የመለስ መታሰቢያ ተቋም (Foundation) የደቀነብን አደጋዎች! – ክፍል 1 – ከግርማ ሞገስ

ግርማ ሞገስ (girma.moges@yahoo.com)

ይኽ ጽሑፍ አራት ክፍሎች ይኖሩታል። የመጀመሪያው ክፍል ከአሚሪካ ቀድሞ ፕሬዘዳንቶች መታሰቢያ ተቋሞች ልምዶች ለመውሰድ ጥናት ያደርጋል። ሁለተኛው ክፍል የአቶ መለስ ቅርስ (Legacy) ኮሚቴ፣ ህውሃት እና እንድሪያስ እሸቴ (ፕሮፌሰር) ስለ አቶ መለስ አገር ወዳድነት፣ ፓን-አፍሪካዊነት፣ ሰላም ወዳድነት እና ሰላም አምጭነት፣ የፍትህ፣ የጥሩ አስተዳደር እና የዲሞክራሲ አባትነት፣ የልማት ጀግናነት የሚያሰራጩትን ፕሮፖጋንዳ ነጥብ በነጥብ በማንሳት መልስ ይሰጣል። ሶስተኛው ክፍል ስለ አቶ መለስ መታሰቢያ ተቋም አስፈላጊነት የታወጀው መንግስታዊ አዋጅ ዲሞክራሲያ አለመሆን፣ ስለ ስመ-ጥሩዎቹ የአነስታይን፣ የኖቤል እና ጆን ኦፍ ኬኔዲ መታሰቢያ ተቋሞች አጫጨር ማስታወሻዎች እና የሚለግሱን ትምህርቶች፣ በወይዘሮ አዜብ ፕሬዘዳንትነት ስለሚመራው የአቶ መለስ መታሰቢያ ተቋም አስፈሪ ግቦች፣ ስለ አቶ መለስ መታሰቢያ ተቋም አስተዳዳሪ ቦርድ አባላት አይነት እና አስደንጋጭነት፣ ጥቂት ምክሮች ለወይዘሮ አዜብ፣ የአቶ መለስ መታሰቢያ ተቋም ገንዘብ ምንጭ ህገ-ወጥነት እና ታክስ ከፋዮች ወደፊት ወይዘሮ አዜብን ህግ ፊት ሊያቀርቡ እንደሚችሉ የተነትናል። አራተኛው ክፍል “ምን ይበጃል?” የሚለው ሲሆን ቀደም ብለው የተነበቡትን ሶስት ክፍሎች መሰረት በማድረግ ጸሐፊው ይበጃሉ የሚላቸውን ተግባሮች ለውይይት ያቀርባል። [መልካም ንባብ!]

ክፍል አንድ (ከአራት ክፍሎች)፥ የአሜሪካ ቀድሞ ፕሬዘዳንቶች መታሰቢያ ተቋሞች

የአሜሪካው የቀድሞ ፕሬዘዳንት የአቶ ቡሽ (ትንሹ) ቤተ-መጽሐፍት እና ቤተ-መዘክር ያካተተ የመታሰቢያ ተቋሙ ምረቃ ስነስርዓት በዳላስ ከተማ (ቴክሳስ) ተፈጸመ። ዕለቱ ሐሙስ ሚያዚያ 17 ቀን 2005 (25 April, 2013) ዓመተ ምህረት። ሲ.ኤን.ኤን. (CNN) የምረቃውን ፕሮግራም ማሳየት ሲጀምር እንደአጋጣሚ ቴሌቪዥን አጠገብ ነበርኩ። በፕሮግራሙ ላይ አራቱ የቀድሞ ፕሬዘዳንቶች፣ ካርተር፣ ቡሽ (ትልቁ)፣ ክሊንተን፣ ቡሽ (ትንሹ) እና ፕሬዘዳንት ኦባማ በመታሰቢያ ተቋሙ ምረቃ ስነስርዓት ላይ ነበሩ። በእንደዚኽ አይነት ፕሮግራም አምስት ፕሬዘዳንቶችን በአንድ ጊዜ ማግኘት ሁልጊዜ የሚሆን ባለመሆኑ እና ስለ አቶ መለስ መታሰቢያ ተቋም በመጻፍ ላይ ስለነበርኩ ፕሮግራሙን አፍ ተልብ ሆኜ ተከታተልኩ። እንደሚታወቀው ከእነዚህ አምስት ፕሬዘዳንቶች ውስጥ ቡሽ (ትልቁ እና ትንሹ) ረፓብሊካን ሲሆኑ የቀሩት ሶስቱ ዲሞክራቶች ናቸው። ስለዚህ በመካከላቸው የፖሊሲ ልዩነቶች እንደሚኖሩ ግልጽ ነው። ይሁን እንጂ በምረቃው ስነስርዓት ላይ ባደረጉዋቸው ንግግሮች ውስጥ በግልጽ ጎልቶ ይታይ የነበረው ልዩነታቸው ሳይሆን ተመሳሳይነታቸው ነበር። ሁሉም አሜሪካዊ መሆናቸው። በፖለቲካም። በተጨማሪ ከንግግሮቻቸው ውስጥ የሚከተሉትን ታዘብኩ፥ (1) አምስቱም ፕሬዘዳንቶች ስለዲሞክራሲ ሲያወሩ ዲሞክራሲ በሚለው ቃል ላይ ‘አብዮታዊ’ የሚል አጭበርባሪ ቅራቅንቦ አይለጥፉም ነበር። ለእነሱ ዲሞክራሲ አንድ እና አንድ አይነት ብቻ ነው። (2) መጠኑ ቢለያይም እያንዳንዳቸው የፖለቲካ እምነታቸውን በአገራቸው እና በህዝባቸው ላይ ተፈጻሚ በማድረግ የአገራቸውን ታሪክ አቅጣጫ ቀይረዋል። ይኽን ያደረጉት ግን ህዝቡ በነፃ ምርጫ ይሁንታውን ከሰጣቸው በኋላ ነው። የመንግስት ስልጣን የህዝብ መሆኑን በሚያረጋግጥ ነፃ ምርጫ ማለት ነው። አምባገነኖቹ መንግስቱ ኃይለማሪያም በመፈንቅለ መንግስት እና መለስ ዜናዊ ደግሞ በእርስ በርስ ጦርነት በኢትዮጵያ ስልጣን እንደያዙ እና የኢትዮጵያን ታሪክ አቅጣጫ አደበላልቀውት እንደሄዱ አስታወሱኝ። (3) የአሜሪካን መንግስትን ወክሎ በፕሮግራሙ ላይ የተገኘው ኦባማ ስለ ቡሽ (ትንሹ) መታሰቢያ ተቋም በፕሮግራሙ ላይ ከሚሰማው በስተቀር ቀደም ብሎ የሚያውቀው አንድም ነገር እንደሌለ ታዘብኩኝ። የቡሽ (ትንሹ) መታሰቢያ ተቋም ምስረታ በእሱ፣ በሚስቱ፣ ቤተሰቦቹ እና በደጋፊዎች እንደተጀመረ፣ ህንጻው የተገነባበትን መሬት እንዴት እንዳገኘ? ህንጻውን ለመገንባት 350 ሺ ያህል ደጋፊ ግብር ከፋይ አሜሪካውያን በፈቃዳቸው ከኪሳቸው እንደረዱት፣ መታሰቢያ ተቋሙን የሚመሩት እሱ እና ባለቤቱ ከመንግስት ነፃ ከሆነ ሙያተኛ ድርጅት ጋር ተቀናብረው እንደሆነ፣ ተቋሙ ትርፍ ከመስራት ነፃ እንደሆነ እና ሌሎች ጉዳዮችን በሙሉ ሲያብራራ ለእኔ አዲስ ዜና የነበረውን ያህል ለቀሩት የቀድሞ ፕረዘዳንቶች እና መንግስትን ወክሎ በፕሮግራሙ ላይ ለተገኘው ለወቅቱ ፕሬዘዳንት ኦባማም አዲስ ዜና ነበር። ስለዚህ የአሜሪካ መንግስት ከፕሬዘዳንቶች መታሰቢያ ተቋም ምስረታ ጋር ምንም ግንኙነት እንደሌለው በግልጽ አየሁኝ።

ፕረዘዳንቱ በአገሩ እና በለም አቀፍ ደረጃ ለህዝብ ታላላቅ ስራዎች ያከናወነ እና ከአገሩ አልፎ በአለም አቀፍ ያሉ ታሪክ ጸሐፊዎች ሰፋፊ ምዕራፎች ቢጽፉለትም መታሰቢያ ተቋም የራሱ የፕሬዘዳንቱ፣ የቤተሰቡ፣ የራሱ ፓርቲ፣ የደጋፊዎች የግል ጉዳይ ሲሆን መታሰቢያ ተቋሙን መገንቢያ ገንዘብ ምንጭም መንግስት ሳይሆን ደጋፊዎቹ ከግል ኪሳቸው በለገሱት ገንዘብ ነበር። ይኽን ነጥብ በአሜሪካ እና በአለም አቀፍ ደረጃ ዛሬም ታዋቂ እና ተወዳጅ የሆነውን የፕሬዘዳንት ሩዝቬልትን አጭር ማስታወሻ እንድንመለከት ያስገድደናል።
ፕሬዘዳንት ፍራንክሊን ዲ. ሩዝቬልት (1933-1945) የአሜሪካ ፕረዜዳንት ሲሆን አሜሪካ ትልቅ ችግር ውስጥ ገብታ ስራ ጠፋ። ህዝብ የሚበላው ጠፍቶ የሩዝቬልት መንግስት ህዝቡን ማብላት ጀመረ። ረሃብ እና ጤና ማጣት እጅግ በበረታባቸው በርካታ የአሜሪካ ከተሞች መንግስት የምግብ ማብሰያ ካምፖች መስርቶ ህዝቡን በየቀኑ መመገብ ጀመረ። ሩዝቬልት በአንድ እጁ ህዝቡን ከሞት የማትረፍ ትግል እያደረገ በዚያኑ ጊዜ ብዙ ፕሮጀክቶች ወጥኖ ፕሮክቶቹ ሲጀመሩ የህዝብ መመገቡ ስራ እዚያው ፕሮጀክቶቹ ባሉበት አካባቢ እንዲቀጥል አደረገ። ከወጠናቸው ፕሮጀክቶች ውስጥ አንደኛው ብዙ ያልተገሩ ጅረቶችን የሚገሩ የኤሊክትሪክ ማመንጫ ግድቦች መገንባት፣ የኤሊክትሪክ ኃይል ማመንጨት፣ ይኽን የኤሊክትሪክ ኃይል በመጠቀም ለህይወት የማይመቹ ግዛቶች መብራት እንዲያገኙ፣ የአየር ጸባያቸው እንዲቀየር፣ የእርሻ ስራ እንዲጀመርባቸው እና ህዝብ እንዲሰፍርባቸው ማድረግ ነበር። ይኽ ፕሮጀክት ብዙ ስራ ፈጠረ። በዚኽ ረገድ አብዛኛዎቹ ፕሮጀክቶች ተሳኩ። የዛሬዋ ዋሽንግተን ክፍለ አገር (ሲያትል) የታላቁ ኩሌ ግድብ (Grand Coulee Dam) ውጤት ነች። በረሃማው የካሊፎርኒያ ግዛት ልማት የሁቨር ግድብ (Hoover Dam) ውጤት ነው። የቴናሲ (Tennessee) ክፍለ አገር ልማት የኖሪስ ግድብ (Norris Dam) ውጤት ነው። እነዚህ ሶስቱ ታላላቅ ያልተገሩ ጅረቶችን ገርተው ለሰው ልጅ ትልቅ ጥቅም የሰጡ ግድቦች ሲሆኑ በሌሎች ግዛቶችም የተለያዩ የልማት ስራዎች ተሰርተዋል። ሁለተኛው ፕሮጀክት ደግሞ ክፍለ አገሮችን የሚያገናኙ ትላልቅ ጎዳናዎች መገንባት ሲሆን ይኽ ፕሮጀክትም ለህዝቡ ብዙ ስራ ከፈተ። ሶስተኛው ሩዝቬልት የፈጸመው ታሪካዊ ተግባር ደግሞ በአገሩ ልማት እና ግንባታን በመምራት ላይ ሳለ በአለም አቀፍ መድረክ አሜርካን በሁለተኛው አለም ጦርነት መምራት ነበር። ጦርነት ውስጥ የገባው ወዶ ሳይሆን ተገዶ ነበር። አሚሪካን በማልማት ላይ ሳለ ሁለተኛው አለም ጦርነት ተቀሰቀሰ። ጀርመን አውሮፓን መውረር ስትጀምር ጃፓን በአካባቢዋ ያሉትን አገሮች ከወረረች በኋል አሜሪካን በአየር ደበደበች። የጃፓንን ቦንብ ድብደባ ተከትሎ ሩዝቬልት “ምንም ነገር አንፈራም። የምንፈርው ነገር ቢኖር እራሱን ፍርሃትን ብቻ ነው” የሚል ምላሽ በአደባባይ ሰጠ። እስከዛሬ ድረስ ዝነኛ ጥቅስ ነች። የሆነው ሆኖ ሩዝቬልት ፓርላማውን አስፈቅዶ አሜሪካን ይዞ ሁለተኛውን አለም ጦርነት ተቀላቀለ። ትረካዬን ላሳጥር። ሩዝቬልት በአገሩ ውስጥ የመራውን ልማት እና አገር ግንባታ እንዲሁም በአለም አቀፍ ደረጃ የመራውን ሁለተኛ አለም ጦርነት በድል ፈጸመ። በሙያዬ የኤሊክትሪክ ኃይል እንጂነር በመሆኔ የማወቅ ጉጉት ገፋፍቶኝ ዝነኞዎቹን የሩዝቬልት የኤሊክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድቦች እና ከግድቦቹ የሚገኘው የኤሊክትሪክ ኃይል የሚሰጠውን ጥቅም ለማየት በአሜሪካ ተጓጉዣለሁ። የኖሪስ ግድብ በቴናሲ (Tennessee) እና የሁቨር ግድብን በካሊፎርኒያ በረኃ ላይ የፈጠሩትን ልማቶች ተዟዙሬ በአይኔ አይቻለሁ። የታላቁ ኩሌ ግድብ ለዋሽንግተን ክፍለ አገር የሰጠውን ልማት ለማየት እድሉን አላገኘሁም። ግድቡን እና የኤሊክትሪክ ኃይል ማመንጫ ጣቢያውን ግን በቪዲዮ አይቻለሁ። ወደፊት በአካል የማየት እቅድ አለኝ።
ይኽ ፕሬዘዳንት በአሜሪካ ታሪክ ለመጀመሪያ እና ለመጨረሻ ጊዜ (እስከዚኽ ድረስ) የአሜሪካ ህዝብ እራሱ ህገ-መንግስቱን ጥሶ ለሶስተኛ ዘመን (ለ12 አመቶች) አሜሪካን በፕሬዘዳንትነት እንዲመራ ያደረገው ተወዳጅ ፕሬዘዳንት ነው። ፕሬዘዳንት ፍራንክሊን ዲ. ሩዝቬልት (1933-1945) ቢሮው ውስጥ ስራ ላይ ሳለ ሞተ። ለምግብ ሊጠሩት ቢሮው ሲገቡ በወንበር ላይ ቁጭ ብሎ ያገኙት እሬሳውን ነበር። ለዚህ የአገሩን ህዝብ ፍቅር እና አክብሮት ላገኘው የቀድሞ ፕሬዘዳንትም ቢሆን መታሰቢያ ተቋም በመንግስት አዋጅ አልተገነባለትም። አቶ መለስ ከሩዝቬልት ተርታ የሚቀመጥ ሰው አይደለም።
‘በአብዮታዊ ዲሞክራሲ’ አገሮች ካልሆነ በስተቀር በዲሞክራሲ አገሮች መንግስት የመሪዎች መታሰቢያ ህንጻ እወጃ እና ግንባታ ውስጥ አይገባም ማለት ነው። መንግስት የአጠቃላይ አሜሪካ ግብር ከፋይ ህዝብ አስተዳዳሪ እንጂ መታሰቢያ ተቋም የሚሰራለት ፕሬዘዳንት ደጋፊዎች ብቻ አስተዳዳሪ ስላልሆነ ከመታሰቢያ ተቋም መንግስት እራሱን ነፃ ማድረግ አለበት ማለት ነው። ስለዚኽ መንግስት ማለት የፖለቲካ ፓርቲ ማለት እንዳልሆነ የፖለቲካ ፓርቲ ማለትም መንግስት ማለት እንዳልሆነ እንዲሁም በመንግስት እና በፖለቲካ ፓርቲ መካከል ግልጽ የሆነ ልዩነት መኖሩን ማወቅ በአምስቱም ፕረዘዳንቶች ዘንድ የሰረጸ ልማድ መሆኑን በግልጽ ታዘብኩኝ። የነበረኝ እምነት ተጠናከረ። የአቶ መለስን መታሰቢያ ተቋም አስመልክቶ በጀመርኩት ጽሑፍ ውስጥ ስከተላቸው የነበሩት መርሆዎች ትክክል መሆናቸውን ቢያንስ እነዚህ አምስት ፕሬዘዳንቶች አረጋገጡልኝ ማለት ነው።
የሆነው ሆኖ የመጨረሻ ተናጋሪ የነበረው ቡሽ (ትንሹ) በንግግሩ መገባደጃ ግድም ሰለ አሜሪካ እና ኢራቅ ጦርነት በንግግሩ ጠቀሰ እና የጦርነት ፕሬዘዳንት መሆን ግን ምኞቱ እንዳልነበር ተናገረ። ለጥቆ “ህዝባችንን እና አገራችንን የተለያዩ እንቅፋቶች ቢገጥሙዋቸውም የአገራችን ብሩህ ቀኖች ገና ከፊታችን ስለመሆናቸው ያለኝ እምነት የማይናጋ ነው” በማለት ላይ ሳለ ድምጹ ተቀየረ። የአገር ወዳድነት ስሜቱ መጥቶበት ይሁን ወይንም በስልጣን ላይ ሳለ የጦር ጊዜ ፕሬዘዳንት በመሆን በአሚሪካ እና በኢራቅ ታሪክ ላይ ያስከተለው የታሪክ አቅጣጫ ለውጥ አስዝኖት ግልጽ አይደለም። ድምጹን እና አይኖቹን መፈታተን የጀመረው ስሜቱ ሳያሸንፈው ንግግሩን ቋጭቶ አይኖቹን በእጆቹ ጠረገ። የንግግር ወለሉን ለቆ ወደመቀመጫው አመራ። ባለቤቱ ሎራ ጎን ሊቀመጥ። በአጠገቡ የነበሩት አራት ፕሬዘዳንቶች ከነቤተሰባቸው እና በመታሰቢያ ተቋሙ ምርቃት ላይ እንዲገኝ የተጋበዘው ህዝብ በሙሉ ጸጥ አለ። ቡሽ (ትንሹ) ፊቱ ላይ ፈገግታ ለማስቀመጥ እየታገለ በአንድ እጁ አይኖቹን መጥረጉን ቀጠለ።
ክሊንተን ቀደም ብሎ በተራው ንግግር እያደረገ ሳለ ለፈገግታ ከማገልገልም ባሻገር አንድ ለጥናታችን ጠቃሚ የሆነ ቁምነገር እንደ ቀልድ አድርጎ ተናግሮ ነበር። እሱም፥ “ከስልጣን በኋላ የቀድሞ ፕረዘዳንቶች ፈተና መታሰቢያ ተቋሞች በመገንባት ታሪካቸውን እንደገና ለመጻፍ መታገል ነው እያልኩ ለኦባማ ሁልጊዜ እነግረዋለሁ” የሚል ነበር። ከፊል ያህሉ ተሰብሳቢ ስቆለታል። እርግጥ ነው አንዳንድ የቀድሞ ፕሬዘዳንቶች ወይንም ጠቅላይ ሚንስትሮች ከሞቱ በኋላ መጪ ትውልድ ጥሩ ሰው አድርጎ እንዲያስባቸው መመኘታቸው አይቀርም። ያን ማለቱ ነው። ያ እንዳይሆን ከዚህ በኋላ የቡሽ (ትንሹ) መታሰቢያ ተቋም የአሜሪካ ህዝብ ንብረት በመሆኑ ማንኛውም ጉብኚ ዜጋ የፈለገውን የመመርመር ህጋዊ መብት ይኖረዋል። በመሆኑም ቀጥሎ መሆን ያለበት በመታሰቢያ ተቋሙ ቤተ-መጽሐፍት እና ቤተ-መዘክር ውስጥ ለህዝብ ይፋ የተደረጉ እና ያልተደረጉ ሰነዶችን ታሪክ ጸሐፊዎች እና ተመራማሪዎች በጥልቀት እና በስፋት መመርመር ነው። ከምርምራቸው እና ከጥናታቸው በኋላ እነዚህ ሰዎች በዜና አውታሮች አማካኝነት ወይንም መጽሐፍት በመጻፍ ከህዝባቸው ጋር ውይይት ሊከፍቱ ይችላሉ። ይከፍታሉም። ታሪክም ዳኝነቷን ትሰጣለች።
እርግጥ የአቶ መለስ መታሰቢያ ተቋም ውጥን ኢላማ ያደረገው የአቶ መለስን ታሪክ አሻሽሎ ለመጻፍ ይሁን ወይንም በስኮላርሽፕ ስም ድጋፍ በመስጠት ብዛት ያላቸው ‘አብዮታዊ ዲሞክራሲ” ካድሬዎች አምርቶ አቶ መለስ በህይወት ሳለ በመገንጠል፣ በባህር በር፣ በነጻ ምርጫ፣ በዲሞክራሲ፣ በሰባዊ መብቶች እና በመሳሰሉ ጉዳዮች ዙሪያ ሲያራምዳቸው የነበሩትን አምባገነናዊ ፖሊሲዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ለማድረግ ይሁን ግልጽ አይደለም። አዜብን ጨምሮ የመለስ ደቀመዝሙሮች የመታሰቢያ ተቋሙ ዋንኛ ግብ የአቶ መለስን ራዕይ ከትውልድ ትውልድ ማስተላለፍ እና ማስረጽ ነው ማለታቸው በሰፊው ተዘግቧል።
ያም ሆነ ይኽ በብእዴኑ በአቶ አዲሱ ለገሰ እና በህውሃቱ በአቶ ካሳ ተ/ብርሃን የሚመራው የአቶ መለስ ቅርስ (Legacy) ኮሚቴ ሰብሳቢዎች እና የአቶ መለስ አማካሪ የነበረው እንድሪያስ እሸቴ (ፕሮፈሰር) በአገር ውስጥ በጉባኤዎች እና በዜና ማሰራጫዎች (ኢቲቪ እና ሬዲዮኖች) የአቶ መለስ በሳል አመራር ለኢትዮጵያ እና ለአለም ህዝብ ያበረከታቸውን ውለታዎች በማተት ህዝብ ማጭበርበር ከጀመሩ ውለው አድረዋል። ክፍል አንድ ይኼን ፕሮፖጋንዳቸውን ነጥብ በነጥብ መርምሮ አጭበርባሪነቱን ለአንባቢ ያቀርባል።
[ክፍል ሁለት ይቀጥላል]

ተጨማሪ ያንብቡ:  ብርቱ ሰው! (The Iron Man) - (ከተመስገን ደሳለኝ)

 

3 Comments

  1. 1ኛ)የሆነው ሆኖ የመጨረሻ ተናጋሪ የነበረው ቡሽ (ትንሹ) በንግግሩ መገባደጃ ግድም ሰለ አሜሪካ እና ኢራቅ ጦርነት በንግግሩ ጠቀሰ እና የጦርነት ፕሬዘዳንት መሆን ግን ምኞቱ እንዳልነበር ተናገረ። ለጥቆ “ህዝባችንን እና አገራችንን የተለያዩ እንቅፋቶች ቢገጥሙዋቸውም የአገራችን ብሩህ ቀኖች ገና ከፊታችን ስለመሆናቸው ያለኝ እምነት የማይናጋ ነው” በማለት ላይ ሳለ ድምጹ ተቀየረ። የአገር ወዳድነት ስሜቱ መጥቶበት ይሁን ወይንም በስልጣን ላይ ሳለ የጦር ጊዜ ፕሬዘዳንት በመሆን በአሚሪካ እና በኢራቅ ታሪክ ላይ ያስከተለው የታሪክ አቅጣጫ ለውጥ አስዝኖት ግልጽ አይደለም። ድምጹን እና አይኖቹን መፈታተን የጀመረው ስሜቱ ሳያሸንፈው ንግግሩን ቋጭቶ አይኖቹን በእጆቹ ጠረገ። የንግግር ወለሉን ለቆ ወደመቀመጫው አመራ። ባለቤቱ ሎራ ጎን ሊቀመጥ። በአጠገቡ የነበሩት አራት ፕሬዘዳንቶች ከነቤተሰባቸው እና በመታሰቢያ ተቋሙ ምርቃት ላይ እንዲገኝ የተጋበዘው ህዝብ በሙሉ ጸጥ አለ። ቡሽ (ትንሹ) ፊቱ ላይ ፈገግታ ለማስቀመጥ እየታገለ በአንድ እጁ አይኖቹን መጥረጉን ቀጠለ።

    2ኛ)ክሊንተን ቀደም ብሎ በተራው ንግግር እያደረገ ሳለ ለፈገግታ ከማገልገልም ባሻገር አንድ ለጥናታችን ጠቃሚ የሆነ ቁምነገር እንደ ቀልድ አድርጎ ተናግሮ ነበር። እሱም፥ “ከስልጣን በኋላ የቀድሞ ፕረዘዳንቶች ፈተና መታሰቢያ ተቋሞች በመገንባት ታሪካቸውን እንደገና ለመጻፍ መታገል ነው እያልኩ ለኦባማ ሁልጊዜ እነግረዋለሁ” የሚል ነበር።

    ***********************************************
    በውጪ ከሚታየው ከአካላዊ ጦርነት በበለጠም የዘመናችን እጅግ ዋናው ፈታኝ ጦርነት በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለውና ይህንንም ተከትሎ ጭምር ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት ነው፡፡በውጪ የሚታየው አካላዊ ጦርነት ቅድሚያ ከውስጥ ያለው በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለው ውስጣዊ ጦርነት ቀጣይ ማስተንፈሻ ወይንም መገለጫ ወይንም መቋጫ ነገር ነው፡፡ይህንንም ተከትሎ ሀሰትንና እውነትን ለማምታታም ሆነ ለማጥራት ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት የዘመናችን ፈታኝ ነገር ነው፡፡ከቡሽም ሆነ ከመለስ በስተጀርባ ያለው ነገር ዲሞክራሲ ከሚለው ዘመነኛ ቃል ጋርና እኛም ለዚህ ዲሞክራሲ ለሚባል ነገር ካለን ጥራዝ-ነጠቅ እይታ አንፃር ሲታይ ከውጪ በሚታየው በቅርፅ ደረጃ የሚታወቀው አይነት የተወሰነ ልዩነት ቢኖረውም በመሰረታዊ የእውነት ይዘት ግን ያው ተመሳሳይነት ያለው ነገር ነው፡፡ተመሳሳይነቱም በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለው ጦርነትና ይህንንም ተከትሎ ጭምር ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት መገለጫ መሆኑ ነው፡፡ፈረንጆች እንደሚሉት The first casualty of war is truth ሲባል በዘመናችን የሰላም የፍቅር የብልፅግና ፀር የሆነው አጥፊው ጦርነት ከመታወጁ በፊት ይህንን አላስፋላጊ የጦርነት ነጋሪት የሚጎስሙና ወደ ጦርነት አውድማም የሚገቡ የአለማችን አጥፊ እኩያን ሃይሎች ቅድሚያ የተደበቀ የእኩይ ስራቸው ሰለባ የሚያደርጉት እራሱን እውነትን ነው፡፡አዎ እውነትን አዛብቶ ደልዞ በርዞ ለሀዝብ ማቅረብና ህዝብ የጦርነት ነጋሪት ለሚጎስሙና ወደ ጦርነት አውድማም ለሚገቡ እጁን አጨብጭቦና መርቆ እንዲልክ ለማድረግ፡፡በዚህ የተነሳም ስልጣን ላይ ያለው የመለስ/ወያኔም አገዛዝ የእኩይ ስራው ሰለባ ሊያደርጋቸው የሚፈልጋቸውንና ለስልጣን መደላድሉ ፈተና ናቸው የሚላቸውን ምስኪን ኢትዮጵያን ለማጥቃት ሲፈልግ ቅድሚያ የሚያደርገው ነገር እራሱን እውነትን አዛብቶ ደልዞ በርዞ ለሀዝብ ማቅረብና ከዚያም አንድ የሆነ አሸባሪነት ወይንም ትምክህተኛ ወይንም ሌላ ታፔላ መለጠፍና ከዚያም ዘብጥያ ማውረድ ወይንም መግደል ነው፡፡እንደ አሜሪካ ያሉት ሃያላን ሀገራትም ለእነሱ ጥቅም የማይመቹና የማያጎበድዱትን ደካማ ሀገራትን ለማጥቃት ሲፈልጉ ቅድሚያ የሚያደርጉት ነገር እራሱን እውነትን አዛብቶ ደልዞ በርዞ ለአለም ሀዝብ ማቅረብና ከዚያም አንድ የሆነ አሸባሪነት ወይንም አውዳሚ የጦር መሳሪያ(WMD) ወይንም ሰብዓዊ መብት ወይንም ዲሞክራሲ የሚል ሽፋን በመጠቀም በዓለም ላይ በተቆጣጠሩት Mainstream Media አማካኝነት ፕሮፖጋንዳ በመንዛት ሀገራትን ቅድሚያ እንዲጠሉና እንዲገለሉ ማድረግ ከዚያም ይህንን እንደ ሰበብ በመጠቀም የጦርነት ነጋሪት እየጎስሙና ወደ ጦርነት አውድማ መግባት ነው፡፡ትንሹ ጆርጅ ቡሽ ስለኢራቅ ሲናገሩ ስሜታቸው የተረበሸው ሳዳም ሁሴን አውዳሚ የጦር መሳሪያ አላቸው በማለት የሀሰት ፕሮፖጋንዳ ለአሜሪካና ለአለም ህዝብ በመንዛት አላስፈላጊ የኢራቅ ጦርነት ውስጥ ገብተው የፈጠሩት እጅግ አሳዛኝኛ አሳፋሪ ዘርፈ ብዙና ጥልቅ የሆነ ቀውስና ውድመት ትዝ ብሏቸው ነው፡፡በእርግጥ አሜሪካንና እና የእንግሊዝን በዋናነት ማእከል ያደረገውን የግሎባል ካፒታሊስት ስርዓት በጥልቀትና በስፋት ለሚረዳ ሰው አሸባሪነትን መዋጋት የሚለውንም ሆነ ይህንን አይነት የኢራቅ ትልቅ ጦርነት አንድ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ብቻውን ዝም ብሎ በራሱ ስልጣንና ውሳኔ ብቻ ዘው ብሎ የሚገባበት ሳይሆን ከበስተጀርባ ያሉት በፔንታጎንም ውስጥ ሆነ ከዚያ ውጭ ያሉት ወሳኝ ልሂቃን ወይንም ኤሊቶች ሁሉ መክረውበት ዘክረውበት በስተመጨረሻ ለፕሬዝዳንቱ ለመጨረሻ ውሳኔ ከቀረበ በኋላ ነው፡፡ስለዚህም ቡሽ ኢራቅን ወረረ ወይንም ቡሽ ጦረኛ ነው ወዘተ አይነት ጥራዝ-ነጠቅ አባባሎች ብዙም ውሃ የማይቋጥሩ አባባሎች ናቸው፡፡የ 9/11 የኒዎርክን የአሸባሪዎች ጥቃት ተከትሎ የታወጀው አሸባሪነትን መዋጋት በሚል ሽፋን በጊዜና በቦታ ያልተገደበ ማብቂያ የሌለው የታወጀው አለም አቀፍ ጦርነት ቅድሚያ በአፍጋኒስታን ከዚያም በኢራቅ ከዚያም በሊቢያ ከዚያም በሶርያ ከዚያም በማሊ ወዘተ እየተዛመተ አለምን ይህ አይነት ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ በቀዝቃዛው ጦርነት ዘመን እንኳን ያልታየ ይህ አይነት ከፍተኛ ቀውስና አለመረጋጋት ውስጥ እየከተታት ያለው እውነትን አዛብቶ ደልዞ በርዞ ለአለም ሀዝብ በMainstream Media አማካኝነት ፕሮፖጋንዳ በመንዛትና በማቅረብ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡እንደ እውነቱ ከሆነ ጆርጅ ቡሽም ሆነ ከበስተጀርባው ያሉት በፔንታጎንም ውስጥም ሆነ ከዚያ ውጭ ያሉት ወሳኝ ልሂቃን ወይንም ኤሊቶች ሁሉ በኢራቅ ለተፈጠረውና አሁንም ቀጣይነት ላለው ሚሊየኖችን ሙት ቁስለኛ በሽተኛ ቤት-አልባ ወዘተ ላደረገ አውዳሚ ጦርነት ቅድሚያ በህሊናና በህግ ከዚያ ደግሞ በታሪክና በፈጣሪ ዘንድ ተጠያቂ ናቸው፡፡በእርግጥ በጦርነት ወቅት ብዙዎች ተጎጅ የሚሆኑትን ያህል በተቃራኒው ደግሞ ጥቂቶች በጦርነት እንደሚያተርፉ የአደባባይ ሚስጥርና የሚታወቅ ነገር ነው፡፡በእርግጥ ግሎባል ካፒታሊዝም በራሱ በጦርነትና ይህንንም ተከትሎ በሚመጣው ቀውስና ውድመት የማትረፍ ሰይጣናዊ ባህሪን እየተላበሰ ነውና በኢራቅም ሆነ በሌላ ከሚደረገው አውዳሚ ጦርነትና ቀውስ በእጅጉ የሚያተርፉ ሀብታም ልሂቃን እንዳሉ የሚታወቅ ነገር ነው፡፡የአሜሪካ MIC(Military Industrial Complex) ደግሞ የዚህ አይነተኛ መገለጫ ነው፡፡የእኛን የመለስን ብዙሃኑ የሚያውቀው ግልፅ የሆነ ነገር ስለሆነ ለጊዜው እንተወውና የቡሽን ነገር ስናነሳው ግን ዋናው ወሳኝ መሰረታዊ እውነታው ግን ፀሃፊው የምርጫ ዲሞክራሲን ብቻ መሰረት አድርጎ በጥራዝ-ነጠቅ ጠባብ እይታ ካቀረበው በዘለለ በእጅጉ የተለየ ነገር ነው፡፡ፀሃፊውን አንድ እጅግ ወሳኝ መሰረታዊ ጥያቄ ላቅርበለት፡፡ለመሆኑ አንድ እንደ ኦባማ ወይንም ቡሽ አይነት የአሜሪካ ፕሬዝዳንት በምርጫ ዲሞክራሲ ስልጣን ላይ ስለወጣ ብቻ ይህ በራሱ ይህንን መሪ ወይንም የሚመራውን ሀገር ሌላ ደካማ ሀገርን (በአምባገነን የሚመራም ጭምር ቢሆን) እንደፈለገው ማንኛውንም ሰብብ እየፈጠረ በጦርነት እንዲወርና ይህንን አይነት አውዳሚ ጦርነትና ተከታይ ቀውስ እንዲፈጥር የይለፍ ፈቃድ የሚሰጥ ነዎይ?አለም አቀፍ ህግስ እንዴት ነው ይህንን የሚያየው፡፡በእርግጥ የተባበሩት መንግስታትም ሆነ አለም አቀፍ ህግ በራሱ አሜሪካና ምእራባውያን ለራሳቸው በሚመች መንገድ የመሰረቱትና ከራሳቸው ጥቅምና ፍላጎት እንፃር የሚዘውሩት ተቋማት እንደሆኑ የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡በእርግጥ ልክ ወያኔ አሸባሪነትን በሚተረጉምበት እይታ በተመሳሳይም መንገድም በአሜሪካና በምእራባውያን ዘንድም እራሱ አሸባሪነትም ሆነ ዲሞክራሲ ሰብዓዊ መብት አለም አቀፍ ህግ በራሱ የሚተረጎመውም ከራሳቸው ከአሜሪካና ምእራባውያን የግሎባል ካፒታሊዝም ኒዎ-ሊበራል እና ኒዎ-ኮሎኒያሊዝም ኢምፔሪያሊስታዊ ጥቅምና ፍላጎት አንፃር እየታየ ነው፡፡ከቀዝቃዛው ጦርነት ማክተም በኋላ ላለፉት 20 ዓመታት ያህል ያየነውና የታዘብነውም ይህንኑ ነው፡፡ፕሮፌሰር አለማየሁ በቅርቡ የፃፉትን የሚከተውን ፅሁፍ በጥሞና ላነበበ ሰው በድጋሚ ላስታውስ የምፈልገው ነገር ከዚህ በኋላ አሜሪካና ምእራባውያን አሸባሪነት ዲሞክራሲ ሰብዓዊ መብት ወዘተ የሚሉትን ቃላቶችና ፅንሰ-ሀሳቦች ለራሳቸው ፍላጎትና ጥቅም በሚመች መንገድ እራሳቸው ለራሳቸው ባዘጋጁት መዝገበ-ቃላት የተቀረነው የዓለም ማህበረሰብ በዚህ እይታ ለመጠቀም ብዙም ፈቃደኛ መሆን የማንችልበት ደረጃ ላይ እንደደረስን እንዲረዱት ነው፡፡ኦባማም ሆነ ጀርጅ ቡሽ በራሳቸው በአሜሪካውያን የዲሞክራሲ ዘይቤ ተመርጠው ስልጣን ላይ እንደወጡ ይታወቃል ጥሩ ነው ነገር ግን ይህ በራሱ ኦባማም ሆነ ጀርጅ ቡሽ ወይንም አሜሪካ በተቀረው አለም ላይ አሸባሪነት ዲሞክራሲ ሰብዓዊ መብት ወዘተ የሚሉትን ቃላቶችና ፅንሰ-ሀሳቦች ለራሳቸው ፍላጎትና ጥቅም በሚመች መንገድ እራሳቸው ለራሳቸው ባዘጋጁት መዝገበ-ቃላት እንደፈለጋቸው እየተረጎሙ እንደ ዩጎዝላቭያ ኢራቅ ሊቢያ ሶርያ ወዘተ አይነት ደካማ ሀገራትን እንደፈለጉት ለመውረር የይልፍ ፍቃድ ሊሆን አይችልም አይገባምም፡፡ትንሹ ጆርጅ ቡሽ ስለኢራቅ ሲናገሩ ስሜታቸው የተረበሸው ሳዳም ሁሴን አውዳሚ የጦር መሳሪያ አላቸው በማለት የሀሰት ፕሮፖጋንዳ ለአሜሪካና ለአለም ህዝብ በመንዛት አላስፈላጊ የኢራቅ ጦርነት ውስጥ ገብተው የፈጠሩት እጅግ አሳዛኝኛ አሳፋሪ ዘርፈ ብዙና ጥልቅ የሆነ ቀውስና ውድመት ትዝ ብሏቸው ነው፡፡አያ ጅቦ ሳታመካኝ ብላኝ ካልሆነ በስቀር ነገር ግን እንደተባለው ሳዳሞ ሁሴን የተባለው አይነት አውዳሚ የጦር መሳሪያ(WMD) እንዳላቸው ምንም አይነት ግልፅና እውነተኛ መረጃ ለማቅረብ አልተቻለም፡፡ነገር ግን አውዳሚ የጦር መሳሪያ(WMD) እና የሳዳምን አምባገነንነት ብቻ እንደ ሰበብ እና ሽፋን በመጠቀም ይህንን ተገቢ ያልሆነ ህገ-ወጥ አውዳሚ ጦርነት ተከትሎ በኢራቅና አካባቢው የተፈጠረው ውድመትና ቀውስ ግን እንዲህ በቀላሉ በቃላት ለማስረዳት የሚከብድ ነው፡፡
    ዛሬ ኢራቅና ኢራቃውያን ከአምባገነኑ ከሳዳም ሁሴን አገዛዝ ዘመን በባሰ በእጅጉ በእጅጉ አስከፊ ሁኔታ ውስጥ ነው ያሉት፡፡ዛሬ ኢራቃውያን በዘርና ሃይማኖት ተከፋፍለው ከፍተኛ የሆነ የእርስ በርስ እልቂት ውስጥ ነው ያሉት፡፡በዚህ የተነሳም በየጊዜው ወቅት እየጠበቀ በሚነሳ የቦንብ ፍንዳታና ሌላም የእርስ በርስ ግጭት ዘወትር ሰዎች እያለቁና ቁስለኛ እየሆኑ ነው ያለው፡፡በአሜሪካ መራሹ ኔቶ አማካኝነት በአየር ላይ የቦንብ ጥቃት የተነሳ የኢራቅ መሰረተ-ልማት በከፍተኛ ሁኔታ ነው የወደመውና የፈራረሰው፡፡ይህም ብቻ ሳይሆን ከእነዚህ የአየር ላይ የቦንብ የጦር መሳሪያዎች ቅሪት በሀገሪቱ በከፍተኛ ሁኔታ ስለተበታተኑ በውስጣቸው ያለው DU(Depleted Uranium) አማካኝነት ኢራቃውያን ከፍተኛ የሆነ የካንሰር ሰለባ በመሆናቸው የሚወለዱት ህፃነት ከፍተኛ የሆነ አካላዊና አእምሯዊ ጉዳት እየደረሰባቸው ነው፡፡ከኢራቅ ወረራ በፊት በዩጎዝቭያ የተከሰተው የኔቶ ወረራ የቦንብ ውርጅብኝ እና እንደዚሁም ከዚያ በኋላ በሊቢያ የተፈጠረው አጠቃላይ ውድመትና ቀውስ እንደዚሁም አሁን በቀጣይ በሶርያ ያለው አጠቃላይ ሁኔታ ወደተመሳሳይ ሁኔታ የሚያመራ ነው የሚሆነው፡፡
    ነገር ግን እጅግ የሚያሳዝነውና የሚገርመው ነገር አንዳቸውም ኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች(ጉልጉልን ጨምሮ) ይህንን አይነት አሳሳች ዘገባ ከማቅረብ ውጪ በዩጎዝላቭያና በኢራቅም ሆነ ከዚያ በኋላ በሊቢያ በሶርያ ስለተፈጠረው አጠቃላይ ውድመትና ቀውስ በተገቢው መንገድ እውነትን ተከትለው ትንፍሽ አለማለታቸው ነው፡፡እኩያን ሃይሎች ለጥፋት ተባባሪ የሚያገኙት ደግሞ የሚያወሩትን የሀሰት ፕሮፖጋንዳ መልሶ የሚያስተጋባለቸው ጆሮዎችና አፎች እስካገኙ ድረስ ብቻ ነው፡፡ይህ የጉልጉል ዘገባም ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ይህ እውነተን የማዛባት የማደብዘዝ ወይንም ግማሽ እውነት ግማሽ ሀሰት/ሸፍጥ የመንዛት የረቀቀና የተቀነባበረ ሁኔታ ተጠናክሮ እስከቀጠለ ድረስ ደግሞ ጥቂት እኩያን ልሂቃን በሚፈልጉት መንገድ አለም ምንጊዜም የጦርነት አውድማ ከመሆን አትቀርም፡፡ብዙ ኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች ስልጣን ላይ ያለውን የወያኔን በደልና ሃጢያት እንደምክንያት ብቻ በመጠቀም ነገር ግን በተቃራኒው እጅግ የተዛባ አለም አቀፍ የሚዲያ ዘገባ ነው እያቀረቡ ያሉት፡፡የወያኔን በደልና ሃጢያት የኢትዮጵያ ህዝብ በእለት ተእለት ህይወቱ የሚያየው የገፈቱ ቀማሽ ስለሆነ ይህንን ብቻ ዝንተ አለም እየደጋገሙ ማውራት አስፋለጊ ነው ቢባል እንኳን በራሱ ግን ብቻውን ብዙም የሚቀይረው ነገር የለም፡፡እርስ በርሷ የምትለያይ መንግስት ትጠፋለች እንዳለው ቅዱስ መፅሀፍ ማንኛውም እኩይ ነገር ሁሉ እርስ በርሱ የተሳሰረና ለህልውናው ሲል የሚደጋገፍ እንደሆነ ብዙዎቻችን ኢትዮጵያውያን የተረዳን አይመስለኝም፡፡ስለዚም የመለስን ፋውንዴሽን የምንቃወም ከሆነ ይህንን ተቃውሞ ለማስረገጥ ሲባል ብቻ በኢራቅ ወረራ የተነሳ አለም አቀፍ የጦር ወንጀለኛ የሆነውን የቡሽን መደገፍ ከምን መሰረታዊ እውነታ የመነጨ እንደሆነ ለእኔ ብዙም አይገባኝም፡፡የምርጫ ዲሞክራሲን ብቻ መሰረት አድርጎ በፀሃፊው በጥራዝ-ነጠቅ እይታ የቀረበው ነገር እንዲያው ከውጪ ያለውን እይታ ቀለም የመቀባባት ነገር ካልሆነ በስተቀር እውነትን ተከትሎ ከውስጥ ያለውን ድብቅ መሰረታዊ እውነታ ግን ብዙም የሚገልጥና የሚዳሰስ አይደለም፡፡ጆርጅ ቡሽና ቶኒ ብሌየር የለየላቸው የጦር ወንጀለኞች ናቸው እናም በምርጫ ዲሞክራሲ ስልጣን ላይ መውጣታቸውና ይህ በፎቶ የተደገፈው ስነ-ስርዓት አይነት ውጪያዊ እይታ ከውስጥ ያለውን ድብቅ መሰረታዊ እውነታ ግን ብዙም የመቀይረው ነገር አይደለም፡፡በአሜሪካና ዋና መሪነት በምእራባውያን ወራሪነት በኢራቅ የተፈጠረውን ኢ-ሰብዓዊና ህገ-ወጥ ጦርነት ውድመትና ቀውስ በትክክል ከመዘገብ ይልቅ የአሜሪካንን የምርጫ ዲሞክራሲ ስርዓት ብቻ ሰብበ አድርጎ ይህንን አይነት ከበስተጀርባ ያለውን የኢራቅንም ሆነ ሌላውን አይነት ዋና ወሳኝ እውነታ የሚያድበሰብስ የተዛባ ዘገባ ማቅረብ በእርግጥ ከኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች የሚጠበቅ ነገር ነው፡፡አሸባሪነትን መዋጋት በሚል ሽፋን ላለፉት 12 ዓመታት ያህል በተከፈተው አለም አቀፍ ጦርነት የተነሳ የኢራቅን ጨምሮ አሜሪካ በድምሩ በትሪሊዬን ዶላር የሚገመት ወጪ አውጥታለች፡፡
    ይህንን አውዳሚ የጦርነት ወጪ ማነው የሚሸፍነው ከዚህስ አውዳሚ ጦርነት ማነው የሚጠቀመው?በአሜሪካና ከዚያም በቀጣይነት የተፈጠረው የምእራቡ አለም የፋይናንስና የኢኮኖሚ ቀውስ ከእንደዚህ አይነት አላስፈላጊ አውዳሚ የጦርነት ጋር ምን ያያይዘዋል?
    ዋናው መሰረታዊ ጥያቄና እውነታ በዚህ ላይ ነው ማጠንጠን ያለበት እንጂ የጆርጅ ቡሽንና የመለስን ፋውንዴሽን በጥራዝ-ነጠቅና በጠባብ እይታ ማወዳደሩ ላይ አይደለም፡፡
    “ክሊንተን ቀደም ብሎ በተራው ንግግር እያደረገ ሳለ ለፈገግታ ከማገልገልም ባሻገር አንድ ለጥናታችን ጠቃሚ የሆነ ቁምነገር እንደ ቀልድ አድርጎ ተናግሮ ነበር። እሱም፥ “ከስልጣን በኋላ የቀድሞ ፕረዘዳንቶች ፈተና መታሰቢያ ተቋሞች በመገንባት ታሪካቸውን እንደገና ለመጻፍ መታገል ነው እያልኩ ለኦባማ ሁልጊዜ እነግረዋለሁ” የሚል ነበር።” ከፀሃፊው የወሰድኩት ከላይ ያለውን የክሊንተንን አባባል ፀሃፊው ከውጪ ያለውን ሰሙን እንጂ ውስጣዊ ቅኔውን በቅጡ የተረዳው አይመስለኝም፡፡ማለትም እንደ አንድ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆርጅ ቡሽ በስልጣን ዘመኑ የሰራውን ያለፈ ነገር ሁሉ አሁን ለመቀየር ፈፅሞ አይችልም፡፡The passed is passed.ነገር ግን አሁን ለማድረግ የሚቻለው ግን ጆርጅ ቡሽ በስልጣን ዘመኑ እንደ አንድ ፕሬዝዳንት የሰራውን ያለፈ ነገር እንዴት እንደሆነ የማቅረብ የመተረክ የማስታወስ የመገምገምና ፍርድ የመስጠት ጉዳይ ብቻ ነው የሚሆነው፡፡ስለዚህም የክሊንተን አባባል እኔ እንደምረዳው ከሆነ እውነትንና ታሪክን በትክክል ከመዘገብ ከመተርጎም ከመመዘንና ፍርድ ከመስጠት ጋር በተያያዘ ያለንበትን ፈታኝ የዘመናችን ሁኔታ የሚያስታውስ ነው፡፡ወደ እኛ ሀገርም ስንመጣም የመለስ ራእይ እና በተያያዥ ያለውም የፋውንዴሽን ጉዳይ ይህንኑ እውነትንና ታሪክን በትክክል ከመዘገብ ከመተርጎም ከመመዘንና ፍርድ ከመስጠት ጋር በተያያዘ ያለንበትን ፈታኝ የዘመናችን ሁኔታ የሚያስታውስ ነው፡፡ይህ ደግሞ እየሆነ ያለው ከታሪክ እንደምንማረው ሰዎች ከታሪክ አለመማራቸውን ነው የሚለውን የሚያስታውስ ብቻም ሳይሆን ከዚህም በከፋ እውነትንና ታሪክን እያጣመሙ ማቅረብ እኩያን ሃይሎች እኩይ ስራቸው ለዘመናት በብዙሃኑ ዘንድ በቅጡ ሳይመረመርና እውነቱ ሳይገለጥ ተሸፋፍኖና ተዳፍኖ እንዲቀጥል የሚያደርጉበት የረቀቀና የተቀነባበረ መሰሪ ሴራ ጭምር መሆኑን የሚያመላክት ነው፡፡ለዚህም ነው በመግቢያዬ ላይ በውጪ ከሚታየው ከአካላዊ ጦርነት በበለጠም የዘመናችን እጅግ ዋናው ፈታኝ ጦርነት በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለውና ይህንንም ተከትሎ ጭምር ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት ነው ያልኩት፡፡ጆርጅ ቡሽ የጦር ወንጀለኛ ናቸው፡፡በእርግጥ ይህ ሲባል ጆርጅ ቡሽ ወይንም ኦባማ ወይንም ሌላ ይህንን አይነት የኢራቅ አይነት ጦርነት በራሳቸው ስልጣን ብቻ የማድረግም ሆነ ያለማድረግ መብት ያን ያህል አይኖራቸውም፡፡
    በእርግጥ ይህ አይነት ጦርነት በዋናነት የሚመነጨው አሜሪካና ምእራባውያን ከሚያራምዱት የግሎባል ካፒታሊዝም ኒዎ-ሊበራልና ኒዎ-ኮሎኒያሊዝም ኢምፔሪያሊስታዊ ፕሮጀክት የሚመነጭ ነውና ጉዳዩ ጆርጅ ቡሽ ጦረኛ ነው አይደለም ከሚል ጠባብ እይታ በዘለለ በራሱ የስርዓቱ መሰረታዊ ውስጣዊ አሰራርና ባህሪ ነው፡፡ስለዚህም ጆርጅ ቡሽ ወይንም ኦባማ ይህንን ፕሮጀክትና ስርዓት በታማኝነት የሚያስፈፅሙ አገልጋይ መሳሪያዎች(Tools) ናቸው፡፡ሃይለማርያም ደሳለኝ የወያኔ መሳሪያ እንደሆኑት ማለት ነው፡፡ወያኔም የባእዳን ቅጥረኛ መሳሪያ እንደሆነው ሁሉ ማለት ነው፡፡ስለዚህም የመለስ ራእይ ይቀጥላል ፋውንዴሽንም ይሰራ ሲባል ወይንም ጆርጅ ቡሽ የጦር ወንጀለኛ ሆኖ ሳለ ለጆርጅ ቡሽ ይህ አይነት ፋውንዴሽን መሰራቱ የሚያመላክተው በውጪ ከሚታየው ከአካላዊ ጦርነት በበለጠም የዘመናችን እጅግ ዋናው ፈታኝ ጦርነት በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለውና ይህንንም ተከትሎ ጭምር ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት ነው የሚለውን ነው፡፡ይህም ብቻም ሳይሆን ይህ አይነት ሁኔታ የሚያሳየው አሜሪካና ምእራባውያን ከሚያራምዱት የግሎባል ካፒታሊዝም ኒዎ-ሊበራልና ኒዎ-ኮሎኒያሊዝም ኢምፔሪያሊስታዊ ፕሮጀክት ስርዓቱና የሚያራምደው አውዳሚ ጦርነት ወረራውና አለም አቀፍ ቀውሱ ተጠናክሮ ይቀጥላል ማለት ነው፡፡ጆርጅ ቡሽ በምርጫ ዲሞክራሲ ሁለት ጊዜ የተመረጠ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት እንደሆነ ይታወቃል በዚህም ለጆርጅ ቡሽ ፋውንዴሽን ተመሰረተ ጥሩ እሺ ኪዚያ በኋላ ግን ምንድን ነው ሊታወስ የሚፈለገው፡፡
    አሸባሪነትን የተዋጋና ከምድረ ገፅ ያጠፋ?በአሸባሪነት ሽፋን እራሱን አሸባሪነትን ያስፋፋና ደካማ ሀገራትን በዚህ ሽፋን እንደፈለገው የወረረ?ኢራቅን የወረረና የኢራቅን ህዝብ ለከፋ ስነ-ልቦናዊ ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ ፖለቲካዊ አካባቢያዊ ቀውስ የዳረገ?በዚህ የአውዳሚ ጦርነት አላስፈላጊ ወጪው የተነሳና በሌላም ምክንያት አሜሪካንና አብዛኛውን የአሜሪካንን ህዝብ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ የዳረገ? በጦርነቱና በፋይናንስ ቀውስ ሰበብ የMIC (Military Industrial Complex) እና Wall-Street ሃብታሞችን የበለጠ ሀብት እንዲያከማቹ ያደረገ?እንደ ግለሰብ በእነዚህ አይነት ፋውንዴሽኖች ላይ መቋቋምና መመስረት ብዙም ተቃውሞ የለኝም ወይንም እንዴት እንደተመሰረቱም ቢሆን ያን ያህል ብዙ አያስጨንቀኝም?ዋናው ቁምነገር ግን ለምን አላማ ሲባል ተመሰረቱ የሚለውና በተያያዥም እውነቱና ታሪኩ በትክክል ይቀርባል የተረጎማል መላው አለምና ቀጣይ ትውልድስ ከዚህ ምን ይማራል የሚለው ነው ይበልጥ የሚያሰጨንቀኝ፡፡Successes or failure is the way we present and interpret it እንደሚባለው መሪዎች የሚሰሩት ስራ ለተወሰነው ዜጋ ወይንም የህብረተሰብ ክፍል ወይንም ሀገር ጥሩና የስኬት ሊሆን ይችላል በተቃራኒው ደግሞ ለተቀረው መጥፎና ውድቀት ሊሆን ይችላል፡፡ስለዚህም ይህ አይነት ፋውንዴሽን መመስረቱ እነዚህን አይነት መሪዎች በጥሩም ሆነ በመጥፎ ለማስታወስ ይረዳል፡፡ ዋናው ቁምነገሩ ያለው ግን ይህንን ፋውንዴሽን ምክንያት አድርጎ ለታሪክና ለትውልድ የሚተላለፈው መልእክት ምንድን ነው የሚለው ላይ ነው፡፡እውን በዚህ የቡሽ ፋውንዴሽን ላይ ቡሽና ቶኒ ብሌየር በኢራቅና በኢራቃውያን ላይ የፈፀሙት የጦር ወንጀልና ይህንንም ተከትሎ የተፈጠረውን አጠቃላይ ስነ-ልቦናዊ ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ ፖለቲካዊ ወዘተ ውድመትና ቀውስ በፊልም በመረጃ ተደግፎ ይቀርባልን?ከእኛ በበለጠ ኢራቃውያንስ ምን ይላሉ? ይህ ካልሆነ ግን የፋውንዴሽኑ መመስረት ብዙም ፋይዳ የለውም፡፡
    በእርግጥ ብዙዎቹ ኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች የአለምን አጠቃላይ ዘርፈ ብዙና ጥልቅ የሆነ ውስብስብ ሁኔታ ብዙውን ጊዜ የሚመለከቱት በዚህ የፈረደበት የታይታ የምርጫ ዲሞክራሲ እና ነፃ-ገበያ በሚል ጥቅል ጥራዝ-ነጠቅ መነፅር ብቻ ነው፡፡ከዚህ በመነጨም እውነታው በትክክል አይቀርብም፡፡ስለ ቡሽ ፋውንዴሽን ማነፃፀሪያው ደግሞ መለስ ሳይሆን መሆን ያለበት እውነትና እውነት ብቻ ነው መሆን አለበት፡፡እውነተኛ ሚዲያዎች ደግሞ ይህንን አይነት አስተያየት ጭምር አሁንም ወደፊትም ሳይበርዙ ሳይከልሱ ያቅርቡ፡፡

  2. በእርግጥ ልክ ወያኔ አሸባሪነትን በሚተረጉምበት እይታ በተመሳሳይም መንገድም በአሜሪካና በምእራባውያን ዘንድም እራሱ አሸባሪነትም ሆነ ዲሞክራሲ ሰብዓዊ መብት አለም አቀፍ ህግ በራሱ የሚተረጎመውም ከራሳቸው ከአሜሪካና ምእራባውያን የግሎባል ካፒታሊዝም ኒዎ-ሊበራል እና ኒዎ-ኮሎኒያሊዝም ኢምፔሪያሊስታዊ ጥቅምና ፍላጎት አንፃር እየታየ ነው፡፡ከቀዝቃዛው ጦርነት ማክተም በኋላ ላለፉት 20 ዓመታት ያህል ያየነውና የታዘብነውም ይህንኑ ነው፡፡ፕሮፌሰር አለማየሁ በቅርቡ የፃፉትን የሚከተለውን ፅሁፍ
    http://ecadforum.com/2013/04/28/watching-american-diplocrisy-in-ethiopia/
    በጥሞና ላነበበ ሰው በድጋሚ ላስታውስ የምፈልገው ነገር ከዚህ በኋላ አሜሪካና ምእራባውያን አሸባሪነት ዲሞክራሲ ሰብዓዊ መብት ወዘተ የሚሉትን ቃላቶችና ፅንሰ-ሀሳቦች ለራሳቸው ፍላጎትና ጥቅም በሚመች መንገድ እራሳቸው ለራሳቸው ባዘጋጁት መዝገበ-ቃላት የተቀረነው የዓለም ማህበረሰብ በዚህ እይታ ለመጠቀም ብዙም ፈቃደኛ መሆን የማንችልበት ደረጃ ላይ እንደደረስን እንዲረዱት ነው፡፡

  3. 1ኛ)የሆነው ሆኖ የመጨረሻ ተናጋሪ የነበረው ቡሽ (ትንሹ) በንግግሩ መገባደጃ ግድም ሰለ አሜሪካ እና ኢራቅ ጦርነት በንግግሩ ጠቀሰ እና የጦርነት ፕሬዘዳንት መሆን ግን ምኞቱ እንዳልነበር ተናገረ። ለጥቆ “ህዝባችንን እና አገራችንን የተለያዩ እንቅፋቶች ቢገጥሙዋቸውም የአገራችን ብሩህ ቀኖች ገና ከፊታችን ስለመሆናቸው ያለኝ እምነት የማይናጋ ነው” በማለት ላይ ሳለ ድምጹ ተቀየረ። የአገር ወዳድነት ስሜቱ መጥቶበት ይሁን ወይንም በስልጣን ላይ ሳለ የጦር ጊዜ ፕሬዘዳንት በመሆን በአሚሪካ እና በኢራቅ ታሪክ ላይ ያስከተለው የታሪክ አቅጣጫ ለውጥ አስዝኖት ግልጽ አይደለም። ድምጹን እና አይኖቹን መፈታተን የጀመረው ስሜቱ ሳያሸንፈው ንግግሩን ቋጭቶ አይኖቹን በእጆቹ ጠረገ። የንግግር ወለሉን ለቆ ወደመቀመጫው አመራ። ባለቤቱ ሎራ ጎን ሊቀመጥ። በአጠገቡ የነበሩት አራት ፕሬዘዳንቶች ከነቤተሰባቸው እና በመታሰቢያ ተቋሙ ምርቃት ላይ እንዲገኝ የተጋበዘው ህዝብ በሙሉ ጸጥ አለ። ቡሽ (ትንሹ) ፊቱ ላይ ፈገግታ ለማስቀመጥ እየታገለ በአንድ እጁ አይኖቹን መጥረጉን ቀጠለ።

    2ኛ)ክሊንተን ቀደም ብሎ በተራው ንግግር እያደረገ ሳለ ለፈገግታ ከማገልገልም ባሻገር አንድ ለጥናታችን ጠቃሚ የሆነ ቁምነገር እንደ ቀልድ አድርጎ ተናግሮ ነበር። እሱም፥ “ከስልጣን በኋላ የቀድሞ ፕረዘዳንቶች ፈተና መታሰቢያ ተቋሞች በመገንባት ታሪካቸውን እንደገና ለመጻፍ መታገል ነው እያልኩ ለኦባማ ሁልጊዜ እነግረዋለሁ” የሚል ነበር።

    ****************************************************************************

    በውጪ ከሚታየው ከአካላዊ ጦርነት በበለጠም የዘመናችን እጅግ ዋናው ፈታኝ ጦርነት በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለውና ይህንንም ተከትሎ ጭምር ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት ነው፡፡በውጪ የሚታየው አካላዊ ጦርነት ቅድሚያ ከውስጥ ያለው በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለው ውስጣዊ ጦርነት ቀጣይ ማስተንፈሻ ወይንም መገለጫ ወይንም መቋጫ ነገር ነው፡፡ይህንንም ተከትሎ ሀሰትንና እውነትን ለማምታታም ሆነ ለማጥራት ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት የዘመናችን ፈታኝ ነገር ነው፡፡ከቡሽም ሆነ ከመለስ በስተጀርባ ያለው ነገር ዲሞክራሲ ከሚለው ዘመነኛ ቃል ጋርና እኛም ለዚህ ዲሞክራሲ ለሚባል ነገር ካለን ጥራዝ-ነጠቅ እይታ አንፃር ሲታይ ከውጪ በሚታየው በቅርፅ ደረጃ የሚታወቀው አይነት የተወሰነ ልዩነት ቢኖረውም በመሰረታዊ የእውነት ይዘት ግን ያው ተመሳሳይነት ያለው ነገር ነው፡፡ተመሳሳይነቱም በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለው ጦርነትና ይህንንም ተከትሎ ጭምር ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት መገለጫ መሆኑ ነው፡፡ፈረንጆች እንደሚሉት The first casualty of war is truth ሲባል በዘመናችን የሰላም የፍቅር የብልፅግና ፀር የሆነው አጥፊው ጦርነት ከመታወጁ በፊት ይህንን አላስፋላጊ የጦርነት ነጋሪት የሚጎስሙና ወደ ጦርነት አውድማም የሚገቡ የአለማችን አጥፊ እኩያን ሃይሎች ቅድሚያ የተደበቀ የእኩይ ስራቸው ሰለባ የሚያደርጉት እራሱን እውነትን ነው፡፡አዎ እውነትን አዛብቶ ደልዞ በርዞ ለሀዝብ ማቅረብና ህዝብ የጦርነት ነጋሪት ለሚጎስሙና ወደ ጦርነት አውድማም ለሚገቡ እጁን አጨብጭቦና መርቆ እንዲልክ ለማድረግ፡፡በዚህ የተነሳም ስልጣን ላይ ያለው የመለስ/ወያኔም አገዛዝ የእኩይ ስራው ሰለባ ሊያደርጋቸው የሚፈልጋቸውንና ለስልጣን መደላድሉ ፈተና ናቸው የሚላቸውን ምስኪን ኢትዮጵያን ለማጥቃት ሲፈልግ ቅድሚያ የሚያደርገው ነገር እራሱን እውነትን አዛብቶ ደልዞ በርዞ ለሀዝብ ማቅረብና ከዚያም አንድ የሆነ አሸባሪነት ወይንም ትምክህተኛ ወይንም ሌላ ታፔላ መለጠፍና ከዚያም ዘብጥያ ማውረድ ወይንም መግደል ነው፡፡እንደ አሜሪካ ያሉት ሃያላን ሀገራትም ለእነሱ ጥቅም የማይመቹና የማያጎበድዱትን ደካማ ሀገራትን ለማጥቃት ሲፈልጉ ቅድሚያ የሚያደርጉት ነገር እራሱን እውነትን አዛብቶ ደልዞ በርዞ ለአለም ሀዝብ ማቅረብና ከዚያም አንድ የሆነ አሸባሪነት ወይንም አውዳሚ የጦር መሳሪያ(WMD) ወይንም ሰብዓዊ መብት ወይንም ዲሞክራሲ የሚል ሽፋን በመጠቀም በዓለም ላይ በተቆጣጠሩት Mainstream Media አማካኝነት ፕሮፖጋንዳ በመንዛት ሀገራትን ቅድሚያ እንዲጠሉና እንዲገለሉ ማድረግ ከዚያም ይህንን እንደ ሰበብ በመጠቀም የጦርነት ነጋሪት እየጎስሙና ወደ ጦርነት አውድማ መግባት ነው፡፡ትንሹ ጆርጅ ቡሽ ስለኢራቅ ሲናገሩ ስሜታቸው የተረበሸው ሳዳም ሁሴን አውዳሚ የጦር መሳሪያ አላቸው በማለት የሀሰት ፕሮፖጋንዳ ለአሜሪካና ለአለም ህዝብ በመንዛት አላስፈላጊ የኢራቅ ጦርነት ውስጥ ገብተው የፈጠሩት እጅግ አሳዛኝኛ አሳፋሪ ዘርፈ ብዙና ጥልቅ የሆነ ቀውስና ውድመት ትዝ ብሏቸው ነው፡፡በእርግጥ አሜሪካንና እና የእንግሊዝን በዋናነት ማእከል ያደረገውን የግሎባል ካፒታሊስት ስርዓት በጥልቀትና በስፋት ለሚረዳ ሰው አሸባሪነትን መዋጋት የሚለውንም ሆነ ይህንን አይነት የኢራቅ ትልቅ ጦርነት አንድ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ብቻውን ዝም ብሎ በራሱ ስልጣንና ውሳኔ ብቻ ዘው ብሎ የሚገባበት ሳይሆን ከበስተጀርባ ያሉት በፔንታጎንም ውስጥ ሆነ ከዚያ ውጭ ያሉት ወሳኝ ልሂቃን ወይንም ኤሊቶች ሁሉ መክረውበት ዘክረውበት በስተመጨረሻ ለፕሬዝዳንቱ ለመጨረሻ ውሳኔ ከቀረበ በኋላ ነው፡፡ስለዚህም ቡሽ ኢራቅን ወረረ ወይንም ቡሽ ጦረኛ ነው ወዘተ አይነት ጥራዝ-ነጠቅ አባባሎች ብዙም ውሃ የማይቋጥሩ አባባሎች ናቸው፡፡የ 9/11 የኒዎርክን የአሸባሪዎች ጥቃት ተከትሎ የታወጀው አሸባሪነትን መዋጋት በሚል ሽፋን በጊዜና በቦታ ያልተገደበ ማብቂያ የሌለው የታወጀው አለም አቀፍ ጦርነት ቅድሚያ በአፍጋኒስታን ከዚያም በኢራቅ ከዚያም በሊቢያ ከዚያም በሶርያ ከዚያም በማሊ ወዘተ እየተዛመተ አለምን ይህ አይነት ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ በቀዝቃዛው ጦርነት ዘመን እንኳን ያልታየ ይህ አይነት ከፍተኛ ቀውስና አለመረጋጋት ውስጥ እየከተታት ያለው እውነትን አዛብቶ ደልዞ በርዞ ለአለም ሀዝብ በMainstream Media አማካኝነት ፕሮፖጋንዳ በመንዛትና በማቅረብ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡እንደ እውነቱ ከሆነ ጆርጅ ቡሽም ሆነ ከበስተጀርባው ያሉት በፔንታጎንም ውስጥም ሆነ ከዚያ ውጭ ያሉት ወሳኝ ልሂቃን ወይንም ኤሊቶች ሁሉ በኢራቅ ለተፈጠረውና አሁንም ቀጣይነት ላለው ሚሊየኖችን ሙት ቁስለኛ በሽተኛ ቤት-አልባ ወዘተ ላደረገ አውዳሚ ጦርነት ቅድሚያ በህሊናና በህግ ከዚያ ደግሞ በታሪክና በፈጣሪ ዘንድ ተጠያቂ ናቸው፡፡በእርግጥ በጦርነት ወቅት ብዙዎች ተጎጅ የሚሆኑትን ያህል በተቃራኒው ደግሞ ጥቂቶች በጦርነት እንደሚያተርፉ የአደባባይ ሚስጥርና የሚታወቅ ነገር ነው፡፡በእርግጥ ግሎባል ካፒታሊዝም በራሱ በጦርነትና ይህንንም ተከትሎ በሚመጣው ቀውስና ውድመት የማትረፍ ሰይጣናዊ ባህሪን እየተላበሰ ነውና በኢራቅም ሆነ በሌላ ከሚደረገው አውዳሚ ጦርነትና ቀውስ በእጅጉ የሚያተርፉ ሀብታም ልሂቃን እንዳሉ የሚታወቅ ነገር ነው፡፡የአሜሪካ MIC(Military Industrial Complex) ደግሞ የዚህ አይነተኛ መገለጫ ነው፡፡የእኛን የመለስን ብዙሃኑ የሚያውቀው ግልፅ የሆነ ነገር ስለሆነ ለጊዜው እንተወውና የቡሽን ነገር ስናነሳው ግን ዋናው ወሳኝ መሰረታዊ እውነታው ግን ፀሃፊው የምርጫ ዲሞክራሲን ብቻ መሰረት አድርጎ በጥራዝ-ነጠቅ ጠባብ እይታ ካቀረበው በዘለለ በእጅጉ የተለየ ነገር ነው፡፡ፀሃፊውን አንድ እጅግ ወሳኝ መሰረታዊ ጥያቄ ላቅርበለት፡፡ለመሆኑ አንድ እንደ ኦባማ ወይንም ቡሽ አይነት የአሜሪካ ፕሬዝዳንት በምርጫ ዲሞክራሲ ስልጣን ላይ ስለወጣ ብቻ ይህ በራሱ ይህንን መሪ ወይንም የሚመራውን ሀገር ሌላ ደካማ ሀገርን (በአምባገነን የሚመራም ጭምር ቢሆን) እንደፈለገው ማንኛውንም ሰብብ እየፈጠረ በጦርነት እንዲወርና ይህንን አይነት አውዳሚ ጦርነትና ተከታይ ቀውስ እንዲፈጥር የይለፍ ፈቃድ የሚሰጥ ነዎይ?አለም አቀፍ ህግስ እንዴት ነው ይህንን የሚያየው፡፡በእርግጥ የተባበሩት መንግስታትም ሆነ አለም አቀፍ ህግ በራሱ አሜሪካና ምእራባውያን ለራሳቸው በሚመች መንገድ የመሰረቱትና ከራሳቸው ጥቅምና ፍላጎት እንፃር የሚዘውሩት ተቋማት እንደሆኑ የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡በእርግጥ ልክ ወያኔ አሸባሪነትን በሚተረጉምበት እይታ በተመሳሳይም መንገድም በአሜሪካና በምእራባውያን ዘንድም እራሱ አሸባሪነትም ሆነ ዲሞክራሲ ሰብዓዊ መብት አለም አቀፍ ህግ በራሱ የሚተረጎመውም ከራሳቸው ከአሜሪካና ምእራባውያን የግሎባል ካፒታሊዝም ኒዎ-ሊበራል እና ኒዎ-ኮሎኒያሊዝም ኢምፔሪያሊስታዊ ጥቅምና ፍላጎት አንፃር እየታየ ነው፡፡ከቀዝቃዛው ጦርነት ማክተም በኋላ ላለፉት 20 ዓመታት ያህል ያየነውና የታዘብነውም ይህንኑ ነው፡፡ፕሮፌሰር አለማየሁ በቅርቡ የፃፉትን የሚከተለውን ፅሁፍ
    http://ecadforum.com/2013/04/28/watching-american-diplocrisy-in-ethiopia/
    በጥሞና ላነበበ ሰው በድጋሚ ላስታውስ የምፈልገው ነገር ከዚህ በኋላ አሜሪካና ምእራባውያን አሸባሪነት ዲሞክራሲ ሰብዓዊ መብት ወዘተ የሚሉትን ቃላቶችና ፅንሰ-ሀሳቦች ለራሳቸው ፍላጎትና ጥቅም በሚመች መንገድ እራሳቸው ለራሳቸው ባዘጋጁት መዝገበ-ቃላት የተቀረነው የዓለም ማህበረሰብ በዚህ እይታ ለመጠቀም ብዙም ፈቃደኛ መሆን የማንችልበት ደረጃ ላይ እንደደረስን እንዲረዱት ነው፡፡ኦባማም ሆነ ጀርጅ ቡሽ በራሳቸው በአሜሪካውያን የዲሞክራሲ ዘይቤ ተመርጠው ስልጣን ላይ እንደወጡ ይታወቃል ጥሩ ነው ነገር ግን ይህ በራሱ ኦባማም ሆነ ጀርጅ ቡሽ ወይንም አሜሪካ በተቀረው አለም ላይ አሸባሪነት ዲሞክራሲ ሰብዓዊ መብት ወዘተ የሚሉትን ቃላቶችና ፅንሰ-ሀሳቦች ለራሳቸው ፍላጎትና ጥቅም በሚመች መንገድ እራሳቸው ለራሳቸው ባዘጋጁት መዝገበ-ቃላት እንደፈለጋቸው እየተረጎሙ እንደ ዩጎዝላቭያ ኢራቅ ሊቢያ ሶርያ ወዘተ አይነት ደካማ ሀገራትን እንደፈለጉት ለመውረር የይልፍ ፍቃድ ሊሆን አይችልም አይገባምም፡፡ትንሹ ጆርጅ ቡሽ ስለኢራቅ ሲናገሩ ስሜታቸው የተረበሸው ሳዳም ሁሴን አውዳሚ የጦር መሳሪያ አላቸው በማለት የሀሰት ፕሮፖጋንዳ ለአሜሪካና ለአለም ህዝብ በመንዛት አላስፈላጊ የኢራቅ ጦርነት ውስጥ ገብተው የፈጠሩት እጅግ አሳዛኝኛ አሳፋሪ ዘርፈ ብዙና ጥልቅ የሆነ ቀውስና ውድመት ትዝ ብሏቸው ነው፡፡አያ ጅቦ ሳታመካኝ ብላኝ ካልሆነ በስቀር ነገር ግን እንደተባለው ሳዳሞ ሁሴን የተባለው አይነት አውዳሚ የጦር መሳሪያ(WMD) እንዳላቸው ምንም አይነት ግልፅና እውነተኛ መረጃ ለማቅረብ አልተቻለም፡፡ነገር ግን አውዳሚ የጦር መሳሪያ(WMD) እና የሳዳምን አምባገነንነት ብቻ እንደ ሰበብ እና ሽፋን በመጠቀም ይህንን ተገቢ ያልሆነ ህገ-ወጥ አውዳሚ ጦርነት ተከትሎ በኢራቅና አካባቢው የተፈጠረው ውድመትና ቀውስ ግን እንዲህ በቀላሉ በቃላት ለማስረዳት የሚከብድ ነው፡፡
    ዛሬ ኢራቅና ኢራቃውያን ከአምባገነኑ ከሳዳም ሁሴን አገዛዝ ዘመን በባሰ በእጅጉ በእጅጉ አስከፊ ሁኔታ ውስጥ ነው ያሉት፡፡ዛሬ ኢራቃውያን በዘርና ሃይማኖት ተከፋፍለው ከፍተኛ የሆነ የእርስ በርስ እልቂት ውስጥ ነው ያሉት፡፡በዚህ የተነሳም በየጊዜው ወቅት እየጠበቀ በሚነሳ የቦንብ ፍንዳታና ሌላም የእርስ በርስ ግጭት ዘወትር ሰዎች እያለቁና ቁስለኛ እየሆኑ ነው ያለው፡፡በአሜሪካ መራሹ ኔቶ አማካኝነት በአየር ላይ የቦንብ ጥቃት የተነሳ የኢራቅ መሰረተ-ልማት በከፍተኛ ሁኔታ ነው የወደመውና የፈራረሰው፡፡ይህም ብቻ ሳይሆን ከእነዚህ የአየር ላይ የቦንብ የጦር መሳሪያዎች ቅሪት በሀገሪቱ በከፍተኛ ሁኔታ ስለተበታተኑ በውስጣቸው ያለው DU(Depleted Uranium) አማካኝነት ኢራቃውያን ከፍተኛ የሆነ የካንሰር ሰለባ በመሆናቸው የሚወለዱት ህፃነት ከፍተኛ የሆነ አካላዊና አእምሯዊ ጉዳት እየደረሰባቸው ነው፡፡ከኢራቅ ወረራ በፊት በዩጎዝቭያ የተከሰተው የኔቶ ወረራ የቦንብ ውርጅብኝ እና እንደዚሁም ከዚያ በኋላ በሊቢያ የተፈጠረው አጠቃላይ ውድመትና ቀውስ እንደዚሁም አሁን በቀጣይ በሶርያ ያለው አጠቃላይ ሁኔታ ወደተመሳሳይ ሁኔታ የሚያመራ ነው የሚሆነው፡፡
    ነገር ግን እጅግ የሚያሳዝነውና የሚገርመው ነገር አንዳቸውም ኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች(ጉልጉልን ጨምሮ) ይህንን አይነት አሳሳች ዘገባ ከማቅረብ ውጪ በዩጎዝላቭያና በኢራቅም ሆነ ከዚያ በኋላ በሊቢያ በሶርያ ስለተፈጠረው አጠቃላይ ውድመትና ቀውስ በተገቢው መንገድ እውነትን ተከትለው ትንፍሽ አለማለታቸው ነው፡፡እኩያን ሃይሎች ለጥፋት ተባባሪ የሚያገኙት ደግሞ የሚያወሩትን የሀሰት ፕሮፖጋንዳ መልሶ የሚያስተጋባለቸው ጆሮዎችና አፎች እስካገኙ ድረስ ብቻ ነው፡፡ይህ የጉልጉል ዘገባም ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ይህ እውነተን የማዛባት የማደብዘዝ ወይንም ግማሽ እውነት ግማሽ ሀሰት/ሸፍጥ የመንዛት የረቀቀና የተቀነባበረ ሁኔታ ተጠናክሮ እስከቀጠለ ድረስ ደግሞ ጥቂት እኩያን ልሂቃን በሚፈልጉት መንገድ አለም ምንጊዜም የጦርነት አውድማ ከመሆን አትቀርም፡፡ብዙ ኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች ስልጣን ላይ ያለውን የወያኔን በደልና ሃጢያት እንደምክንያት ብቻ በመጠቀም ነገር ግን በተቃራኒው እጅግ የተዛባ አለም አቀፍ የሚዲያ ዘገባ ነው እያቀረቡ ያሉት፡፡የወያኔን በደልና ሃጢያት የኢትዮጵያ ህዝብ በእለት ተእለት ህይወቱ የሚያየው የገፈቱ ቀማሽ ስለሆነ ይህንን ብቻ ዝንተ አለም እየደጋገሙ ማውራት አስፋለጊ ነው ቢባል እንኳን በራሱ ግን ብቻውን ብዙም የሚቀይረው ነገር የለም፡፡እርስ በርሷ የምትለያይ መንግስት ትጠፋለች እንዳለው ቅዱስ መፅሀፍ ማንኛውም እኩይ ነገር ሁሉ እርስ በርሱ የተሳሰረና ለህልውናው ሲል የሚደጋገፍ እንደሆነ ብዙዎቻችን ኢትዮጵያውያን የተረዳን አይመስለኝም፡፡ስለዚም የመለስን ፋውንዴሽን የምንቃወም ከሆነ ይህንን ተቃውሞ ለማስረገጥ ሲባል ብቻ በኢራቅ ወረራ የተነሳ አለም አቀፍ የጦር ወንጀለኛ የሆነውን የቡሽን መደገፍ ከምን መሰረታዊ እውነታ የመነጨ እንደሆነ ለእኔ ብዙም አይገባኝም፡፡የምርጫ ዲሞክራሲን ብቻ መሰረት አድርጎ በፀሃፊው በጥራዝ-ነጠቅ እይታ የቀረበው ነገር እንዲያው ከውጪ ያለውን እይታ ቀለም የመቀባባት ነገር ካልሆነ በስተቀር እውነትን ተከትሎ ከውስጥ ያለውን ድብቅ መሰረታዊ እውነታ ግን ብዙም የሚገልጥና የሚዳሰስ አይደለም፡፡ጆርጅ ቡሽና ቶኒ ብሌየር የለየላቸው የጦር ወንጀለኞች ናቸው እናም በምርጫ ዲሞክራሲ ስልጣን ላይ መውጣታቸውና ይህ በፎቶ የተደገፈው ስነ-ስርዓት አይነት ውጪያዊ እይታ ከውስጥ ያለውን ድብቅ መሰረታዊ እውነታ ግን ብዙም የመቀይረው ነገር አይደለም፡፡በአሜሪካና ዋና መሪነት በምእራባውያን ወራሪነት በኢራቅ የተፈጠረውን ኢ-ሰብዓዊና ህገ-ወጥ ጦርነት ውድመትና ቀውስ በትክክል ከመዘገብ ይልቅ የአሜሪካንን የምርጫ ዲሞክራሲ ስርዓት ብቻ ሰብበ አድርጎ ይህንን አይነት ከበስተጀርባ ያለውን የኢራቅንም ሆነ ሌላውን አይነት ዋና ወሳኝ እውነታ የሚያድበሰብስ የተዛባ ዘገባ ማቅረብ በእርግጥ ከኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች የሚጠበቅ ነገር ነው፡፡አሸባሪነትን መዋጋት በሚል ሽፋን ላለፉት 12 ዓመታት ያህል በተከፈተው አለም አቀፍ ጦርነት የተነሳ የኢራቅን ጨምሮ አሜሪካ በድምሩ በትሪሊዬን ዶላር የሚገመት ወጪ አውጥታለች፡፡
    ይህንን አውዳሚ የጦርነት ወጪ ማነው የሚሸፍነው ከዚህስ አውዳሚ ጦርነት ማነው የሚጠቀመው?በአሜሪካና ከዚያም በቀጣይነት የተፈጠረው የምእራቡ አለም የፋይናንስና የኢኮኖሚ ቀውስ ከእንደዚህ አይነት አላስፈላጊ አውዳሚ የጦርነት ጋር ምን ያያይዘዋል?
    ዋናው መሰረታዊ ጥያቄና እውነታ በዚህ ላይ ነው ማጠንጠን ያለበት እንጂ የጆርጅ ቡሽንና የመለስን ፋውንዴሽን በጥራዝ-ነጠቅና በጠባብ እይታ ማወዳደሩ ላይ አይደለም፡፡
    “ክሊንተን ቀደም ብሎ በተራው ንግግር እያደረገ ሳለ ለፈገግታ ከማገልገልም ባሻገር አንድ ለጥናታችን ጠቃሚ የሆነ ቁምነገር እንደ ቀልድ አድርጎ ተናግሮ ነበር። እሱም፥ “ከስልጣን በኋላ የቀድሞ ፕረዘዳንቶች ፈተና መታሰቢያ ተቋሞች በመገንባት ታሪካቸውን እንደገና ለመጻፍ መታገል ነው እያልኩ ለኦባማ ሁልጊዜ እነግረዋለሁ” የሚል ነበር።” ከፀሃፊው የወሰድኩት ከላይ ያለውን የክሊንተንን አባባል ፀሃፊው ከውጪ ያለውን ሰሙን እንጂ ውስጣዊ ቅኔውን በቅጡ የተረዳው አይመስለኝም፡፡ማለትም እንደ አንድ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆርጅ ቡሽ በስልጣን ዘመኑ የሰራውን ያለፈ ነገር ሁሉ አሁን ለመቀየር ፈፅሞ አይችልም፡፡The passed is passed.ነገር ግን አሁን ለማድረግ የሚቻለው ግን ጆርጅ ቡሽ በስልጣን ዘመኑ እንደ አንድ ፕሬዝዳንት የሰራውን ያለፈ ነገር እንዴት እንደሆነ የማቅረብ የመተረክ የማስታወስ የመገምገምና ፍርድ የመስጠት ጉዳይ ብቻ ነው የሚሆነው፡፡ስለዚህም የክሊንተን አባባል እኔ እንደምረዳው ከሆነ እውነትንና ታሪክን በትክክል ከመዘገብ ከመተርጎም ከመመዘንና ፍርድ ከመስጠት ጋር በተያያዘ ያለንበትን ፈታኝ የዘመናችን ሁኔታ የሚያስታውስ ነው፡፡ወደ እኛ ሀገርም ስንመጣም የመለስ ራእይ እና በተያያዥ ያለውም የፋውንዴሽን ጉዳይ ይህንኑ እውነትንና ታሪክን በትክክል ከመዘገብ ከመተርጎም ከመመዘንና ፍርድ ከመስጠት ጋር በተያያዘ ያለንበትን ፈታኝ የዘመናችን ሁኔታ የሚያስታውስ ነው፡፡ይህ ደግሞ እየሆነ ያለው ከታሪክ እንደምንማረው ሰዎች ከታሪክ አለመማራቸውን ነው የሚለውን የሚያስታውስ ብቻም ሳይሆን ከዚህም በከፋ እውነትንና ታሪክን እያጣመሙ ማቅረብ እኩያን ሃይሎች እኩይ ስራቸው ለዘመናት በብዙሃኑ ዘንድ በቅጡ ሳይመረመርና እውነቱ ሳይገለጥ ተሸፋፍኖና ተዳፍኖ እንዲቀጥል የሚያደርጉበት የረቀቀና የተቀነባበረ መሰሪ ሴራ ጭምር መሆኑን የሚያመላክት ነው፡፡ለዚህም ነው በመግቢያዬ ላይ በውጪ ከሚታየው ከአካላዊ ጦርነት በበለጠም የዘመናችን እጅግ ዋናው ፈታኝ ጦርነት በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለውና ይህንንም ተከትሎ ጭምር ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት ነው ያልኩት፡፡ጆርጅ ቡሽ የጦር ወንጀለኛ ናቸው፡፡በእርግጥ ይህ ሲባል ጆርጅ ቡሽ ወይንም ኦባማ ወይንም ሌላ ይህንን አይነት የኢራቅ አይነት ጦርነት በራሳቸው ስልጣን ብቻ የማድረግም ሆነ ያለማድረግ መብት ያን ያህል አይኖራቸውም፡፡
    በእርግጥ ይህ አይነት ጦርነት በዋናነት የሚመነጨው አሜሪካና ምእራባውያን ከሚያራምዱት የግሎባል ካፒታሊዝም ኒዎ-ሊበራልና ኒዎ-ኮሎኒያሊዝም ኢምፔሪያሊስታዊ ፕሮጀክት የሚመነጭ ነውና ጉዳዩ ጆርጅ ቡሽ ጦረኛ ነው አይደለም ከሚል ጠባብ እይታ በዘለለ በራሱ የስርዓቱ መሰረታዊ ውስጣዊ አሰራርና ባህሪ ነው፡፡ስለዚህም ጆርጅ ቡሽ ወይንም ኦባማ ይህንን ፕሮጀክትና ስርዓት በታማኝነት የሚያስፈፅሙ አገልጋይ መሳሪያዎች(Tools) ናቸው፡፡ሃይለማርያም ደሳለኝ የወያኔ መሳሪያ እንደሆኑት ማለት ነው፡፡ወያኔም የባእዳን ቅጥረኛ መሳሪያ እንደሆነው ሁሉ ማለት ነው፡፡ስለዚህም የመለስ ራእይ ይቀጥላል ፋውንዴሽንም ይሰራ ሲባል ወይንም ጆርጅ ቡሽ የጦር ወንጀለኛ ሆኖ ሳለ ለጆርጅ ቡሽ ይህ አይነት ፋውንዴሽን መሰራቱ የሚያመላክተው በውጪ ከሚታየው ከአካላዊ ጦርነት በበለጠም የዘመናችን እጅግ ዋናው ፈታኝ ጦርነት በእውነትና በሀሰት እንደዚሁም በመልካም ነገርና እና በመጥፎ ነገር መካከል ያለውና ይህንንም ተከትሎ ጭምር ያለው የታሪክ ሽሚያ ጦርነት ነው የሚለውን ነው፡፡ይህም ብቻም ሳይሆን ይህ አይነት ሁኔታ የሚያሳየው አሜሪካና ምእራባውያን ከሚያራምዱት የግሎባል ካፒታሊዝም ኒዎ-ሊበራልና ኒዎ-ኮሎኒያሊዝም ኢምፔሪያሊስታዊ ፕሮጀክት ስርዓቱና የሚያራምደው አውዳሚ ጦርነት ወረራውና አለም አቀፍ ቀውሱ ተጠናክሮ ይቀጥላል ማለት ነው፡፡ጆርጅ ቡሽ በምርጫ ዲሞክራሲ ሁለት ጊዜ የተመረጠ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት እንደሆነ ይታወቃል በዚህም ለጆርጅ ቡሽ ፋውንዴሽን ተመሰረተ ጥሩ እሺ ኪዚያ በኋላ ግን ምንድን ነው ሊታወስ የሚፈለገው፡፡
    አሸባሪነትን የተዋጋና ከምድረ ገፅ ያጠፋ?በአሸባሪነት ሽፋን እራሱን አሸባሪነትን ያስፋፋና ደካማ ሀገራትን በዚህ ሽፋን እንደፈለገው የወረረ?ኢራቅን የወረረና የኢራቅን ህዝብ ለከፋ ስነ-ልቦናዊ ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ ፖለቲካዊ አካባቢያዊ ቀውስ የዳረገ?በዚህ የአውዳሚ ጦርነት አላስፈላጊ ወጪው የተነሳና በሌላም ምክንያት አሜሪካንና አብዛኛውን የአሜሪካንን ህዝብ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ የዳረገ? በጦርነቱና በፋይናንስ ቀውስ ሰበብ የMIC (Military Industrial Complex) እና Wall-Street ሃብታሞችን የበለጠ ሀብት እንዲያከማቹ ያደረገ?እንደ ግለሰብ በእነዚህ አይነት ፋውንዴሽኖች ላይ መቋቋምና መመስረት ብዙም ተቃውሞ የለኝም ወይንም እንዴት እንደተመሰረቱም ቢሆን ያን ያህል ብዙ አያስጨንቀኝም?ዋናው ቁምነገር ግን ለምን አላማ ሲባል ተመሰረቱ የሚለውና በተያያዥም እውነቱና ታሪኩ በትክክል ይቀርባል የተረጎማል መላው አለምና ቀጣይ ትውልድስ ከዚህ ምን ይማራል የሚለው ነው ይበልጥ የሚያሰጨንቀኝ፡፡Successes or failure is the way we present and interpret it እንደሚባለው መሪዎች የሚሰሩት ስራ ለተወሰነው ዜጋ ወይንም የህብረተሰብ ክፍል ወይንም ሀገር ጥሩና የስኬት ሊሆን ይችላል በተቃራኒው ደግሞ ለተቀረው መጥፎና ውድቀት ሊሆን ይችላል፡፡ስለዚህም ይህ አይነት ፋውንዴሽን መመስረቱ እነዚህን አይነት መሪዎች በጥሩም ሆነ በመጥፎ ለማስታወስ ይረዳል፡፡ ዋናው ቁምነገሩ ያለው ግን ይህንን ፋውንዴሽን ምክንያት አድርጎ ለታሪክና ለትውልድ የሚተላለፈው መልእክት ምንድን ነው የሚለው ላይ ነው፡፡እውን በዚህ የቡሽ ፋውንዴሽን ላይ ቡሽና ቶኒ ብሌየር በኢራቅና በኢራቃውያን ላይ የፈፀሙት የጦር ወንጀልና ይህንንም ተከትሎ የተፈጠረውን አጠቃላይ ስነ-ልቦናዊ ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ ፖለቲካዊ ወዘተ ውድመትና ቀውስ በፊልም በመረጃ ተደግፎ ይቀርባልን?ከእኛ በበለጠ ኢራቃውያንስ ምን ይላሉ? ይህ ካልሆነ ግን የፋውንዴሽኑ መመስረት ብዙም ፋይዳ የለውም፡፡
    በእርግጥ ብዙዎቹ ኢትዮጵያውያን ሚዲያዎች የአለምን አጠቃላይ ዘርፈ ብዙና ጥልቅ የሆነ ውስብስብ ሁኔታ ብዙውን ጊዜ የሚመለከቱት በዚህ የፈረደበት የታይታ የምርጫ ዲሞክራሲ እና ነፃ-ገበያ በሚል ጥቅል ጥራዝ-ነጠቅ መነፅር ብቻ ነው፡፡ከዚህ በመነጨም እውነታው በትክክል አይቀርብም፡፡ስለ ቡሽ ፋውንዴሽን ማነፃፀሪያው ደግሞ መለስ ሳይሆን መሆን ያለበት እውነትና እውነት ብቻ ነው መሆን አለበት፡፡እውነተኛ ሚዲያዎች ደግሞ ይህንን አይነት አስተያየት ጭምር አሁንም ወደፊትም ሳይበርዙ ሳይከልሱ ያቅርቡ፡፡

Comments are closed.

Share