ትላንት ህዳር 12 ቀን 2011 ከደቡብ ህዝቦች ምክር ቤት ጽ/ቤት የወጣው ደብዳቤ ለአዲሲቷ የምርጫ ኮሚሽን ሰብሳቢ የመጀመሪያ ስራ እንደሚሆን ለመረዳት ችለናል፡፡
ደብዳቤው በርዕሱ ‹‹ህዝበ ውሳኔ እንዲከናወን ስለመጠየቅ›› ይልና የተላከው ለምርጫ ቦርድ እንደሆነ ያሳያል፡፡ ደብዳቤው ሲዘረዝር ‹‹በክልላችን ካሉት 56 ብሄር ብሄረሰቦች አንዱ የሆው የሲዳማ ብሄር ራሱን ችሎ ክልል ሆኖ የመደራጀት ጥያቄ በቁጥር ም/ቤ/02/38/0034 በቀን 12/11/2010 አ.ም. በተፃፈ ደብዳቤ የዞኑ ምክር ቤት አባላት በኢፌዲሪ ህገ መንግስት አንቀፅ 47/2 እና 3ሀ እንዲሁም በክልሉ ህገ መንግስት አንቀፅ 39/5 እና 9ሀ መሰረት በሙሉ ድምፅ የወሰኑትን ውሳኔ በቀን 13/11/2010 አ.ም. ለምክር ቤታችን አባሪ አድርገው በማቅረብ ጠይቀዋል›› ይላል፡፡ ደብዳቤው ጨምሮም ይህ ጥያቄ ጥቅምት 23 ቀን 2011 በተደረገው የምክር ቤቱ መደበኛ ጉባኤ ተፈፃሚ እንዲሆን አቅጣጫ መቀመጡን አውስቶ ምርጫ ቦርድ በአዋጅ ቁጥር 532/1999 አንቀፅ 32/2 በተሰጠው ስልጣን መሰረት ህዝበ ውሳኔ እንዲያከናውን ጠይቋል፡፡ በክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ሄለን ደበበ ወ/ጊዮርጊስ ፊርማ ትላንት የወጣው ደብዳቤ በግልባጭ ለጠ/ሚ/ር ዶክተር አብይ አህመድ፣ ለፓርላማው አፈ ጉባኤና ምክትል አፈ ጉባኤ፣ ለክልሉ መስተዳድር ምክር ቤት፣ እንዲሁም ለሲዳማ ዞን ምክር ቤት እንዲደርስ መደረጉን ለማወቅ ችለናል፡፡ በመሆኑም የወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ቢሮ የመጀመሪያ ስራው ይህንን የሲዳማ ክልልነት ጥያቄ በህዝበ ውሳኔ ማስፈፀም ይሆናል፡፡
https://www.youtube.com/watch?v=W20KYng_SXM