“መንግሥት ውስጥ የተሸሸገ ሸኔ አለ” የሰላም ሚኒስትር ዲኤታ ታዬ ደንደአ

July 30, 2022

Tayeየሰላም ሚኒስትር ዲኤታ እና የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ታዬ ደንደአ የግድያ ማስፈራሪያዎች እንደሚደርሷቸው ለቢቢሲ ተናገሩ።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በማኅበራዊ ሚዲያዎች እና በተለያዩ መድረኮች በሚያነሷቸው ሃሳቦች አነጋገሪ የሆኑት ሚኒስትር ዲኤታው፤ በብልጽግና ፓርቲ ውስጥ አለ ስለሚሉት ‘የማፊያ ቡድን’ እና በግል ስለሚደርሱባቸው ጫናዎች ለቢቢሲ ተናግረዋል።

“ድምጼ ታፍኗል”

አቶ ታዬ በቅርብ በተካሄደው የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት ስብሰባ ላይ አስተያየት “እንዳልሰጥ ድምጼ ታፍኗል” ብለው የፌስቡክ ገጻቸው ላይ ካሰፈሩ በኋላ ጉዳዩ የብዙዎች መነጋገሪያ ሆኖ ነበር።

አቶ ታዬ በጨፌው [በኦሮሚያ ምክር ቤት] የሆነው ሲያስረዱ፤ አፈ ጉባኤዋ የዕለቱን አጀንዳ ካቀረቡ በኋላ ምክር ቤቱ በሁለት ተጨማሪ ጉዳዮች ላይ እንዲነጋገር አጀንዳ ለማስያዝ ያደረጉት ጥረት አለመሳካቱን ይናገራሉ።

የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዲኤታ የሆኑት አቶ ታዬ፤ የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት ከመቼውም ጊዜ በላይ “እየተበላሸ መጥቷል” ስላሉት የክልሉ የደኅንነት ሁኔታ አጀንዳ አድርጎ እንዲወያይበት ማቅረብ ፈልገው እንደነበረ ይገልጻሉ።

ሁለተኛው ማንሳት የፈለጉት ጉዳይ ደግሞ “ከሌብነት ጋር በተያያዘ በክልላችን አስተዳደሩ ተዳክሟል” የሚል መሆኑን ጠቅሰዋል።

“እጄን ሳወጣ ይዩኝ አይዩኝ [አፈ ጉባኤዋ] አላውቅም ዝም ብለው አጀንዳ ወደማጸደቅ ሄዱ። ከዚያ ‘ክብርት አፈ ጉባኤ የማነሳው ሃሳብ አለኝ’ አልኩ” ይላሉ አቶ ታዬ።

“ከዚያ ዕድል እንደመስጠት አሉና እንዳልናገር ደግሞ ማይክሮፎኑን ዘጉብኝ። ትንሽ ቆይተው ‘ዕድሉን መጠቀም አልቻሉም’ አሉ። ‘ዝጉበት፣ ዝጉበት’ የሚል ድምጽ ይሰማ ነበር” በማለት አቶ ታዬ በጨፌው አጋጥሟል ያሉትን ለቢቢሲ ተናግረዋል።

አቶ ታዬ አስተያየቴን እንዳልሰጥ የተከለልኩት፤ ምክር ቤቱ በአጀንዳነት የያዛቸው ሪፖርቶች ችግር እንዳሉባቸው ስለሚታወቅ ነው ይላሉ።

ከአንድ ዓመት በፊት የኦሮሚያ የፀጥታ ስጋት በአጭር ወራት ውስጥ ይወገዳል ተብሎ፣ ከአንድ ዓመት በኋላ ስንገናኝ የክልሉ የፀጥታ ችግር ተባብሷል የሚሉት አቶ ታዬ፤ ለዚህ የፀጥታ መደፍረስ ምክንያቱ ምንድን ነው? ተጠያቂውስ ማን ነው? በሚሉ ጉዳዮች ላይ ምክር ቤቱ እንዲወያይ ቢፈልጉም ዕድሉ እንደተነፈጉ ያስረዳሉ።

“በብልጽግና ፓርቲ ውስጥ የተደራጀ ማፊያ አለ”

የብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር የሆኑት አቶ ታዬ፤ በፓርቲው ውስጥ “ሌብነት ላይ የተሰማራ የተደራጀ ማፊያ አለ” ሲሉ ይከስሳሉ።

አክለውም “ለዜጎች ክብር የለውም” ያሉት ቡድን በአካል እንጂ በሃሳብ ብልጽግና አይደለም ሲሉ ተናግረዋል።

“ወረቀት ይዞ ብልጽግና ነኝ ሊል ይችላል እንጂ፣ ይህ ሰው አስፈራርቶ አፍኖ የሚወስድ ቡድን ብልጽግና አይደለም። . . . የታገልንለት ወደ ኋላ እንዲመለስ፤ ማፊያ እጅ እንዲገባ እኛ እንፈልግም” ብለዋል።

አቶ ታዬ በንግግራቸው በኦሮሚያ ክልል አስተዳደር ውስጥ አለ ያሉት የማፊያ ቡድን፣ አባላቱ እነማን እንደሆኑ እንዲሁም “ማፊያ” ያሉት ቡድን ፈጽሟል ስላሉት አሉታዊ ተግባር ያቀረቡት ማስረጃ የለም።

“እዚህ ቡድን ውስጥ ያሉት እነ እከሌ ናቸው ብሎ ለመዘርዘር ጊዜው አሁን አይደለም። ጊዜው ሲደርስ ስማቸውን እንዘረዝራለን” ሲሉ በደፈናው ማለፍን መርጠዋል።

“የደኅንነት ስጋት አለብኝ”

አቶ ታዬ በቅርቡ በፌስቡክ ገጻቸው ላይ የደኅንነት ስጋት እንዳለባቸው ገልጸው ነበር።

“ ‘እንረሽንሃለን…ግንባርህን እንልሃለን’ እያሉ በግልጽ የሚያስፈራሩ አሉ።…ሁሉንም አስፈራርቶ አይሆንም። ሰው መጉዳት፣ ሰው መግደል ይቻላል። ይህ ብዙ ቦታ ሆኗል። ሃጫሉ ሁንዴሳ ላይም ተፈጽሟል” በማለት ጠንከር ያለ አስተያየት ሰጥተዋል።

የግል ጠባቂዎቻቸው እንዲነሱ መደረጋቸውን የሚናገሩት ሚኒስትር ዲኤታው፣ ምንም እንኳ የግድያ ዛቻን ጨምሮ ማስፈራሪያ ቢደርስባቸውም፤ “በትግላቸው” እንደሚቀጥሉ ይናገራሉ።

ቢቢሲ የሚኒስትር ዲኤታ ጠባቂዎች ስለመነሳታቸው ከሚመለከተው የመንግሥት አካል ማረጋገጥ አልቻለም።

“… እኛ ከቤት የወጣነው ለነጻነት ነው። ለሕዝብ ነጻነት ታግዬ ብታፈን በተቃራኒ ጎራ ስለታገልኩ ነው። ዋስትናችን ትግላችን ነው” ሲሉም አክለዋል።

የፎቶው ባለመብት,PROSPERITY PARTY/YOUTUBE

“ለውይይት በሩ ዝግ ነው”

አቶ ታዬ በኦሮሚያ ክልል አስተዳደር ውስጥ አሉ የሚሏቸው ብልሹ አሰራሮችን በንግግር ለመፍታት መንገዶች ዝግ መሆናቸውን ይናገራሉ።

“በውይይት ውስጣችንን ማየት አለብን። በኦሮሚያ ሥልጣን ላይ ያለው ቡድን ግን ይህ እንዲደረግ አይፈልግም። ለውይይት በሩ ዝግ ነው። እኔ በጣም ብዙ ጊዜ ሞክሪያለሁ። ለዚህ ማስረጃ ማቅረብ እችላለሁ። የሚሰማኝ ግን አጣሁ” ብለዋል።

የኦሮሚያ ክልል ደኅንነት ሁኔታ

የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዲኤታው አሁን በኦሮሚያ ክልል ያለው የፀጥታ ሁኔታ “…ወንድ ልጅ የሚደፈርበት፣ አባ ገዳዎች የሚገደሉበት፣ ሰው ወጥቶ መግባት የማይችልበት፣ እጅግ በጣም አስቀያሚ ነገሮች ያሉበት” ሲሉ ይገልጹታል።

አቶ ታዬ የዜጎች ደኅንነትን ማረጋገጥ ሳይቻል ሰው ወጥቶ መግባት ስጋት ሆኖበት ሳለ፤ “በክልሉ አጠቃላይ ስኬት ማስመዝገብ ተችሏል ሲባል፤ ቀድሞ ምን ታቅዶ ነበር” ያስብላል ይላሉ።

“በክልሉ ከተገነቡት ትምህርት ቤቶች ይልቅ የተቃጠሉት ይበልጣሉ። ሕዝባችን መኖሪያ ቤቱ ተቃጥሎ መሄጃ አጥቷል። በሬው ታርዶበት የሚያርስበት የለውም። ያለው ችግር ተቆጥሮ አያልቅም።”

አቶ ታዬ ለጠቀሷቸው ዘርፈ ብዙ ችግሮች እርሳቸው አባል የሆኑበትን አስተዳደርን ተጠያቂው ያደርጋሉ።

“ከሁሉም በላይ የሕዝብ ደኅንነት የማረጋገጥ ኃላፊነት ያለበት መንግሥት ነው። …ስለዚህ በአሁኑ ጊዜ በኦሮሚያ ለተከሰተው ችግር ትልቁን ኃላፊነት መውሰድ ያለበት መንግሥት ነው” ብለዋል።

አቶ ታዬ “ክልሉ ገብቶበታል” ላሉት ችግር ከመንግሥት በተጨማሪ ሌሎች ኃላፊነት መውሰድ ያለባቸው አካላት እንዳሉ ይናገራሉ።

“በሰላማዊ መንገድ ከተማ ተገብቶ ከዚያ በኋላ ወደ ጫካ መሄድ አግባብ አይደለም” በማለት በክልሉ የሚንቀሳቀሰው ታጣቂ ቡድንም “የሰላም ፀር” መሆኑን አንስተዋል።

“ሁለት ሸኔ ነው ያለው”

አቶ ታዬ ከዚህ ቀደም በአሮሚያ ክልል ሁለት ሸኔ ነው ያለው ሲሉ ተደምጠው ነበር።

ሚኒስትር ዲኤታው መንግሥት አሸባሪ ሲል የፈረጀው እና ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ጦር ብሎ የሚጠራው ቡድን አንዱ መሆኑን ገልጸው፤ “ሌላኛው ሸኔ መንግሥት ውስጥ የተሸሸገው ነው” ሲሉ ጠንከር ያለ አስተያየት ይሰጣሉ።

“ጫካ ያለው አለ። ሌላኛው ደግሞ መንግሥት ውስጥ የተሸሸገው አለ። ወንጀል ደግሞ በዚህም በዚያም ይፈጽማሉ። ስለዚህ እኛ ውስጥ ያለ አለ፤ ከውጪም አለ” ብለዋል።

በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ካሉ የፀጥታ ችግሮች አንጻር የመስተዳደሩ መዋቅር ላይ ትችቶች ሲሰነዘሩበት የቆየ ሲሆን፣ ባለሥልጣናትም መዋቅራቸውን ለማስተካከል እርምጃ እንደሚወስዱ በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲናገሩ ቆይተዋል።

“የሥልጣን ጥም የለኝም”

አቶ ታዬ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጾቻቸው እና በተለያዩ መድረኮች አባል የሆኑበትን አስተዳደር አጥብቀው የሚተቹት ‘ሥልጣን ስለሚፈልጉ ነው’ የሚሉ ትችቶች ሲነሱባቸው ይታያል።

አቶ ታዬ ግን ይህ “ቀልድ ነው” ይላሉ።

“ሥልጣን ብንፈልግ ኖሮ በወያኔ ዘመንም አገኘው ነበር። ወያኔ አይደለም ለእኛ አይነት ሰው በአግባቡ መጻፍ ለማይችሉት ሁሉ ሥልጣን ሲሰጥ ነበር። ሥልጣን ፍለጋ እድሜያችንን አልገበርንም።”

አቶ ታዬ አሁን ያሉበት የሚኒስትር ዲኤታ ሥልጣን ከዚህ ቀደም ከነበሩበት ከፍ ያለ መሆኑን ተናግረው፤ “ሰው በየዕለቱ እየተገደለ፣ ኢኮኖሚ እየደቀቀ፣ ወጥቶ መግባት እና በሕይወት መኖር አሳሳቢ በሆነበት ጊዜ ምን አይነት ሥልጣን ያምራል? የማይመስል ነገር ከማስመስል ቢቀር ይሻላል” ብለዋል።

Source- BBC

4 Comments

  1. አቶ ታየ ነገሮችን አገጣጥሜ ሳየው ሽመልስ’ መራራ፤ዳውድ፤ግሪሳው ፤ ከኦነግ ጋር ቀለበት ሳይሰሩብህ አልቀሩም ጠ/ሚኒስተሩም ይህንን እያወቁ ከለላ አለመስጠታቸው ማብራሪያ ያስፈልገዋል፡፡ ለማንኛውም የግሪሳው ፍላጻ አንተ ላይ ለማረፍ እየተምዘገዘገ ነው እንግዲህ ቀድም ባለው ጊዜ ዘረኝነትን ከምታራምድ ለአንድነት ብትቆም ዛሬ አብሬህ እቆም ነበር ያም ሆነ ይህ በሰብአዊነት በሚቻለኝ ሁሉ እንደ ወለጋ አማሮች በስጋ በነብስህ ሰቆቃ እንዳይደርስባት እጥራለሁ አይዞህ የግሪሳውም የነ ሽመልስም የግፈኞች ቀን ይጨልማል፡፡ ከቦታህ ሳትነሳ ስብሃት ነጋን የለቀቀ የፍትህ ተቋም አቶ ታዲዮስ ታንቱንም እንዲፈታ የበኩልህን ጥረት አድርግ፡፡

  2. ይሄ ነገር ግራ ያጋባል ለግሪሳው( ለጁዋር መሃመድ) ጥበቃ ሲደረግለት ለሌሎች ቱባ ወንጀለኞች ጥበቃ ሲደረግ ለአንድ የኢትዮጵያ ሚኒስቴር ጥበቃው የሚነሳበት ከምን የመጣ ውሳኔ ነው? እረ ኦቦ ሺመልስ ጥጋብዎን በልክ ያድርጉት ከጥበቃ ጉድለት አንድ የኢትዮጵያ ሚኒስቴር በጠላት እጅ ቢወድቅ በሚኒስተርነቱ ያገኘው ምስጢር ጠላት እጅ ገባ ማለት ነው? ቦታዎ ነገሮችን በዚህ መልክ ሊያሳዮ በተገባ ነበር። እርሶ ዋናው ስራዎ እርስዎ መባሎንና መንጎማለሎን ስለ ሆነ የስራ ድርሻዎ በእውቀት የተጎዱ ጀሌዎቾዎን የኦነግን ጨርቅ አስይዞ ጃዝ በማለት አገርን ማተራመስ ሁኗል። መቼም እርሶን እዛ ቦታ ላይ ያስቀመጠ ክፉ የኢትዮጵያ ጠላት ነው በእርግጥ ቢፈልጉ እንኳን ከዚህ በላይ መሆን ስለማይችሉ የድንቁርና ስራዎን ቀጥሉበት አንድ ከተማ በቁሙ ሲነድ ከእንቅልፍ አትቀስቅሱኝ ብለው የተቆጡ የኢትዮጵያ ኔሮ ነዎት።

    አቶ ታየም ቀደም ባለው ጊዜ ስያራምዱት የነበረው ተመልሶ እርሶ ላይ መጣ ትክክል ያልሆነ ነገር ሁሉ ውጤቱ ይህ ነው። መለስ ዘራዊ በዘር ሸንሽኖ ድርሻችሁ ያልሆነውን ሰጣችሁ እሩቅ ማየት የተሳናችሁ ለጊዜው እናገኛለን በሚል ስሌት ተጠቅማችሁ አገርን እንዳልነበረ አደረጋችሁ ውጤቱ ወደርሶ ሆነ ካሁን በኋላ ያለው ጉዛ ማን ማንን ይቀድማል ነው ለማንኛውም ጥንቃቄ ጥሩ ነው።
    የህግ እውቀትዎ ብልጭ ሲልቦት የተሰሩ ስራዎች ሁሉ ትክክል ያለመሆናቸውን ህሊናዎ መልእክት ሳያደርሶት አይቀርም። እኔማ ምን አገባኝ ያሉበት ሁኔታ ቀደም ሲልም የምጠብቀው ስለሆነ የመኖሮ ጉዳይ አሳስቦኝ ነው። ለሃጫሉ ያልሳሱ ለእርሶ ይመለሳሉ ብዬ አልገምትም። እኔማ በዘሬ በሃይማኖቴ በማንነቴ ጥቃት የማይደርስብኝ አገር እየኖርኩ ይህ ወደ ሃገሬ እንዲደርስ ፍላጎቴ ነበር ታዲያ የኬኛ አርበኞች ትግሬ አቡክቶ ጋግሮ የክፋት እስትንፋስ ስለዘራችሁበት ካሁን በኋላ ሮቦት እንጅ ሰው ለመሆን እንደማትችሉ ተገንዘበናል። ቢችሉ አመሻስ ላይ ከቤቶ አይውጡ፤ ስለ እንቀስቃሴዎ ለማንም መረጃ አይስጡ፤ ቢሮዎ የሚሄዱበትን ሰአት ይለዋውጡ፤ አለባሌ ሰው ሁኖ መሄዱንም ተለማመዱት፤ ብዙ ገንዘብም ጭነው አይውጡ ይህም አንደም እንደ ናዘሬቱ ሊወስድቦት ይችላል አንደም የህዝብ ገንዘብ ሰርቆ ከሃገር ሊወጣ ነው ሽመልስ አብዲሳ በኤግዝቢትነት ያስመዘግብቦታል።ሰላም ይሁኑ ከተቻለ እንዴት ያለ ክፉ ጊዜ ላይ ደረስን።

  3. አቶ ታየ ግሪሳው ሸኔ የሚባል የለም ብሏል ትክክለኛው እርሶ ነዎት ወይስ ጁዋር መሃመድ ወይስ በተሰበጣጠረ መረጃ ህዝቡን እንክፈለው ከሚል እሳቤ የመጣ ነው? ጃል መሮም እኔ የምመራው የኦሮሞ ሰራዊትን ነው እንዲህ ያለ ወሮበላ ቡድን እኔዘንድ የለም ብሏል እርሶስ ስለ ሁኔታው ግልጽልጽ አድርጎ እንድ ነጋሳ መናገር ምን አስፈራዎት? ነገሩን ውስብስብ አያድርጉት እንጂ አንድ ነብስ ነው ያሎት በነብስ ወከፍ እራሶን ለመጠበቅም ምናምን አያጡም እንዲህ ያለ የፍርሃት ቆፈን ምንድነው? ስጋት ካለቦት አዘውትረው ይጻፉ ህዝብ ዉሎዎን ያዳምጣል ቀደም ሲል ተው ይሄነገር ማንንም አይጠቅምም ብለን ነበር ማን ይስማ በዘመነ ጥጋብ ሁሉ የኛ ነው ነው፤ለክተን የምንሰጣችሁ እኛ ነን ነው፤ከአዳም ጀምሮ ታሪክ ስርተናል አዳምጡን ነው አገር ምድሩ ኦሮሞ ነበር የምትሉት። አቶ ታየ አንድን ሰው ትግሬ፤አማራ፤ኦሮሞ የሚያደርገው ምንድነው? በተለይ እንደ ኦሮሞ በታሪኩ ሙሉ ሲዘዋወር ለኖረ ጎሳ ክልልና ማንነት ላይ ሙጥኝ ማለት ጥሩ ይመስሎታል? አሁን ጁዋርና በቀለ ገርባን፤ክነጋሶ ጊዳዳ፤በያን ሱጳ፤ዳውድ ኢብሳ፤ሌንጮ ለታ ጋር የሚያመሳስላቸው ምን አለ? የነጋሶ ጊዳዳ፤ብርሃኑ ጁላ፤የመሳሰሉ ቱባ ኦሮሞነት የተስጣቸው ምን ሁነው እንደተገኙ ሳይሰሙ አልቀሩም። ለማንኛውም ትግሬዎች ጭነውብን የሄዱት ነገር በተባበር ክንድ ካልሆነ ልንወጣው ይክበዳለ።

  4. “መንግሥት ውስጥ የተሸሸገ ሸኔ አለ”
    It would be closer to the truth to say that there are a few non-Shene people in the OPDO leadership and the palace. Abiy is/was not one of them.

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Abiy 71
Previous Story

ለአገሩ ባዳ! – አገሬ አዲስ       

295922611 640027501021842 2363535761675940881 n 1
Next Story

የባልደራስ ተወካይ ከአሜሪካ መንግስት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልእክተኛ ጋር ተወያየ

Go toTop