ጠቅላይ ሚኒስት ዶክተር ዐብይ አህመድ የኢህአዴግ አባልና አጋር ድርጅቶች ከጥቂት ወራት በኋላ አንድ ሀገራዊ ፓርቲ እንደሚመሠርቱ ይፋ አደረጉ::
https://www.youtube.com/watch?v=ZdkEBlHGPDA&t=1s
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ ከ3 ሺህ በላይ ከሐረሪ፣ ጋምቤላ፣ ቤኔሻንጉል ጉሙዝ፣ ከአፋርና ከሶማሌ ክልል ከተውጣጡ የማኅበረሰብ ተወካዮች፣ የሃይማኖት መሪዎችና የሀገር ሽማግሌዎች ጋር በጽሕፈት ቤታቸው በሀገራዊ ለውጡ መሠረታውያንና አካሄድ ዙሪያ ምክክር ሲያደርጉ ከዋሉ በኋላ እንዳስታወቀው ‹‹ከጥቂት ወራት በኋላ የአፋር፣ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ የሶማሌ፣ የኦሮሞ፣ የአማራ … ፓርቲ እያልን አንሄድም። እንደ ኢህአዴግ ከጫፍ ጫፍ ያሉ ሁሉም ኢትዮጵያውያን በነፃነት የሚሳተፉበት አንድ ሀገራዊ ፓርቲ እንመሠርታለን፡፡›› ተናግረዋል::
በቅርቡ የጥናቱ ውጤት ተጠናቅቆ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶችና አጋር ድርጅቶች መክረው የጋራ ካደረጉት በኋላ አንድ ሀገራዊ ፓርቲ የሚመሠርቱ መሆናቸውን የገለጹት ዶ/ር አብይ ኢህአዴግ በሐዋሳው ጉባዔ ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት አጋር ድርጅቶችን ወደ ግንባሩ ለማስገባት ጥናት እንዲካሄድ መወሰኑን አስረድተዋል::
“በሀገሪቱ የመጣው ለውጥ በመላ ኢትዮጵያዊ ጥረትና መስዋዕትነት መሆኑ ተረድተን ካላከበርነው ልክ በፍጥነት እጃችን እንደገባው በፍጥነት ከእጃችን ሊወጣ ይችላል:: ስለዚህም ያገኘናቸውን ድሎችና ውጤቶች በትክክል እያከበርን የቀረውን ለመሙላት መጓዝ ያስፈልጋል” ያሉት ዶ/ር አብይ “የመንግሥትን የለውጥ እንቅስቃሴ መደገፍ እንዲችሉ የተቋማትን አቅም መገንባት አስፈላጊ ነው:: ከዚህም በተጨማሪ የዴሞክራሲ ሥርዓቱን ለማዳበር የሕዝቦች ፈጣንና ወትሮ ዝግጁነት ያለው ተሳትፎ አስፈላጊ ነው:: የምንፈልጋትን ኢትዮጵያ ለማየት የሁላችንንም ተሳትፎ ይፈልጋል” ሲሉም ተናግረዋል።
“አንድ ኢትዮጵያዊ ፓርቲ ሁላችንም ያለንበት በመፍጠር ሁሉም ኢትዮጵያ እኩል የሚነጋገርበት እኩል የሚወስንበት ድምጹ የሚሰማበት ከየትኛውም ጫፍ ብቃት ያለው ሰው በየትኛውም ኃላፊነት ክለከላ የማይደረግበት ስርዓት ለመፍጠር ለውጡ በፍጥነት እየተጓዘ ይገኛል” ያሉት ዶ/ር አብይ ከአጋር ድርጅቶችና የማኅበረሰብ አባላት ለቀረቡላቸው የተለያዩ ጥያቄዎችም ምላሽ ሲሰጡም “ችግሮች የሌሎች ክልል ናቸው ከማለት ይልቅ ኃላፊነትን በመውሰድ የትብብርና መፍትሔ ፈላጊ ባሕልን ማስፈንና በየክልሉ የነዋሪዎችን ቅሬታ መስማት የመሪዎች ተግባር መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል:: የህግ የበላይነትን በተመለከተም የሕግ የበላይነት የሚሰፍነው ሕዝቦች ለሰላም ዋጋ ሲሰጡና ሲንከባከቡት እንጂ በጠመንጃ እንደማይመጣ መረዳት መገንዘብ ያስፈልጋል:: የመንግሥት ምጣኔ ሀብታዊ የለውጥ እንቅስቃሴ ሥራ አጥነትን ለመቅረፍ፣ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማሳደግ ዘርፍ በቅድሚያ የሚከወን ይሆናል” ብለዋል::