መንግሥት ማኅበረ ቅዱሳንን በአክራሪነት አልፈረጅኹም አለ

  • እንደ ፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ሕዝብ ግንኙነት ሓላፊ ገለጻ በማኅበረ ቅዱሳን ውስጥ በአክራሪነት የተፈረጁት ‹አንዳንድ ግለሰቦች›÷ ‹‹አንዲት ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት›› የሚሉቱም ናቸው፡፡ ታዲያ ምን ይበሉ?!
  • ‹‹በይፋ አክራሪ ናችኹ ያለን አካል የለም፡፡›› /ተስፋዬ ቢኾነኝ፤ የማኅ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ/
  • ‹‹በጉዳዩ ላይ የጠራ ነገር የለም፤ ነገር ግን ጢስ አለ፡፡ ከጢሱ በስተጀርባ ያለው እሳት ይኹን እሳተ ገሞራ ባይታወቅም ለጊዜው ግን ማኅበሩን በተመለከተ ግልጽ የኾነ ነገር የለም።›› /ዲ.ን ዳንኤል ክብረት/

/ሰንደቅ፤ ፱ ቁጥር ፬፻፵፰፤ ሚያዝያ ፩ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም./

ዘሪሁን ሙሉጌታ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በ፲፱፻፺፬ ዓ.ም ለሦስተኛ ጊዜ ጸድቆ በተሰጠው መተዳደርያ ደንብ መሠረት የተቋቋመውን ማኅበረ ቅዱሳንን የኢትዮጵያ መንግሥት በአክራሪነት አለመፈረጁን አስታወቀ፤ ማኅበረ ቅዱሳንም በበኩሉ በይፋ በአክራሪነት የፈረጀው አካል እንደሌለ ገልጦአል።

በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊ አቶ አበበ ወርቁ እና የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ÷ ‹‹ማኅበረ ቅዱሳንን መንግሥት በአክራሪነት ፈርጆ ሊያፈርሰው ነው፤›› የሚለውን አስተያየት በተመለከተ ተጠይቀው እንደመለሱት፣ ማኅበሩ በአክራሪነት በይፋ መፈረጁን እንደማያውቁ ተናግረዋል።

‹‹የአክራሪነት ፍረጃው ጉዳይ ከምን አንጻር እንደተነሣ ግልጽ አይደለም። በየትኛውም መድረክ ላይ ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪ ነው ተብሎ የተነሣበት ኹኔታ የለም። ማኅበረ ቅዱሳንን የማሳደግ፣ የመደገፍ ሓላፊነት የራሱ የሃይማኖቱ ተቋም እንጂ የመንግሥት ጉዳይ አይደለም፤ የማፍረስ ዓላማ አለው የተባለውም ስሕተት ነው፤›› ያሉት አቶ አበበ፣ ‹‹መንግሥት ማኅበረ ቅዱሳንን ለማፍረስ ሕገ መንግሥቱም አይፈቀድለትም፤ የመንግሥትም ባሕርይ አይደለም፤›› ብለዋል።

‹‹የመንግሥት ፍላጎት ሃይማኖት ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን ተከትሎ በአግባቡ በዚህች ሀገር ላይ ሰላማዊ የአምልኮ ሥርዓት እንዲፈጸም እንጂ በሲኖዶሱ የተደራጀን ተቋም ሊያፈርስ የሚችልበት ሕገ መንግሥታዊ ሥልጣን የለውም፤›› ሲሉ አቶ አበበ ጨምረው ገልጸዋል።

‹‹መንግሥት ማኅበረ ቅዱሳንን ሊያፈርስ ነው፤›› የሚለው ጉዳይ የተለያየ መነሻ እንደሚኖረው የጠቀሱት የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊው፣ ጉዳዩ ከግንዛቤ እጥረት ወይም ሃይማኖትን ሽፋን በማድረግ የአክራሪነት አስተሳሰብን የማስፋፋት ፍላጎት ባላቸው አካላት የተነሣ ሊኾን እንደሚችል ገምተዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በቃሊቲ ማረሚያ ቤት በዛሬው እለት አንድ አስገራሚ የሰርግ ስነስርአት ተከናውኗል

‹‹ሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሃይማኖትን ሽፋን አድርጎ የሚካሔድን እንቅስቃሴ ሊሸከም የሚችል ትከሻ እንደሌለው በተደጋጋሚ አሳይቷል፤ ትልቅ ትግልም አካሒዷል፤›› ያሉት አቶ አበበ፣ የአሉባልታው ምንጭ አክራሪነትን በማስፈንና አክራሪነትን በመዋጋት መካከል ባለው ፍልሚያ የተቀሰቀሰ አሉባልታ ነው ብለዋል።

‹‹ጉዳዩ በሬ ወለደ ነው፤›› የሚሉት ሕዝብ ግንኙነቱ፤ ‹‹ከዚኹ አካባቢ[ከማኅበረ ቅዱሳን] አክራሪነትን ሊደግፉ የሚችሉ ግለሰቦች ሊኖሩ ይችላሉ፤›› ብለዋል። ‹‹የሰላማዊው አምልኮ ሥርዓት እየጠነከረ በሄደ ቁጥር የአክራሪው መድረክ እየጠበበ ስለሚመጣ ከሕዝብ ልንነጠል ነው በሚል ፍራቻ ልክ በሕዝበ-ሙስሊሙ አካባቢ የሐሰት ወሬ ተዘርቶ መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ ገብቷል እንዳሉት ኹሉ አሁን ደግሞ ወደ ሕዝበ-ክርስቲያኑ በማሰራጨት በባዶ ጩኸት ሕዝቡን ለማሳሳት የታለመ ነው፤›› ብለዋል።

‹‹መንግሥት ማኅበረ ቅዱሳን ላይ ምንም ዓይነት ስጋት የለውም፤›› ያሉት አቶ አበበ፣ ማኅበረ ቅዱሳን ከመንፈሳዊ ሥራው ጎን ለጎን እያካሄደ ያለው የልማት፣ የሰላም፣ የዴሞክራሲ ሥራ ስለሚሠራ፣ መንግሥት ከያዘው አጀንዳ ጋር ስለሚጣጣም በአጋዥነት ስለሚያየው ይደግፈዋል እንጂ አያፈርሰውም ብለዋል። ይህ ሲባል ግን እንደ ማንኛውም ተቋም የተቀደሰውን ዓላማ የሚያራክሱ፣ ማኅበሩን ወዳልኾነ አቅጣጫ የሚወስዱ ግለሰቦች አይኖሩም ማለት እንዳልኾነ ጠቅሰዋል። በተለይም ‹‹አንድ ሃይማኖት! አንድ ሀገር! አንድ ጥምቀት!›› እያሉ የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦች ሊኖሩ ይችላሉ። እንደዚህ ዓይነቶቹ ግለሰቦች በአክራሪነት ሊፈረጁ ይችላሉ ብለዋል።

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ ስለ ጉዳዩ ተጠይቀው፣ ‹‹ማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በቅዱስ ሲኖዶስ ዕውቅና አግኝቶ መተዳደርያ ደንብ ተቀርፆለት የሚተዳደር ማኅበር እንደኾነ አስታውሰው፤ ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያኗ ሥር የሚያገለግል ማኅበር በመኾኑ ከአክራሪነት ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም፤›› ብለዋል።

‹‹ክርስትናችን አክራሪነትን የሚያስተምር አይደለም። የማኅበሩም አገልግሎት ሙሉ በሙሉ ከአክራሪነት ጋር ምንም የሚያገናኝ ሥራ የለውም። የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እየሰጠ ያለ ማኅበር ነው፤ በጉዳዩም ላይ በይፋ የደረሰን የተጻፈ፣ በቃልም የተባልነው ነገር የለም። ካለም ልንወያይ፣ አስፈላጊውን ነገር ልንተባበር እንችላለን፤›› ሲሉ አቶ ተስፋዬ ከአክራሪነት ፍረጃ ጋር በተያያዘ በይፋ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ተናግረዋል፤ ማኅበሩም የተለመደ አገልግሎቱን እየሰጠ እንደሚገኝም ጨምረው ገልጸዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወላይታ ላይ ሰማያዊ ፓርቲ ቅስቀሳ እንዳያደርግ ተከለከለ

ማኅበሩን በተመለከተ እየተነሣ ያለው የፍረጃ ሐሳብ ምንጩ ምን እንደኾነ አናውቅም ያሉት አቶ ተስፋዬ፣ ምንጩን ሊያውቁ ይችላሉ ብለን የምንገምተው ሚዲያዎቹ ናቸው። እኛ ምንም የምናውቀው ነገር የለም። እንደማንኛውም ጉዳዩን እንደሚከታተል አካል ነው የምናየው ብለዋል።

ከዚህ ቀደም ከአክራሪነት ጋር በተያያዘ በወጡ ሰነዶች ላይ ማኅበሩ መጠቀሱን በተመለከተ አቶ ተስፋዬ ተጠይቀው፣ በማኅበር ደረጃ በይፋ በግልጽ የተጠቀሰ ነገር እንደሌለ ተናግረዋል። ማኅበሩን በቀጥታ የሚመለከት በደብዳቤም ኾነ በሌላ መንገድ የተባለ ነገር የለም ብለዋል።

ዲያቆን ዳንኤል ክብረት

አንዳንድ የማኅበሩ ምንጮች በመጋቢት ፳፻፭ ዓ.ም. ‹‹የፀረ አክራሪነት ትግል የወቅቱ ኹኔታና ቀጣይ አቅጣጫዎች››*በሚል ርእስ በተዘጋጀ ሰነድ ላይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስትና መድረክ የአክራሪነት አደጋ ያለው በሃይማኖት ሽፋን በሚንቀሳቀሱና የከሰሩ ፖሊቲከኞች ምሽግ በመኾን ያገለግላሉ በተባሉ ማኅበራት ውስጥ ነው መባሉ፤ በቅርቡም በሐዋሳ ከተማ‹‹አክራሪነትና ጽንፈኝነት ችግሮቹና መፍትሔዎቹ››**በሚል ርእስ በቀረበ ጽሑፍ፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የአክራሪዎች ምሽግ የኾኑት የወጣት ማኅበራት አደረጃጀቶች መኾናቸውንና እኒህም ማኅበራት በሃይማኖት ተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች ይኹንታ ያላቸው ከመኾኑም በላይ ማኅበራቱ ከጽንፈኛ የፖለቲካ ኃይሎች ጋራ ግንኙነት እንዳላቸው መጠቀሱእንዲሁም ከፓትርያርክ ምርጫው፣ ከቀድሞ ፓትርያርክ ጋር ዕርቅ ለመፍጠር የተደረገውን ጥረት ማኅበሩን ከከሰሩ ፖለቲከኞች ጋር ለማስተሳሰር መሞከሩና ሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮች የማኅበሩ አባላት መንግሥትን በጥርጣሬ እንዲያዩት መደረጉን ይገልጻሉ።

በማኅበረ ቅዱሳን ውስጥ ንቁ ተሳትፎ ከነበራቸው አመራሮች አንዱ የነበሩት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በግል ስለ ኹኔታው ተጠይቀው፣በጉዳዩ ላይ የጠራ ነገር አለመኖሩን፣ ነገር ግን ጢስ መኖሩን ገልጸዋል። ከጢሱ በስተጀርባ ያለው እሳት ይኹን እሳተ ገሞራ ባይታወቅም፤ ለጊዜው ግን ማኅበሩን በተመለከተ ግልጽ የኾነ ነገር የለም ብለዋል።

በግላቸው መንግሥት ማኅበረ ቅዱሳንን በማፍረስ ስሕተት ይሠራል ብለው እንደማይገምቱና ምናልባትም ለማኅበሩ ያሰቡ ሰዎች መስለው ለማኅበሩ የተሳሳተ መረጃ ያቀበሉ እንዲሁም በመንግሥት በኩል ማኅበሩን በተመለከተ አፍራሽ አቋም ሊያንጸባርቁ የሚችሉ አንዳንድ ግለሰብ ባለሥልጣናት ሊኖሩ እንደሚችሉ ያላቸውን ጥርጣሬ ተናግረዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  Hiber Radio: "የጎንደሩ የተቃውሞ ሰልፍ ለመሳተፍ ለሱዳን መሬታችን ከተሰጠበት አካባቢ ያሉ ጉዳዩን የሚያውቁ በርካቶች እንሳተፋለን ብለዋል"

ማኅበረ ቅዱሳን በ፲፱፻፹፬ ዓ.ም በዋናነት በእምነቱ ተከታዮች የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የተመሠረተ ሲኾን፤ የአባልነት መዋጮ በመክፈልና ከፍተኛ አገልግሎት በማበርከት ተሳትፎ ያላቸው ከ፴ ሺሕ በላይ አባላትና ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ተባባሪ አባላት አሉት፤ ማኅበሩ በስብከተ ወንጌል ረገድ ከሚያከናውነው ዓበይት መንፈሳዊ አገልግሎት ባሻገር ገዳማትና የገጠር አብያተ ክርቲስያናት በልማት ራሳቸውን እንዲችሉ፣ የአብነት ት/ቤቶች እንዲጠናከሩና እንዲጎለብቱ ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት ላይ የሚገኝ ማኅበር ነው።

>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>>> 

በኦርቶዶክስ ክርስትና ሃይማኖት ሽፋን የሚንቀሳቀሱ ማኅበራት የአክራሪነትና የከሰሩ ፖሊቲከኞች ምሽግ በመኾን መገልገል ከጀመሩ ውሎ አድሯል፡፡ ከ፮ው ፓትርያርክ ምርጫ ጋራ በማያያዝ የየራሳቸው ፍላጎት የሚያሳኩ ውሳኔዎችን ለማስተላለፍና አሜሪካ ከሚገኘው ስደተኛው ሲኖዶስ ከሚባለው ቡድን ጋራ የዕርቅ ኹኔታ በሚል እንቅስቃሴዎችን ያደርጋሉ፡፡

በዚኽ በራሳቸው በፈጠሩት ትርምስ ውስጥ መንግሥት እጁን አስገብቷል ወዘተ እያሉ የኦርቶዶክስ አማኞችን ለማወናበድ ይሞክራሉ፡፡ በራሳችንም እንደሌላው ኃይል ሰልፍ ልንወጣ ይገባል በሚል የዐመፅና የሁከት ቅስቀሳ ለማድረግ ይፈልጋሉ፡፡

በተለይም ሰሜን አሜሪካ የሚገኘው ራሱን ስደተኛው ሲኖዶስ ብሎ የሚጠራው አካል ሰላማዊ፣ አሳታፊና ግልጽ ኾኖ የተካሔደውን የ፮ው ፓትርያርክ ምርጫ አውግዘናል በማለት መግለጫ ሲሰጥ የሰነበተ ቢኾንም የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዩ ሕዝብ ጆሮውን ሳይሰጠው አልፏል፡፡ በሒደትም ይህ ኃይል ሰላም እንዳልኾነ፣ የሰላም ጥረቶችን በሙሉ ሲያሰናክል የሰነበተ፣ ሃይማኖታዊ እንቅስቃሴ ሳይኾን የከሰሩ ፖሊቲከኞች እንቅስቃሴ መኾኑን ግንዛቤ ይዟል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን ውስጥ የመሸጉ የትምክህት ኃይሎች ጽንፈኛ የፖሊቲካ ኃይሎች አካል በመኾን በጋዜጣና በመጽሔት ሕዝባችንን ለዐመፅና ሁከት ለማነሣሣት ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡ በስደተኛው ሲኖዶስ በመሸፈንም እያንዳንዱ ሌላ ቀን ኢትዮጵያ የምትባል አገር የሌለች አስመስለው የግንቦት ሰባትን ከበሮ ሲመቱ ከርመዋል፡፡ (የፀረ አክራሪነት ትግል የወቅቱ ኹኔታና ቀጣይ አቅጣጫዎች፤ መጋቢት ፳፻፭ ዓ.ም.)

**

1 Comment

  1. my comment is not for this but somebody help us .we need a help some body help refuge in Kenya .we r Ethiopian we can’t go back to home but know Kenyan police reap and Stoll everything we have we t torch there …plz help

Comments are closed.

Share