በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን አይሁዶች በትላንትናው እለት በአዲስ አበባ የእስራኤልን ውሳኔ ለመቃወም ስብሰባ አድርገዋል፡፡
የእስራኤል መንግስት ኢትዮጵያዊያን አይሁዶችን ወደእስራኤል መውሰዱን ማቆሙን ማስታወቁ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ተቆራርጠው እንዲቀሩ የሚያደርግ ውሳኔ መሆኑን ነው በተቃውሟቸው የገለፁት፡፡
8 ሺህ በኢትዮጵያ የሚኖሩ አይሁዶችን እንወክላለን ያሉት እነዚህ ተቃዋሚዎች የእስራኤል መንግስት ውሳኔውን ወደገዢው ሊክዊድ ፓርቲ ወስዶ ከማስወሰኑ በፊት ቆም ብሎ እንዲያስብበት ጠይቀዋል፡፡
በአዲስ አበባና በጎንደር የሚገኙ አይሁዳዊያን ፈላሾች አስተባባሪ የሆኑት አቶ ንጉሴ ዘመነ ለአሶሺየትድ ፕሬስ ሲናገሩ ‹‹የእስራኤል መንግስት እዚህ የቀረነውን አይሁዶች መውሰድ ያቆመው እንደገለፀው በፋይናንስ እጥረ
ት አይመስለኝም፡፡ ይልቁኑ የፖለቲካ ውሳኔ ወይንም ዘረኝነት ነው ብዬ አስባለሁ›› ብለዋል፡፡ የእስራኤል መንግስት ኦክቶበት 7 ቀን 2015 እ.ኤ.አ. ለአንድ ሺ ኢትዮጵያዊያን ብቻ የመግቢያ ፈቃድ ሰጥቶ ሌሎቹን እንደማይቀበል መወሰኑ ቤተሰቦችን ከማቆራረጡም በላይ በረሃብ እንዲገረፉ እንዳደረጋቸው አስተባባሪው አስረድተዋል፡፡
እያዩ አቡሀይ የተባሉት ሌላው አስተባባሪ በበኩላቸው ከ2015ቱ የመንግስት ውሳኔ ወዲህ 50 ኢትዮጵያዊያን አይሁዶች እንደሞቱ ተናግረው ‹‹ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ናቲናይሁ እኛ ሁላችንም እዚህ በማለቃችን በፊት እንዲያድኑን እንማፀናለን›› ብለዋል፡፡ ባለፈው አመትም ፈላሻዎቹ ተመሳሳይ ተቃውሞ በአዲስ አበባ ማሰማታቸው የሚታወቅ ሲሆን ይህን ተከትሎ የእስራኤል ባለስልጣናት በተደጋጋሚ ወደኢትዮጵያ የመጡ ቢሆንም ምንም የተፈጠረ ነገር እንደሌለ የተቃውሞው አስተባባሪዎች ያስረዳሉ፡፡
https://www.youtube.com/watch?v=6Vu03MkJX_0