌ በሙስናና በአሸባሪነት ስም ወህኒ ማውረድ። ደርግ ምን ያደርግ ነበር ብንል የማይፈልጋቸውን ሰዎች “የፍየል ወጠጤ” የሚለውን ልብ ነቅናቂ ዘፈን አስቀድሞ ከዚያ በግልጽ ይገድል፤ ያስር ነበር። ሙስና የዘመናችን የፍየል ወጠጤ ናት ማለት ነው? ከሆነ አይቀር አንድኛውኑ የፍየል ወጠጤው ይሻላል። ከጀርባ ከመመታት እያወቁት ከፊት ለፊት መመታት።

“ኮንስፒረሲ ቲዮሪ” የሚወድ ባህል መፍጠር፣
እውነተኛው ምክንያት ሆኖ ለሰበቡ ግን ሌላ ነገር መፍጠር ቀስ በቀስ አዲስ ልማድ እየሆነ ነው። በሙስና ስም የፖለቲካ ልዩነትን ማስተንፈስ ሲለመድ ነገ በትክክሉ ሙስና የፈጸሙ ሰዎች ለወንጀላቸው ሐዘኔታ የሚሰማው ሰው እንዲያገኙ መንገዱ ይመቻችላቸዋል። በርግጥም ሙሰኞቹን ከፖለቲካ መብት ተከራካሪዎች ለይቶ መመልከት ይከብዳል።

አሸባሪ የሚባለውን ቃልና ሐሳብ በዚሁ አገባብ ልንመለከተው እንችላለን። የፖለቲካ ልዩነት ያላቸው፣ መብታቸውን የጠየቁ ሰዎች ‘አሸባሪዎች” ሲባሉ ትክክለኞቹን ከአሸባሪው መለየት ከባድ ይሆናል። በዚህ መምታታት ውስጥ የሚያድጉ ልጆች ምን ዓይነት መረዳት ይዘው እንደሚያድጉ ፈጣሪ ይወቀው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አዲስ ለሚዋቀረው ለኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ አማራጭ ሀሳብ ጠቁዋሚ - ይድረስ ለሚመለከታችሁ ሁሉ

ተኩላ ሳይመጣበት ለቀልድ “ኡኡኡ ድረሱልኝ፣ ተኩላ በጎቼን ፈጀ” ያለው እረኛ ታሪክ አይመጣባችሁም? ለቀልድ ያለው እውነት ሲሆን ረዳት ያጣው ልጅ ታሪክ። ዛሬ ሙሰኛ እና አሸባሪ የተባሉት ነጻ ሆነው እውነተኞቹ ሙሰኞችና አሸባሪዎች መያዝና ለፍርድ መቅረብ ሲጀምሩ ይኼ መንግሥት እንዴት ተአማኒነት ይኖረዋል? አልቅሶ ቢነግረንም አናምነውም ያኔ። በየራሳችን የኢሕአዴግ “ኮንስፒረሲ” እንደሆነ ስለምንገምት።

ለጥቂት ጥቅም ትልቁን አጥር መናድ
የፍየል ወጠጤው ይሻላል ስል የመግደል ጥሩ ኖሮት አይደለም። የደርጉ እንስሳዊ የጭካኔ በሽታ ከዚያው ዘመን ወደ ሌሎች ዘመኖች የማይተላለፍ ስለሆነ እንጂ። ሕግን የተንኮል ማከናወኛ ስናደርጋት ግን በሽታው በዚያ የማይቀር ተላላፊ እናደርገዋለን። በአገራችን ሕጋዊ ተቋማት ስም የሚፈጸሙ ተንኮሎች ተላላፊ በሽታ ይሆናሉ።

በግብጽ ሆስኒ ሙባረክ ወርደው መሐመድ ሙርሲ ቢመጡም የፖሊሱ ችካኔ፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እና ጭካኔ ያልተሻሻለው ለምንድነው? ሕጋዊ ተቋማቱ ሕገወጥነትን ስለተለማመዱና የተላላፊው በሽታ ተጠቂዎች ስለሆኑ ነው። ኢሕአዴግ ጊዜያዊ ድል ለማግኘት ትልልቅ አጥሮችን መናድን ሕጋዊ አድርጎታል። ዛሬ የተናዱትን የሕግ፣ የባህልና የሥነ ምግባር አጥሮች ዳግም መገንባት ቀላል አይሆንም። በጥቂት ዓመታት እንደተናዱት ማደሱም እንዲሁ በጥቂት ዓመታት የሚሳካ ላይሆን ይችላል። … ነገ ያስፈራል።

የመንግሥት ርምጃዎች ትክክል መሆን አለመሆናቸውን ማን ባጣራልን?
ከዚህ ችግር ልንተርፍ የምንችለው እና መንግሥትም ቢሆን የሚናገረው ነገር በርግጥም እውነት እንዳለው ሊያጣራለት የሚችለው እውነታ-አንጣሪ (Fact-checker ለሚለው የሚለውን ነው የተረጎምኩት) ሚዲያው እና መያዶች (መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች) ነበሩ። ከእነርሱ ጋር ደግሞ ዓይንና ናጫ፣ እሳትና ጭድ ሆነ። በደርግ ዘመን እንኳን ከመጥፋት የተረፉ መያዶች ከኢሕአዴግ ግን አልተረፉም። እነርሱን ባጠፋ መጠን ራሱን እየጎዳ መሆኑ ከቀን ቀን ግልጽ እየሆነ ነው። ስለ ሀገር እና ስለ መጪው ትውልድ ሲባል ኢሕአዴግ ያፈረሰውን መገንባት መጀመር አለበት። መንገዱንና ሕንጻውን መገንባት ብቻ አገር መገንባት አይሆንም። መንገዱና ሕንጻው ለኢትዮጵያዊው ይገነባለታል እንጂ እኛ ዜጎቹ ለመንገዱና ለሕንጻው አንኖርም። አለበለዚያ አዲስ ነገር በተከሰተ ቁጥር የራሳችንን መላ ምት እየሰጠን “ሕልምና የኛ አገር ፖለቲካ እንደፈቺው” ሆኖ ይቀራል።

ይቆየን፣ ያቆየን

1 Comment

  1. ስለባህርዳሩ ግድያ የፃፍከው ደህና የሚባል ቢሆንም፣ ስለሙስናው የፃፍከው ግን ብዙ ጉድለት አለበት፡፡ ለምሳሌ፦
    ፩. ዐቅም ማለት ሰውዬው በተመደቡበት ቦ ሃላፊነታቸውን በሚገባ ለመወጣት የሚያስችል አዕምሮአዊ ብቃት አለቸው ወይ ለማለት ነው እንጂ እንተ እነደምትለው ከጉለረበት ሥራ ጋር የሚዛመድ አይደለም።
    ፪ የደርጉ የፍየል ወጠጤ ይሻል ነበር ያልከው ለትዝብት ይዳርግኻል። ምንስ ቢሆን ምትክ የሌለውን የሰው ህይወት ያለምንም የፍርድቤት ውሳኔ መቅጠፍ እንዴት ነው የተሻለ የሚሆነው?

Comments are closed.

Share