በአርባ ምንጭ ከተማ ተሰብስቦ የቆየው የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) ዛሬ ባወጣው መግለጫው በክልሉ እየተነሱ ያሉ አዳዲስ የክልል እንሁን ጥያቄዎችን አጽንኦት ሰጥቶ መወያየቱን አስታወቀ:: በፌዲራሊዝሙ ጉዳይም “ህዝቦችን በፍትሃዊነት መንገድ ማስተናገድ የሚችል የፌደራሊዝም ስርዓት እያጠናከርን መሄድ ለክልላችን ህዝቦች የህልውና ጉዳይ ነው፡፡” ሲል በአቋም መግለጫው ገልጿል::
https://www.youtube.com/watch?v=14ql5rq_pMI
“አሁን በክልሉ ውስጥ የሚነሳውን ተጨማሪ ክልል ሆኖ የመደራጀት ጥያቄ መላውን የክልሉን ህዝብ በሚጠቅም አኳሃን በተረጋጋና እጅግ ኃላፊነት በተሞላው እና ዘላቂ መፍትሄ በሚያመጣ መንገድ በድርጅቱ መመራት እንዳለበት መግባባት ላይ ደርሰናል፡፡” ያለው ደህዴን ቀጥሎም “ስለሆነም እየተነሱ ያሉ አዳዲስ የክልል ጥያቄዎች የክልሉን መሪ ድርጅት ቀጣይነት፤ አገራዊ ነባራዊ ሁኔታ እና የሁሉንም ህዝብ ጥቅም ማእከል ተደርጎ መታየት እንዳለበት ማእከላዊ ኮሚቴው አፅንኦት ሰጥቶ መክሮበታል፡፡ ድርጅቱንም ከየትኛውም ጥቃት መከላከል የሚችል አመራርና መዋቅር በቀጣይነት መገንባት እንደሚገባንም አይተናል፡፡ የተጀመረውን የለውጥ ፍላጎት መምራት የሚችሉ ምሁራን፣ ወጣቶችን እና ሴቶችን ማእከል ያደረገ የምልመላና የግንባታ ስራ አጠናክረን መቀጠል እንዳለብን ወስደናል፡፡” ብሏል::
በፌዴራሊዝሙ ዙሪያም መግለጫው እንዲህ ብሏል: “ብዝሃነትን ያለ አድልዎ ማስተናገድ የሚችል እንዲሁም ኢትዮጵያዊ አንድነታችንን ማጠናከር የሚችል የፌደራሊዝም ስርዓት ዕውን እንዲሆን መላው የሀገራችን ህዝቦች ከዳር እዳር በጋራ የታገሉለት ዓላማ መሆኑን ደኢህዴን በፅኑ ያምናል፡፡ ክልላችን የተለያዩ ብሄር ብሔረሰቦች እና ህዝቦችን ያቀፈ እንደመሆኑ በፌደራሊዝም ስርዓት ይበልጥ ተሳታፊ እና ተጠቃሚ ናቸው፡፡ በዚህም ህዝቦችን በፍትሃዊነት መንገድ ማስተናገድ የሚችል የፌደራሊዝም ስርዓት እያጠናከርን መሄድ ለክልላችን ህዝቦች የህልውና ጉዳይ ነው፡፡ በመሆኑም ህብረብሄራዊነትን ለመናድ የሚነሳው የትኛውም ኃይል የብሄር ብሄረሰቦችን እና የሀገሪቱን ህልውና አደጋ ላይ የሚጥል በመሆኑ ድርጅታችን ደኢህዴን ስርዓቱን ለመጠበቅና ለማበልፀግ ግንባር ቀደም ሆኖ ይታገላል፡፡”
ደኢህዴን አክሎም “የፌዴራል ስርዓቱ ለክልላችን ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች የህልውና ጉዳይ እንደሆነ ድርጅታችን ያምናል፡፡ በመሆኑም ብዝሃነትን በመምራት ልምድ ያለው ድርጅታችን የክልሉን ህዝቦች አንድነት ማጠናከር ለኢትዮጵያዊ አንድነታችን ያለው ፋይዳ ትልቅ መሆኑን ይገነዘባል፡፡ ስለሆነም ህብረብሄራዊነትን የሚያስተናግደው የፌደራል ስርዓት አጠናክሮ ማስቀጠል የክልሉ መሪ ድርጅት የሁል ጊዜ አጀንዳ ሆኖ መቀጠል እንዳለበት ተሰምሮበታል፡፡” ብሏል በመግለጫው::