የአሜሪካ መንግስትን ጫና ፣በቆራጥ የልማት ትግልና ለመሰዋትነት ዝግጁ በመሆን እንቋቋመዋለን (መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ)

” የዚህ ዓለም ነገረ እጅግ ይገርማል ። ሰው ከዚህ ቦታ መጣ ሳይባል ይወለዳል ። በዚህም ዓለም ጥቂት ጊዜ ሲታገል ቆይቶ በሱ ፈንታ የሚታገሉትን አዲሶች ሰዎች ተክቶ ያልፋል ፤ ይረሳልም ። ሰው ለምን እንዲፈጠር ለምንስ እንዲሞት እንዲህ ነው ለማለት ግን ሥራችን አይደለም ።ሰው ሁሉ ለራሱ የሃይማኖት ካህናት አሉትና ከነዚያ ይጠይቅ ።እንደዚሁም ደግሞ ህዝቦች ይወለዳሉ ፤ ይሞታሉም ፤  ይረሳሉም ።ህዝቦች ከተፈጠሩ ዠምሮ እሥኪያልፉ ድረስ ምንም ህዝቦቹ ዘራቸውና ቋንቋቸው ልዩ ፣ ልዩ ቢሆን አስማምቶ የሚያስኬደው ሥርዐት ግን መሠረቱ አንድ ነው ። ሁሉም ምድር የምትሰጠውን ሲሳይ ለማግኘት ይጥራሉ ።ቢያገኙ ይበላሉ  ፤ ይጠጣሉ ፤ ይለብሳሉ ፤ ይመቻቸዋልም ። ቢያጡም ይራባሉ ፤ ይጠማሉ ፤ ይታረዛሉ ፤ ይቸገራሉም ።

ሕዝቦችን ሁሉ የሚፈጥር አንድ አምላክ ነው ። ይህም አምላክ የምንለው የሕዝቦች ፈጣሪ ሕዝቦቹን ሁሉ ትክክል አድርጎ ፈጥሮ ፣ላኗኗራቸውና ለልማታቸው የሚያስፈልጋቸውን ነገር ሁሉ ከሙሉ ፈቃድና ሥልጣን ጋር በጃቸው ሰጥቷቸዋል ። ስለዚህ ማናቸውም ሕዝብ ቢለማም ቢጠፋም በገዛ እጁ ነው ። ሕዝብ የሚጠፋበት አንዳንድ ጊዜ ምክንያት ቢገኝ  ያውም ምክንያት ባንዳንድ ሰው ቢመካኝ ነገሩ ትክክል አይሆንም ። የልማትን መንገድ ለማግኘት የሚጥር ህዝብ ቢገኝ ባንዳንድ ክፉ ሰው ምክንያት ሊጠፋ አይችልም ። እንዲሁም ደግሞ የልማትን መንገድ ለማግኘት የማይጣጣር ሕዝብ ባንዳንድ ደኅና ሰው ኃይል ልማት ሊያገኝ አይችልም ።ደግሞም ማናቸውም ህዝብ የሚለማበት መንገድ አንድ መንገድ ብቻ ነው ። ማናቸውም ህዝብ የሚጠፋ ይህንን የልማት መንገድ ትቶ በሌላ መንገድ የሄደ እንደሆነ ነው ። ”

( ተፃፈ ከነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ የካቲት 1 ቀን 1916 ዐ/ም  በአልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን ማተሚያ ቤት ታተመ ። አሳታሚው  አቶ ጳውልስ መናመኖ ናቸው ። )

 

ባላባራስ ገ/ሕይወት ባይከዳኝ ፣ የሰው ሥብስብ የሆነው የአንድ አገር  ህዝብ ፣ በጥረቱ ፣ በግረቱ ና በቆራጥ ትግሉ እንጂ በሥንፍና እና በወሬ የሚያጠግብ እንጀራ ና ንፁህ ውሃ ለማግኘት  እንደማይችል ፤ የዛሬ 97 ዓመት ፣ “ መንግሥትና የህዝብ አስተዳደር ። “ በማለት በፃፉት መፀሐፍ የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲነቃ ምክራቸውን በፅሑፉ መቅድም ለግሰዋል ።

ነጋድረስ እውነትን አውቀን ፣ በሥራ መበልፀግ እንደምንችል ፣ መንግሥትም ቆሞ ቀር እንዳይሆን ከዘመኑ ጋር እንዲራመድ ፣ በመፀሐፈቸው በትሁት ቋንቋ መክረዋል ።

እውነት ነው ።  አውሮፖዊው ፣ አሜሪካዊው ፣ ኢሲያዊው  ሰው ፤ በተፈጥሮው ከአፍሪካዊው አይበልጥም ። ሁለቱም ሰው እና የዓምላክ ፍጡራን ናቸው ።ምንም እንኳን አውሮፓዊው በተቀናጀ የብዝበዛ  ትብብር አፍሪካን በመውረር ፣አፍሪካ  በራሷ መንገድ ወደ ሥልጣኔ እንዳታመራ ፣ ህዝቧን ለባርነት ፣ የተፈጥሮ ሀብቷን ለምዝበራ ፣ ቢዳርገውም የአፍሪካዊያኑንን ሰውነት ለመፋቅና ከሰው በታች ለማድረግ አልቻለም ። በእርግጥ አንዳንድ የነጭ ምሁራን አፍሪካን ከሰው በታች የመመደብ የግብዝ ፅሑፋቸውን ይፋ ቢያደርጉም ፣ ዛሬ አፍሪካ በአእምሮ ከነጮች ከፍተኛ ብልጫ ያላቸው ዜጎች እንዳላት በተግባር አረጋግጣለቸ። ይህ እውነት ሆኖ ሣለ አፍሪካ ለምን የድህነት ተምሣሌ ሆና ቀረች ?

የጥያቄው መልሥ ቀላል እና ግልፅ ነው ። አፍሪካ ያልበለፀገችው እንድትበለፅግ የማይፈልጉ ምእራብያውያን  በዝባዦች ፣ በላይዋ ላይ ሰፍረው የተፈጥሮ ሀብቷን ለዘመናት በመመዝበራቸውና ዘሬም ፤ ለብዝበዛ የተመቹ ፣ የገዛ አገራቸውን ሀብት በመዝረፍ ወደእነሱ አገር የሚያሸሹ መንግሥታትን ለሥልጣን በማብቃት ፣ያለማቋረጥ  እየመዘበሯት በድህነት አረንቋ ውሥጥ ሥለጨመሯት ነው ።

ዛሬም ይሄው እኩይ ድርጊት ፣ ዘርፈው በማይጠረቁ  ባዕዳን ባለፀጎች የአፍሪካ መንግሥታት እጅ በመንግሥቶቻቸው ይጠመዘዛል ። በዝባዦቹ ቆም ብለው ለማሰብ ከማይችሉ ከሰው ተርታ ከወጡ ፣ ዛሬም በኢትዮጵያ ህዝብ ጫንቃ ላይ ሆነን አገሪቱን ለበዝባዦች አሳልፈን ካልሰጠን ከሚሉት ጋር መሠለፍ ነውና ፍላጎታቸው አርቆ አሳቢ የነቃና የበቃ መሪ አይፈልጉም  ። እነሱ የሚፈልጉት ከብዝበዛ አጋራቸው ጎን መሠለፍ ነው ።

መሰለፍ ብቻ ሳይሆን በትግራይ ውሥጥ በምግብ እጦት ሰዎች እንዲሞቱ ምቹ የዳቢሎስ መንገዶችንም ከወዲሁ ሲቀይሱ እየታዘብናቸው ነው  ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በመቐለ የሚገኘው መስፍን ኢንዱስትሪያል የአሸባሪው ህወሓት የመሳሪያ ማከማቻ፣ መስሪያ እና መጠገኛ ሆኗል።

እብዶ በገብያ እየዞረች “  ማታ ቤት ይቃጠላል ። “ እያለች ሥትናገር ማንም የሰማት አልነበረም ። እናም ማታ እራሶ በአንድድ ቤት ላይ እሳት ለኩሳ ቤቱን ማቃጠል ጀመረች ። ጎረቤትም ጩኸት ሰምቶ እየተሯሯጣ ወጣ ። እርሷም  “ ቤት ይቃጠላልል ብዬ አልነገርኳችሁም ነበር ? “ እያለች መሣቅ ጀመረች ።

ይህ ተረት ፣ ለእኛ አሥተማሪ ነውና የቱጃሮቹን መንግሥታት ሤራ እናውቃለን ። ” የዘራፊው ማፍያ ቡድን ” እዛና እዚህ በመፍጠር ፣ ዘርፎ ና ቀምቶ በላተኛን ለማበራከትና የእርዳታ እህል ለተረጂው በቀጥታ እንዳይሰር እየተደረገ ነው ። ይህንን በሴራ የተቀነበበ  እኩይ ድርጊት   ደግሞ በኤርትራ ጦር  ይላከካል ።

የዲጃታል ወያኔም የጥቁር ውሸት  ፕሮፖጋንዳ ማሽን  የኤርትራ ና የኢትዮጵያን ጦር በሐሰት ይከሳሉ ። እና ሚሊዮንም ሚሊዮን ውሸት ይፈበርካሉ ።እነ 360ም ሱሪ በአንገት ይውለቅ በማለት የእብድ ጩኸት ይጮኻሉ ።

ሚሊዮን በብዕሩ በጎ ሥራዎችን  ጭምር ፕሮፖጋንዳ ያደርጋል ። ወያኔ ከልማት ባንክ  በጀነራል ክንፈ አማካኝነት ወሥዶ የጨረገደውን የተለያዩ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች  በቢሊዮን የሚቆጠር የልማት  ገንዘብ መንግስት ፤” እነዚህ የልማት  ደርጅቶች ያለብሉትን ገንዘብ መክፈል የለባቸውም ።” ብሎ ያለ አግባብ የተጫነባቸውን ዕዳ  መሠረዙ እና የተሻለ ትርፋማ ሆነው እንዲቀጥሉ አዲስ ና ያልተሄደበትን መንገድ መምረጡ ነውሩ ምኑ ላይ ነው ?

ወደ ብልፅግና መራመድ ምን ነውር አለው ? ነውርስ በአገርና በህዝብ ላይ የውንብድና ተግባር መፈፀም ነው ። ነውርስ እጅግ በበዛ ትዕግሥት ሲለምናቸው የነበረውን የኢትዮጵያን መንግሥት ምንም አያመጣም ብሎ መናቅ ነው ። የንቀት ውጤትም በተግባር ታይቷል ።ወር ባልሟላ ፣ ቀናት ውሥጥም ማፍያው ወያኔ ወድሟል ። ሞቷል ።  ዛሬ ” ከመቃብር አውጥቼ  አነግሰዋለሁ ። ” ይላል  ያ ሰው ። ( የአሜሪካ ህዝብ ግን ይህንን ሃሳቡን ይቀበለዋልን ?  የአሜሪካ ህዝብና ሴኔቱ  ከጥበብ የራቀ ነውን ?  ወያኔ ግፈኛ፣ በሰው ሥቃይ የሚደሰት ፣ ነውረኛ ፣ ባለጌ ፣ ነፍሰ ገዳይ እና በአለም ተወዳዳሪ የሌለው ውሸታም እንደሆነ  አያውቅምን ? በእየ እሥር ቤቱ ያሰቃያቸው ፣ በየሜዳው ያለፍርድ የገደላቸው  ፣ በሱማሌ ክልል እና በትግራይ ባዶ ሥድሥት የፈፀመው ለጆሮ የሚገለማ ድርጊትን እንደፅድቅ ሥራ ይቆጥራልን ? )  ።

እርግጥ ለማይገባቸው ጥቅም ሟቾቹ የአሜሪካ ባለስልጣናት ና ተባባሪዎቻቸው ፣ ለጥቅማቸው ሥኬት ወይም የበለጠ ሀብት በዘረፋ ለማካበት ማንኛውንም እኩይ ድርጊት ለመፈፀም ወደኋላ እንደማይሉ ይታወቃል ። የአሜሪካ መንግሥትም ፣ የዓለምን ኢኮኖማ ለመቆጣጠር የሚፈልጉ  ቱጃሮችን ለማሥደሰት የአፍሪካን የፖለቲካ ትኩሳት ፣ በጎራ ተከፋፍሎ እንዲግል ዘወትር እንደሚባዝን ከዓለም የተሰወረ አይደለም ።

የሁለት ጎራ የፖለቲካ ትኩሳቱ የበለጠ  እንዲግልም  ፣በትዕዛዙ መሰረት በሚሾሩት የጎረቤት አገራትና ለጥቅም ባደሩ የውስጥ ፖለቲከኞች ይጠቀማል ፡፡  የገንዘብ ችግር በሌለባቸው በራሱ  ሚዲያዎችም በመታገዝ ሐሰተኛ ፕሮፖጋንዳ ያለማቋረጥ በመንዛት የአለም ህዝብን ያደናግራል ፡፡  በእንዲህ አይነት መንገድ ነው  ፣ ዛሬም እንደትናንት የአሜሪካ መንግስት አሥቀድሞ ወደ አቀደው ኢትዮጵያን የማጥፋት እኩይ ተግባር በስም ብቻ ካለው ፣  ከማፍያው ወያኔ ጋር ለመስራት የወሰነው ፡፡

” ባልበላውም ፣ እበትነዋለሁ ፡፡ ” በሚል የዶሮ ጭንቅላት ሃሳብ በጭፍን የሚጓዘውም የወያኔ ርዝራዥ ፣ ውንብድናንን እንደሥራ በመቁጠር ፣ የትግራይን የከተማ ኗሪና አርሶአደር  ሰርቶ እንዳይበላ በዘረፋ እና በሌብነት እያሥቸገረው  እንደሆነ እያወቁ ግፋ በለው በማለት ያበረታቱታሉ።

የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ መገንዘብ ያለበት ያለማጋነን በ30ሺና በ40ሺ የሚቆጠሩ እሥረኞችን ከእሥር ቤት በመፍታት ከፊሉ ወደ ሰላማዊው ከተሜና አርሶ አደር እንዲቀላቀሉ አድርጓል ። ከነዚህ እሥረኞች ግማሾቹ አውዳሚ ሃሳብ ና ምግባር ያላቸው ፣ ማህበረሰቡን ለመጉዳት የተለያየ  ካራ የሚመዙ ናቸው ።  ዛሬ በትግራይ ኗሪ ሰው ላይ እየተፈፀመ ያለው ነውረኛ ድርጊት በዋነኝነት በእነዚህ ምግባረ ብልሹ ሰዎች  የተከሰተ ነው ።

ዋና ተዋንያኑ ማፍያው ወያኔ እነደሆነ አትጠራጠሩ ፡፡ ወያኔ እኮ ሐሰተኛ ጦርነት በመፍጠር የሚታወቅ ነው ። ዛሬም የቆረጣ ፕሮፖጋንዳ ሥልቱ አልነጠፈም ።” ዕድሜ ህሊናቸውን በከተማ የተደላቀቀ ምቾት ፣በቮድካና በሐሺሽ ላጡ ግብረአበሮቼ !” እያለ  ፣ ያለእረፍት ይሄን የውሸት ፕሮፖጋንዳ  ማሽኑን እያስጓራ ዛሬም ህዝቡን ” መና ከሰማይ አወርድልሃለው ” ። በማለት ለማሞኘት ይጥራል ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የ6ኛ ዙር ፓርላማ አንደኛ ዓመት የሥራ ዘመን በ3ኛ አስቸኳይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያቀረብናቸው ጥያቄዎች፤

ዛሬም ያለማቋረጥ ውሸትን የሚነዛው ሂትለራዊው ና ሞሶሎኒያዊው የፕሮፓጋንዳ ማሽኑ አልተዘጋም ። እንደውም ብሶበት በቆረጣ ሥልት ቀጥሏል ። ሽብርን ፣ አሥገድዶ መድፈርን  ይፈፅምና ” ይኸው የኢትዮጵያ መንግሥት የህዝቡን ሰላምና ደህንነት መጠበቅ አልቻለም ። ” ይለናል ።

እንሆ ዛሬ ደግሞ ሞቶ ተቀብሮ ተሥካሩ እየተበላለት ሣለ ፤ ወያኔ አለ ለማሰኘት ፣ ህዝብን በርሃብ አለንጋ ገርፎ ለመግደል በብርቱ እየሰራ ነው ። የአሜሪካ ና አንዳንድ የአውሮፖ መንግሥታትም ይህንን እኩይ ድርጊቱን ደግፈው ውሸትን ያንጫጩታል።…

የትግራይ ህዝብ ከወገኑ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር በማበር ፣ ይህንን እኩይ ድርጊት ለማሥቆም   በጋራ መቆም እና እንቢ ለፋሺስቶችና ለዘረኞች ማለት አለበት ። በግልፅ ዘረኛውን እና የሞሶሎኒንን ስልት ተከታዩን ወያኔን ማውገዝ ብቻ ሳይሆን ከከፋፋይ ሃሳቡና አመለካከቱ  በተቃራኒ ተሠልፎ እኩይ ድርጊቱን ማሥቆም አለበት  ። ” የአገሬ ጅብ ይብላኝ ! ” በማለት በህይወቱ መቀለድ የለበትም ። ጅብ ጅብ ነው ። ጅብ ከሚበለው በልቶትት ቢቀደሥ ይበጀዋል ።

የክልሉም ሆነ ፊደራል መንግሥት  ህዝቡን በግልፅ ማወያየት ና ይህንን ሴራ እንዲገነዘብ ማድረግ አለበት ።ይህም በሚዲያ በተከታታይ መለቀቅ ይኖርበታል ። ያላቋረጥ የእውነት የፕሮፖጋንዳ ሥራ መሠራት አለበት ።  ጥቂቶችን ለማሥደሰት ብዙሃኑንን ማሠቃየትም ማብቃት አለበት ። ሁሉም በሙያው አግባብ የሆነ ሥራ መሥራት ግዴታው ነው ። ካልሰራ ከቦታው ሊነሳ ይገባዋል ።

ለህዝብ እውነትን ማሳወቅ የማይችል ሚዲያ ለአገር የሚጠቅም አይደለም ። ለደሃው የትግራይ ህዝብ ዛሬ ዳቦ ቀዳሚ ጥያቄው ነው ። ዳቦ እንዳያገኝ ግን ጥጋበኞቺ እያሴሩ ና በየመንገዱ አድፍጠው ሰው እየገደሉ ነው ። ያውም የእርዳታ ሠራተኞችን ።

ይህንን እውነት የትግራይ ህዝብ ሊያውቅ ይገባል ። ከአወቀና ከተገነዘበ በኋላ ምርጫው የራሱ ነው ።  ከእውነት ጋር በመቆም ሐሰትን ተዋግቶ በማሸነፍ በላቡ ሠርቶ በልፅጎ መኖር አልያም ሁሌም ተመፅዋች በመሆን በየወሩ ሥንዴ እየተሰፈረለት የመከራ ህይወትን መግፋት ? ( ይህንን የዱቄት ሰፈራ ነበር ወያኔ ለ27 ዓመት  ሲከውን የነበረው ። )

በነገራችን ላይ የትግራይ ኗሪ ህዝብ በሌሎች የኢትዮጵያ ክልሎች ሠርቶ በመበልፀግ ይታወቃል ። ይሁን እንጂ ይህ የዜግነት  ዕድል እንዲጠፋ እና ሰዎች እንደ ዱር እንሥሣት በጉልበተኝነት ላይ ተመሥርተው በመበላላት እንዲኖሩ እንዲፈናቀሉ ዛሬም በመቃብር ውሥጥ ለሆነው የገጣይ እና አስገንጣይ ቡድን በውጪ አገር በሚኖሩ ፣ ዶላር ባሰከራቸው ህሊና ቢሶች  ይጮኸለታል  ። ይህ አፍረተ ቢስነት ነው ፡፡ ኢትዮጵያ የሁላችንም ናት ፡፡ የትግራይ ህዝብም የትም ሰርቶ የመበልፀግ መብት አለው ፡፡ ዛሬ ግን የትግራይ ህዝብ አገር እንደሌለው ተቀጥሮ ለጂቦች ሰለባ እንዲሆን እየተደረገ ነው ፡፡ እንደትላንቱ ለእኩይ ዓላማቸው ሊማግዱት በጥቁር ፐሮፖጋንዳቸው እያመቻቹት ነው ፡፡

የኢትዮጵያ ህዝብ ይህንን እኩይ ዓላማቸውን ተገንዝቦ ፣ በተቀናጀ መልኩ ፣ ዳር ድንበሩን ለመጠበቅ ዝግጁ መሆን አለበት ። የየክልሉ ልዩ ኃይልም ወደ ጦር ሠራዊቱ በአሥቸኳይ መቀላቀል አለበት ። በአዲሱ በጀት ዓመት ይህ ሥራ ተግባራዊ ከሆነ የኢትዮጵያ የሠራዊት ችግርና የሠራዊት ምልመላ ችግርም ይቀረፋል ። ኢትዮጵያ እንድትሸነሸን የሚጥሩም ቁርጣቸውን ያውቃሉ ።  ይህንን እውነት ሲመለከትም  በመላው ኢትዮጵያ ከተሞች ተከባብሮ የሚኖረው ልዩ ፣ ልዩ ቋንቋ ተናጋሪ የሆነው ኢትዮጵያዊ ዜጋ  ልቡ ይረጋጋል ። ለአገሩ ለመሞትም ከቶም ወደኋላ  አይልም ፡፡

በዴሞክራሲ ሥም ዴሞክራሲን እየረገጡ ፣ በፍትህ ሥም በፍትህ እያላገጡ እኛ የዴሞክራሲ ጠበቆች ነን ። እኛ የፍትህ ዘበኞች ነን የሚሉንንም የምናሳፍራቸው በዚህ መንገድ ብቻ ነው ፡፡ ከላይ የጠቀስኩት ሲተገበር  በምን አይነት የሞራል እውነታ ውሥጥ ሆነው ፣በህዝብ ቅቡልነት ያለውን መንግስት እንደሚቃወሙ እናያለን ፡፡…

ኢትዮጵያውያን ፣ አዲስ አበባ የእኔም አገር ነው  ፤ድሬደዋ የእኔ አገር ነው ፤ አዳማ የእኔ አገር ነው ፤ አዋሳ የእኔ አገር ነው ፤ ባህር ዳር የእኔ አገር ነው ፣ ወዘተ ። ብለው ያምናሉ ። በትግሪኛ ተናጋሪነቴ ሰውነቴን ክጄ ትግራይ ለትግሪኛ ተናጋሪዎች ብቻ መሆን አለበት ፣ የሚል ትግራዊ እንደህዝብ አለ ብዬ አላምንም ።  ከመሐል አገርም ” ጓዜን  ጠቅልዬ ወደ ትግራይ መሄድ ነው ያለብኝ ፡፡ ” የሚልም ትግሪኛ ተናጋሪ የለም ።ሰው  ለመኖር በዓለም ደረጃ መተባበር ግዴታው ነው ። እናም እያንዳንዱ ሰው ኢትዮጵያም ይኑር አሜሪካ  ሥለፍቅር ፣ ሥለሠላም ፣ሥለትበብር ና አብሮነት ፤ እንዲሁም ሥለ ልማትና ብልፅግና ለማሰብ የሚገደደው ለራሱ ህይወት ፍሥሐ ሲል እንደሆነ አውቃለሁ  ። ምክንያቱም ህይወት አጨር ናት ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በኖርዌይ ለግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል የተደረገ የገቢ ማሰባሰቢያ በስኬት ተከናወነ

እኛ ሰዎች ነን። ህይወታችንም አጭር ናት ። በዚህ አጭር ህይወት በቋንቋ እንድንነታረክ ባደረጉን ወያኔዎች ሰበብ ህይወታችንን መራራ ማድረግ የለብንም ።

እኔ የምናገረው ቋንቋ አማርኛ ቢሆን ሰው ነኝና ሰው ለሆነው ለማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ ልቤ ክፍት መሆን ይኖርበታል ። ኦሮምኛ ፣ ትግሪኛ ፣ ሲዳማኛ ፣ ሱማሊኛ ፣ አፋርኛ ፣ ኩናምኛ ፣ አኝዋክኛ ፣ ወላይትኛ ፣ አደርኛ ፣ ከፍኛ ፣ሐመርኛ ወዘተ ልናገር ።ይህ ቋንቋዬ ግን በምንም ዓይነት መንገድ ከሰውነት ተራ አያወጣኝም ። በቋንቋዬ ምክንያትም ዜግነቴን አላጣም ። የዓለም የኑሮ መሥተጋብርም ይሄው ነው ።

በአማርኛ ፣ በኦሮምኛ ፣ በሱማሊኛ ፣ በትግሪኛ ፣ በሲዳምኛ ፣ በአፋርኛ ፣ በወላይትኛ ፣ በጉራጊኛ ቋንቋ ወዘተ።  ትግባባለህ እንጂ አንተ ሰው ነህ ። አንተ ማለት ማሰብና ማመዛዘን የምትችል ባለ አእምሮ ሰው ነህ ። አንዳንድ ባለፀጋ  አገሮችን በሞራል ያልበለፀገ አእምሮ ያለው ለዘረፋ የቋመጠ ቱጃር ያሽከረክራቸዋል። ” ሁሌም ድሆች ከበለፀጉ ለብዝበዛ አይመቹምና እንዳይበለፅጉ እንኮርኩማቸው ፤  ለእኛ ታዛዥ የሆነ አሻንጉሊት መንግሥትም እንፍጠርላቸው ። ” በማለት የአገሩን መንግሥት ይጎተጉታል ። ( ትላንት አባቶቹ የከበሩት በአፍሪካ ጥሬ ሀብት እንዲሁም  በባርያ ነግድ ፣በጥቁሮች አእምሮ ና ጉልበት  ነውና ዛሬም በእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ  የአፍሪካን ሀብት ሙጥጥ ማድረግ አለብን በማለት ቆርጠው ተነሥተዋል ፡፡ )  መንግሥታቸውም ፣ባለው የኢኮኖማ አቅም  በመታገዝ ደሃ አገራትን እንዲበዘበዙ ያሥገድዳል ። በዚ ሳቢያም ፣ በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር አፍ አውጥቶ ከውሸት ጋር በመወገን   መናገር ሲጀምር  ፍትህ ደብዛዋ ይጠፋል ። ሰብአዊ መብትም ይጨፈለቃል ።

በአፍሪካ እየሆነ ያለው ይሄ ነው ። ገንዘቡን ያገኙ ለውሸት ተገዝተው ሲቀባጥሩና ምንም የማያውቀውን ህዝባቸውን ፣ ለችጋር ፣ለሥቃይ ፣ ለመከራ ፣ለሥደትና  ለሞት ሢዳርጉት እናሥተውላለን ።

ዛሬም እነዚሁ ሞራለ ቢስ የአሜሪካና የአውሮፖ የመንግሥት ባለሥልጣናት ለጥቅማቸው ሲሉ  እኛንም ከ2010 ዓ/ም በፊት ወደ ነበርንበት የበዝባዦች ሥርዓት ሊመልሱን ይፈልጋሉ ። እነሱ ምንጊዜም ከዱቄቱ እንጂ ከሚለፋው ህዝብ ድካም ጋር አይደሉም ። በለፀገ አልበለፀገ ደንታ የላቸውም ።  እያንዳንዱ የአፍሪካ መንግሥት የትም ፈጭቶ ዱቄቱን ሊሰጣቸው ካልቻለ በመንግሥትነት መቀጠል አይችልም ። ወደደም ጠላ ትንሽ ለራሱ እየቆነጠረ በማሥቀረት አብዛኛውን  የአገሩን ሀብት ወደ አገራቸው እንዲያግዙ ማድረግ ይጠበቅባታል ።

ይህ እንዲሆን የኢትዮጵያ መንግሥት አልፈቀደም ። ያልፈቀደውም   እኛም እንደ አውሮፖና አሜሪካ የመበልፀግ መብት አለን።  “ አገሬን አልበዘብዝም አላስበዘብዝምም ።”   በሚል ፅኑ አቋሙ ነው።    ይህ የመንግሥታችን ሃሳብ በመላው ዜጋ የሚደገፍ ነው ። መንግሥታችን በአቆሙ እንዲገፋበት መላው ህዝብ ይፈልጋል ። በትጋት ለብልፅግናችን ከመታገል ውጪ ሌላው መንገድ የባርነት መንገድ ነውና የመንግስታችንን አቋም የምንደግፈው ከዚህ አንፃር ነው ፡፡ታላቁ ሊቃውንት ነጋድራሥ ገብረሕይወት ባይከዳኝ እንዳሉት

” ሰው ሲፈጠር ከፍ ያለ አእምሮ ተሰጠው ፡፡ ከፍ ባለው አእምሮውም ላይ በጊዜ ብዛት እውቀት ጨምሮበት የምድር ጌታ ሆነ ፡፡ይህንን እውቀቱንና ጌትነቱን ግን ሰው በአንድ ጊዜ አለገኝም ፡፡ ከተፈጠረበት ጊዜ ዠምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ባለፈው ዘመን ውስጥ ብዙ ጊዜ በትጋት ታግሎ ነው ያገኘው ፡፡ “

1 Comment

  1. ጎበዝ ይሄ ዮሀንስ አብረሀም የተባለው ትግሬ ይሆን ችካል የሚያስተክልብን?

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share