ይድረስ ለአርበኛው ጸሐፊ ዕዝራ አስቻለው ዘለቀ – ግርማ በላይ

በተከታታይ የጻፍካቸውን ሁለት ግሩም መጣጥፎች በፍቅር አነበብኳቸው፡፡ በነዚህ ጽሑፎች እንደተረዳሁት ጥሩ አንባቢ ነህ፤ የብዕር አጣጣልህም ውብ ነው፡፡ ሀገርህንም እንደምትወድ በጽሑፍህ ብቻ ሣይሆን በረሃ መውረድህ ራሱም በቂ ምሥክር ነው፡፡ ማቄን ጨርቄን ሳትል ለአንዲት እናትህ ኢትዮጵያ ስትል እያሳለፍከው ያለኸውን መከራና ስቃይ መረዳት እችላለሁና የእምዬ አምላክ ይከተልህ፡፡ አንተን ብቻም ሣይሆን ለተመሳሳይ በጎ ዓላማ የተሰለፋችሁትን ጓዶችህንም ሁሉ ፈጣሪ ይጠብቃችሁ፤ ያሰባችሁትንም ያሳካላችሁ፡፡ በረከቱ የሁላችንም ነውና፡፡ እኛም በጸሎት ከጎናችሁ አለን፡፡

ይሁንና በግልጽ መነጋገር ለሁሉም ወገን የሚበጅ እንደመሆኑ ከጽሑፍህ ለመረዳት የሞከርኩትን በግልጽ የተነገሩና ያልተነገሩ አንዳንድ ነጥቦችን ማንሳት ወደድኩ፡፡ ከብረት ዝገት ከሰው ስህተት እንደመገኘቱ ተሳስቼ የተረዳሁብህ ነገር ቢኖር አስቀድሜ ይቅርታ መጠየቅ እፈልጋለሁ፡፡ የምናገረው በግልጽ ነው፤ ይሉኝታ መጥፎ ነው፡፡ በትንሽ በትልቁ መኮራረፍና የሸሚዝን እጄታ መሰብሰብ ባህል በሆነባት ሀገራችን ውስጥ ሃሳብን እንደወረደ ማቅረብ ቁም ስቅል እንደሚያስከትል ብረዳም ምርጫ የለኝም፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ እኔ አንተን ብሆን ኖሮ የሚከተለውን ቃል በምንም መንገድ አልናገርም(አልጽፍም) ነበር፤ ደግመህ አንብበውና አርመኝ፡፡

… በኦሮሞውም ላይ ሆነ በሌላው ወገናችን ላይ በአማራ ስም ለደረሱ በደሎች በይፋ ይቅርታ የሚጠይቅና የሞራል ካሳን ከፍሎ ሰላምና እርቅ የሚያወርድ ሕዝብ የመረጠው መንግስታዊ ኣካል በሀገሪቱ ታሪክ ውስጥ በሌለበት ሁኔታ ውስጥ ይህንን ሃላፊነት ስለምን እኛው በኛው ስለኛው አናደርገውም? ብሄራዊ ዕርቅና መግባባትስ ላይ ለመድረስ ምን አዳገተን? ሌላስ ከኛ የቀረበና ሊያስታርቀን የሚችል ምን ሃይል ይኖራል ስል [ራሴን]ጠየቅኩ።…

ይህ የሚያሳየን ግንቦት ሰባት በርግጥም ፀረ አማራ መሆኑንና አማራ የሠራው ይቅርታ የሚያስጠይቅ ታሪካዊ በደል መኖሩን እንደሚያምን ነው – ይህንንም ነጥብ ከተራ አስተያየት ባለፈ በቁጭትና በፀፀት ነው የገለጽከው፡፡ በተጨማሪም ዴሞክራሲያዊ መንግሥት ባይኖረንም አሁንም ቢሆን አማሮች ተነሳሽነቱን ወስደው ይቅርታ መጠየቅ እንደሚገባቸው እየመከርክ ነው፡፡ ስለሆነም ግንቦት ሰባት አሸንፎ ቤተ መንግሥት ቢቆጣጠር አማራ ለሁለተኛ ጊዜ ይቅርታ መጠየቅ ሊኖርበት ነው፡፡ የመጀመሪያውን ይቅርታ በነፕሮፌሰር እንድርያስና ማንትስ አስገልጥ (ስሙን ረሳሁት) በሚባሉ የወያኔና የሻዕቢያ አጫፋሪዎች የዛሬ 26 ዓመታት ገደማ አሥመራ ላይ ተደርጓል – ሻዕቢያና ወያኔ ይቺን “ይቅርታ” የሚሏትን ቃል እንዴት እንደሚወዷት መቼም ለማንም ግልጽ ነው(ትርጉሟን ግን በርግጠኝነት አያውቋትም)፡፡ እናም መንግሥት በተለወጠ ቁጥር ይህ መከረኛ የአማራ ሕዝብ ይቅርታ ሲጠይቅ መኖሩ ነው – እንደ አንተ እንደዕዝራና ምናልባትም እንደግንቦት ሰባት፡፡ አሁን ላይ ሆኜ የወደፊቱ ሲታየኝ – ግንቦት ሰባት ህጋዊ መንግሥት ሲሆን የዱሮው “የአማራው ገዢ መደብ”  የበደለውን ሁሉ ይቅርታ ይጠይቃል፤ ካሣም ይከፍላል፡፡ በቃ፡፡ “የምታሸንፈውን ምታ ቢሉት ወደ ሚስቱ ሮጠ” ይሏል ይሄኔ ነው፡፡ የሆኖ ሆኖ ይህ ነገር አንዳንድ የዋሃንን “ግንቦት ሰባት የመረረ ትግል እያካሄደ ያለው ለካንስ ለዚህ ነው” ወደሚል ጫፍ ቢወስዳቸው አንፈርድባቸውም፡፡ ግንቦቶች ከወያኔና ሻዕቢያ ግዙፍ ወንጀሎች ይልቅ ባለፉ ጥቃቅን የታሪክ ስህተቶች ላይ ይበልጥ የሚብከነከኑ ይመስላል፡፡ በጤናና ለጤና ከሆነ ደግ ነው፡፡

እኛ የምንለው ኢትዮጵያን የገዙት ወይም ያስተዳደሩት – የአሁኑን የእፉኝት ዘመን ሳይጨምር – የሁሉም ዘውጎቿ ውህድ የሆኑ ልጆቿ እንጂ አንዱ ብቻ ተነጥሎ በስግብግበነትና በዘረኝነት ልክፍት ታውሮ አልነበረም ነው፡፡ ስለዚህም መበዳደል እንኳን ቢኖር (ጎሣና ነገድን ባካተተ መልክም ጭምር) አንዱ ሁሉንም በሚጨፈልቅ ሁኔታ ሣይሆን ሁሉም ወገን በቡድን ወይ በተናጠል ሁሉንም ወገን በድሏል ወይም ጨቁኗል ብለን ነው የምናምነው፡፡ እዚህ ላይ አማርኛ እየተናገረ ሀገር የገዛው ሁሉ አማራ ነው የሚል እምነት ካለ ክርክሩን በጊዜ ማቆም ነው የሚሻለው፡፡ እንጂ ጉራጌው አፄ ኃይለ ሥላሤና ኦሮሞው አፄ ገላውዴዎስ በጨቆኑ አጎቴ ስንሻው ተገኝ ዐፅሙ እንኳን እንዳያርፍ በአኮርባጅ ሊገረፍ አይገባም፡፡ ይህን ዓይነቱን አካሄድም ልዩ ተልእኮ እስከሌለውና በአስተዳዳሪዎቹ ለመወደድ እስካልፈለገ ድረስ ግንቦት ሰባት ባያቀነቅነው ይመረጣል፡፡ በሥልት ደረጃ ለተወሰነ ጊዜ ሊጠቀምበት ፈልጎ አማራንና የኢትዮጵያን ታሪክ ማንኳሰሱን የሚገፋበት ከሆነ ግን የማይወጣው አዘቅት ውስጥ ሊገባ እንደሚችል መረዳት ይኖርበታል፡፡ ሁኔታዎች ተለዋዋጭ ናቸው፡፡ በተለይ በዚህ ዘመን፡፡ ይሁንና ወያኔና ሻዕቢያ አማራ ላይ ያላቸውን ሥር የሰደደ ጥላቻ በተመለከተ ዓለም ብታልፍም ለውጥ አይኖርም፡፡ ከሌላ አቅጣጫ ግና ለውጥ መከሰቱ የሚጠበቅ ነው፡፡ ያኔ አንድን ከሦስትነት፣ ሦስትነትን ከአንድነት ለመለየት ማበጠር ያስፈልግ ከሆነ ችግር መፈጠሩ አይቀርም፡፡ ስለሆነም በተለይ መዝገብ ላይ የሚሰፍሩ አንዳንድ አፍ እላፊዎች ላይ ጠንቀቅ ማለቱ አይከፋም፡፡ ሁሉም ያልፋል፡፡ ሲያልፍ ግን ጠባሳ እንዳይተው – ቢተው ደግሞ የጠለቀ ጠባሳ እንዳይሆንና አብሮነታችን ላይ ጥቁር ጥላ እንዳያጠላ  መጣር ብልኅነት ነው፡፡

እኔ ዕዝራን ብሆን የሚከተለውን በፍጹም አልልም ነበር፡-

… የብሄር ፖለቲካው ተጧጡፏል። እጅግ የሚገርመው ከነኚህ የብሄር ጦረኞች ውስጥ የተወሰኑት አዛውንቶች መሆናቸው ናቸው። እርግጥ አንዳንድ በተለይ ኦሮሞንና አማራን እንወክላለን የሚሉ “መሃላ ገልባጭ፣ ልሳነ ብልጥ አሲዳም ብላቴኖች” እዚህም እዚያም ባይጠፉም። አዛዉንቶቹ ግን በኔ እይታ የአቦይ ስብሃት የመንፈስና የስጋ መንትያዎች ይመስሉኛል።

አዛውንት ሀገር የለውም ወይም ስለሀገሩ አያገባውም ያለው ማን ነው? ይህ ዓይነቱ ወዝ የሌለው ቀልድ ቢቀር ጥሩ ነው – ዓላማው እርግጥ ነው ሰውን ተስፋ በማስቆረጥ ወደ ዳር ለመገፍተር ነው፤ ግን ነውር ነው፡፡ ለኔ  እንደሚገባኝ ለምሣሌ ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያምን “ይህችን ሀገር  ከቋጥኝ ጋር እያላጋን እንዴት እንደምንመራት ዝም ብለህ ተመልከት እንጂ ትንፍሽ አትበል!” ብሎ እንደመገሰጽ ነው፤ ከዚህ በላይ ነውር – “በሀገርህ ጉዳይ አያገባህም!” ብሎ የእኩል ሀገርን ለራስ የፖለቲካ ዓላማና ጥቅም ሲሉ ከመንጠቅ የበለጠ በደል ደግሞ የለም፡፡ ሀገር ሰጪና ነሽ ግንቦት ሰባት ይቅርና ወያኔም ሆነ ሻዕቢያ አይደሉም፤ ሀገራችንን የተነጠቅነው በስንፍናችን ነው፤ በስንፍናችሁ ቀጥሉ ብሎ ደግሞ ማንም ሊመክረን አይገባም፤ አይችልምም፡፡ የአቦይ ስብሃት የመንፈስና የሥጋ መንትያዎችን በሚመለከት እነዚህ ወገኖች እነማን እንደሆኑ ለማወቅ ተመካክሮ መግባባት  ሳያስፈልግ የሚቀር አይመስለኝም – በከንቱ መፈራረጅ ዘመኑ ያወረደብን መቅሰፍት ሆነና ክፉኛ አስቸገረን፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ጥሩ ጸሐፊ የቃላት ምርጫውንና ምኞቱን ቢገራ ጥሩ ነው እላለሁ፡፡ ይበልጥ የሚያራርቁ አገላለጾችን ከመጠቀም ይልቅ የሚያቀራርቡ ቢሆኑ ይመረጣል፡፡ አለበለዚያ ፈግጠው ፈግጪው ይሆንና ትርፉ ጠላትን ማብዛት ነው፡፡ ግንቦት ሰባት ደግሞ መጣር ያለበት ሰውን በፍቅር አማልሎ በመሳብ ደጋፊን ማብዛት እንጂ እንደዚህ ዓይነት ከራር አቀራረብ ደግ አይደለም፡፡ “የፈሺታ ተቆጪታ” ያስብላል፡፡ ባሉበት ከመርገጥ በአስተሳሰብና በአመለካከት የተሻለ ሆኖ መገኘት ተመራጭ ያደርጋል፡፡ የየጁ ደብተራ በቅኔው ላይ ቀረርቶውን የጨመረበት ቢጨንቀው ነው፡፡ ከዚህ ደብተራ የማይማር ካለ ዝንጉ ነው፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ስድብና ዘለፋ የምናበዛ ሰዎች ሞልተናል፡፡ ይህም የአሸናፊነት ሳይሆን የተሸናፊነት ምልክት ነው፡፡ ዘለፋ፣ ስድብ፣ ዛቻና ፉከራ የሚቀናው ሰው ሊያደርግ በሚያስበውና ሊያደርግ በሚችለው መካከል ያለው ክፍተት የሚፈጥርበት የአቅም ውስንነት የሚያንገላታው አሳዛኝ ፍጡር ነው፡፡ አንድ ሰው የአቅም ውስንነት ሲገጥመው ያለው አማራጭ ከሁለት አይበልጥም – አንድም ሽንፈቱን በፀጋ ተቀብሎ መቀመጥ፡፡ አለበለዚያም እንደወያኔ ከፀሐይ በታች ያሉ የክፋት መድብሎችን በመጠቀም ወደሚፈለገው የድል ጫፍ መዝለቅና ያንንም ድል ላለማስነጠቅ ሌት ከቀን ዘብ መቆም፡፡ ከዚህ አኳያ ወያኔዎች “ወንድ” ናቸው – ሊያውም የወንዶች ቁንጮ! ዓላማቸው ምንም ይሁን ምን – እኛ ምንም እንበላቸው ምን – እነሱ ግን በጥንካሬያቸው ገፍተው ይሄውና 43 ዓመታትን ደፈኑ – የገማ ዓላማም ዓላማ ሆኖ በቆራጥነታቸው ግን እስካሁን ከወሬ በስተቀር ከአራት ኪሎ አንድም ስንዝር ሊያነቃንቃቸው የቻለ ምድራዊ ኃይል አልተገኘም፡፡  እኛም ጎራ ለይተን ስንጎሻመጥና አንዳችን ለአንዳችን ሞትንና ኪሣራን ስንመኝ የጀምበርን  መጥለቅ የሚያረዳው የመጨረሻው ሐሙስ ላይ ደረስን፡፡ አዎ፣ አማራን ባልዋለበት ለማዋል የሚደረገው የጠላቶቻችንና የተላላኪዎቻቸው ጥረትም ከዚህ በእውነተኛ የጦር ቀጣና ውስጥ በconventional እና non-conventional መሣሪያ(ዎች) ተዋግቶ የማሸነፍና ያለማሸነፍ ታሪክ ጋር የሚገናኝ ነው፤ አማራን እንደ ሕወሓት ዝቀጥና በየትም ፍጪው ሥልጣኑን ብቻ ተቆጣጠር ብትለው አይሆንለትም – ሥነ ልቦናው ትክክለኛውን ላዕላዊ ሥፍራ የተቆናጠጠ በመሆኑ ዛሬ ለሀብትም ሆነ ለሥልጣን ሲል በበታችነት ስሜት የሚሰቃዩት ወያኔዎች የሚሠሩትን ግፍ ይጸየፈዋል፡፡ ጊዜ ግን የማያዳላ ዳኛ ነውና በቅርብ ምናልባትም በጣም በቅርብ አንድ ነገር ማየታችን አይቀርም፡፡  ግን ግን ይብላኝ  ኅሊናውን ስቶ እውነትን ለሚደፈጥጥ ገልቱ ዜጋ(ለምንም ዓይነት ጥቅምና ፍላጎት)፡፡ እናም እባካችሁን ከአማራ ራስ ውረዱ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  አቶ አላሙዲንን እንደ በጎ አድራጊ፣ ቸር እና ደግ ሰው የምትቆጥሩ ሰዎች በጣም አስቂኝ ናችሁ

ዕዝራን ብሆን እንዲህ አልልም ነበር – “ ከፍቅር ይልቅ ለጥላቻ፣ ከአንድነት ይልቅ ለልዩነት፣ከትዕግስት ይልቅ ለስም ማጥፋት፣  ከሕይወት ይልቅ ለመቃብር የቀረቡ። ከዚህ አለም ይልቅ የቀጣዩ አለም አፉን ከፍቶ የሚጠብቃቸው ።”

በባህላዊ አነጋገራችን እንድጠቀም ቢፈቀድልኝ ተክሌ የሻው ቢሞት ግንቦት ሰባት ምሥጥ ሆኖ አይበላውም፡፡ ለግንቦት ሰባት ከኢሣይያስ አፈወርቂ ይልቅ ተክሌ የሻው በጣም ቅርብ ነው፡፡ ደግሞም ምን ቢጠሉት ለሰው ሞትን መመኘት ያስነውራል፡፡ በዕድሜ አንጋፋ መሆንም የሚያኮራ እንጂ ለሣቅ ለሥላቅ የሚዳርግ አይደለም፤ “ጌታ ሆይ፣ እንደሳቸው የዕድሜ ባለፀጋ እንድሆን ዕድሉን ስጠኝ” በሚል በመንፈስ ይቀኑበታል እንጂ በዚህን ያህል ደረጃ ወርደው ግፍ የሚናገሩበት አይደለም – የዕድሜ ባለጠግነት፡፡ እኔ ሃቁን ተናገርኩ እንጂ የተክሌም ሆነ የሌላ የማንም አቦካቶ አይደለሁም፡፡  ነግ በኔን ማሰብ ጥሩ ነው፡፡ የዛሬ ልጆች ባጭር የሚቀጩት – አንዱ ምክንያት የሚመስለኝ – ታላላቆቻቸውን ስለማያከብሩና ከዚያም ባለፈ እንደዕዝራ በታላላቆቻቸው የዕድሜ መግፋት ስለሚያላግጡ ነው፡፡ተክሌ የሻውን ነፃ ለማውጣት ከተክሌ የሻው ታሪካዊ ጠላት ጉያ ሄዶ የተወተፈ ወገን በዘዴና በጥበብ ተክሌን ከሚወርድበት ጣምራ ውርጅብኝ ለማዳን ይጥራል እንጂ በቁስሉ ላይ ጨው ሊነሰንስበት ባልተገባ ነበር፡፡ አዝኛለሁ፡፡

በግልጽ እንነጋገር፡፡

ኢሣይያስ አፈወርቂ አማራን አይወድም ብቻ ሣይሆን ልክ እንደወያኔ ወንድሞቹ አማራ ካልጠፋ እንቅልፍ የማይወስደው ሰው ነው፤ ይህን አቋሙን ደግሞ እንኳን አማራን በመሳደብና በመወረፍ ኢትዮጵያን ከነሕዝቧ መቀመቅ አውርደው ቢያሳዩትም ለአፍታም አይተወውም – ሲፈጠር ጀምሮ የተጣባው አጋንንታዊ መንፈስ ነው፡፡ ኢሣይያስ ግንቦት ሰባትን ከአማራ ለማጽዳት የሚፈልግበት ዋነኛ ምክንያትም ኢትዮጵያ በአዲስ መልክ እንኳን ብትፈጠር አማራ ወደ ሥልጣንም ሆነ ወደሀብት የማይቀርብ መሆኑን እርግጠኛ ለመሆን ነው፤ ለዚህም ነው በዚያ በኩል የሚደረግ እንቅስቃሴ ሁሉ ታጥቦ ጭቃ ነው የሚባለው፤  እውነትም ነው፡፡ ግንቦት ሰባት በ10 ዓመትና በዚህ ሁሉ የዲያስፖራ ድጋፍ አንዲት መንደር ነፃ ያላወጣው እንደ አንዳርጋቸው ጽጌ አባባል ራሱም ነፃ ስላልወጣ ለመሆኑ ከፈጠጠውና ድርጅቱን ራሱን ከሚያስደነግጠው መሬት ላይ የሚታይ እውነታ የበለጠ ማስረጃ የለም፡፡ ይህንንም ሆነ ሌሎች ኢትዮጵያዊ ጉዳዮችን “ከግንቦት ሰባት በበለጠ እኔ አውቃለሁ” – እንደኦሮሞነቴ ሞራ አነባለሁ፤ እንደ አማራነቴ መጣፍ እገልጣለሁ፤ እንደዚች ዓለም ዜግነቴ ደግሞ በደንብ የምጠቀምበት ስድስተኛው የስሜት ሕዋስ አለኝ፡፡ ስለዚህ በዚህ ጉዳይ ከቀዳሚ “ኤክሰፐርቶች” አንዱ ነኝ ብል ስህተቴ ለሸንጎ ፍርድ አያቀርበኝም፡፡ እናም ንገረን ካላችሁ ልናገር – በእስራኤላውያንና በፍልስጥኤማውያን መካከል – በይሁዲዎችና በዐረቦች መካከል –  ያለ ጥል በትግሬና በአማራ መካከል እንዲፈጠር ተሞክሮ ፍሬው እያሸተና እየጎመራ ይገኛል፡፡ ጽዮናዊነት መልኩን ለውጦና ጭካኔውን አክርሮ በሕወሓት አማካይነት ወደ አፍሪካ ቀንድ ከገባ ቆይቷል፤ ችግሩ ደግሞ “በደምባራ ፈረስ ቃጭል ተጨምሮ” እንዲሉ በማይማን ወያኔዎች ዘንድ የገባ ትግሬያዊ ጽዮናዊነት እንደዋናዎቹ እስራኤላውያን በጥበብና በመላ ሳይሆን በጀብድና በዕብሪት በመከናወኑ የሚያደርሰው ጥፋት ሊደበቅ የማይችልና መረን የለቀቀ መሆኑ ነው፡፡ በሕዝብና በሕዝቦች መካከል ቅራኔን በመፍጠር ረገድ የሚታወቁትና ሰማንያ መቶኛውን የዓለም ሕዝብ በመጨረስ የራሳቸውን አዲስ የዓለም መንግሥት (the New World Order)ለመመሥረት በመጣደፍ ላይ የሚገኙት የታችኛው ዓለም አገልጋይ ፈረንጆች ይህን ትግሬያዊ ጽዮናዊነት ጸንሰው የወለዱትና ተ(ን)ከባክበው ያሳደጉት ቢሆኑም ሃሳቡን ተቀብለው እውን ያደረጉት ግን የባንዳዎቹ ልጆች እነስብሃት ነጋና መለስ ዜናዊ ናቸው፡፡ የአደባባይ መሥጢርን መናገር ነውር የለበትም፡፡ ከዚህ አኳያ አማራንና ኦርቶዶክስን ካላጠፋ ዕረፍት እንደማያገኝ በማኒፌስቶው ጭምር አስቀምጦ የአማራን ዘር እያጠፋ የሚገኝ ወያኔ በዋናው የሥልጣን ወንበር ላይ ተቀምጦ ባለበት ሁኔታ ከወያኔ መልማይና አሰልጣኝ የሻዕቢያ ዕቅፍ ውስጥ ሆኖ ስለአማራ ነፃነት ማውራት በትንሹ ዶሮ ማታ ነው፡፡ ስለነፃነት ማውራቱ ሊቀጥል ይችላል፤ ችግርም ክፋትም የለውም፡፡ ነገር ግን አማራን ከመሳደብና ከማንቋሸሽ መቆጠብ ያስፈልጋል፡፡ አማራ ያሉት ጠላቶች ከበቂ በላይ በመሆናቸው የጦር ግምባሮችን ባታበዙበት ይሻላል፡፡ አማራው የዝምብ ልጃገረድን ይቅርና ከመቶ ዓመት በኋላ ስለምትፈጠር ጠንጋራ ዝምብም ያውቃል፡፡ አማራ ችግሩ መለያየቱ እንጂ ዕውቀትና ጥበብ ወይም የአተኳኮስ ችሎታ ማጣት አይደለም፤ የዕልቂት ዒላማ ውስጥ ያስገቡት ይልቁናም እነዚህ ነገሮች ናቸው፡፡ “የሚያልፍን ቁዝምዝም ጎንበስ ብለህ እለፍ” ብሎ የተረተው አማራ መሆኑን አንዘንጋ፡፡ አማራጭ አጥቶ ራሱን ከጨርሶ ዕልቂት ለመከላከል  ሲል ብቻ የገባበትን ጊዜያዊ ጠባብ ዋሻ በማየት ይህን የነፍስ አድን ጥረቱን እንደወንጀል ቆጥራችሁ የምትቅበዘበዙ ወገኖች ራሳችሁን መርምሩ፡፡ መጽሐፉ (በራሴ ትውስታ) “በአንተ ዐይን ውስጥ የሚገኘውን ዕርፍ እሚያህል ጉድፍ ሳታወጣ በጓደኛህ ዐይን ውስጥ እምትገኘውን ነቁጥ እምታህል ጉድፍ ለማውጣት ለምን ትቸኩላለህ?” ይላልና በዚህ በአማራው የመከላከል የነፍስ አውጪኝ ጥረት ብዙም አትደነቁ፡፡ ይልቁንስ ኢትዮጵያ ስለተደገሰላት መከራ አልቅሱ፤ አሁን ጊዜ እያላችሁ “ዋይ፣ዋይ” በሉላት፡፡ ኢትዮጵያ ጉግማንጉግ መንግሥትና ጉግማንጉግ የሃይማኖት መሪዎች እንደ ዘንዶ ተጠምጥመውባት እንደነሱው ሁሉ ሕዝቡም በተለይም ወጣቱ የሰይጣን ግብረ በላ እንዲሆንና ከሞራል ዕሤቶችም ከባህልም ከሰብኣዊነትም ከሃይማኖትም …ወጥቶ የለዬለት እንስሳና ዐውሬ እንዲሆን የሚደረገው ጥረት ሁሉ እየተሳካ ነው፡፡ በዚህና በሌሎች ተያያዥ ምክንያቶች የተነሣ ሀገራችን እንደሶዶምና ገሞራ ልትነድ የቀራት ቅጽበት በጣም አጭር ነው፡፡ ፈርዶብኝ ይህንንም አውቃለሁ፡፡ የማላውቀውና አሁን የማልናገረው ምሥጢር ግን ከዕልቂቱ በኋላ ወርቃማ ዘመን ይብትና ኢትዮጵያ ከውጪ ወደውስጥ የሚሰደዱባት እንጂ ከውስጥ ወደ ውጪ የማይሰደዱባት በቁሣዊና መንፈሣዊ ሀብቶች የበለፀገች ሀገር እንደምትሆን የሚጠበቀው የተስፋ ቃል ነው፡፡ ወያኔና ወያኔ-ነክ ፍጡራን ሊበሳጩብኝ ይችላሉ፤ ይቅርታ፡፡…

ተጨማሪ ያንብቡ:  በአርባ ጉጉ እና አካባቢው በአማራው ህዝብ ላይ የተፈጸመውን የዘር ማጥፋት ወንጀል መካድ አይቻልም - ሞረሽ ወገኔ የባህል ማህበር በስዊድን

ለመሆኑ አማሮች ምን አጠፉ? ከ42 ዓመታት በላይ በታወጀባቸው የዘር ማጥፋት ዕልቂት ብዙዎቹ አለቁ፡፡ ወያኔ ከሥራም ከኑሮም ከቀያቸውም አፈናቀላቸው፡፡ የመንግሥት ሥራ ላይ እንዳይቀጠሩ፣ ቢቀጠሩም ትግሬ ወይም ሌላ ታማኝ ሎሌ እስኪተካቸው ድረስ እንዲሆን ተደረገ፡፡ በገዛ ሀገራቸው ባይተዋርና የበይ ተመልካች ሆኑ፡፡ በሌላ አካባቢ ይቅርና በተቀነበበላቸው አዲስ ክልል ውስጥ እንኳን ሀብት ማፍራትና ሥልጣናቸውን በተግባር ማዋል እንዳይችሉ ሆኑ፡፡ አዛዥ ናዛዡ ሙሉ በሙሉ ትግሬ ሆነ፡፡ በድህነት አረንቋ ውስጥ ጥለው አርመጠመጡት፤ በማይምነት መጋረጃ ጀቦኑት፡፡ አማራ እንደዜጋም ባይሆን እንደሰው እንኳን ቁጠሩኝ ብሎ በለመነ የሕወሓት ጀሌዎች ዘቅዝቀው አረዱት፤ ዘር መቋጠሪያው ላይ ከባድ ዕቃ በማንጠልጠል አሰቃዩት፤ አመከኑት፡፡ የስድብ ዓይነት በየፈርጁ ፈለሰፉበት፡፡ በጀግንነቱ ተሣለቁ፡፡ (በአንዳንድ ቅንጡዎች ዘንድ ይህን መናገርም ወንጀል ነው፡፡)ለመናገር የሚሰቀጥጥና አበነፍሳቸው ሰይጣን ራሱ ያላስተማራቸውን ወንጀሎችና ነውሮችን ፈጸሙበት –  በዚህ  ላማዊ የአሸናፊነት ሥነ ልቦና በፈጠረባቸውና በግማሽ ምዕተ ዓመት ረጂም ዘመንም ሊሰክንላቸው ባልቻለ የመቅበዝበዝ ስሜት ተመርተው በተለይ አማራው ላይ የሠሩት ግፍና በደል ሁሉ በወርቅ ቀለም ተመዝግቦላቸዋል፤ ከዚያም ጊዜው ሲደርስ ያወራርዱታል፤ ከዚያም ከዚያን በኋላ ሀገራችን ሰላም ትሆናለች፡፡ አማራ ላይ ያልተፈጸመ ወንጀልና የአድልዖና የማግለል ድርጊት የለም፡፡ ሰሞኑን የማውቀውን አንድ ነገር ልናገር በዚህ አጋጣሚ – አንድ መሥሪያ ቤት ውስጥ አንድ አማራ ለሥራ ዕድገት በወጣ የውስጥ ማስታወቂያ ተፈትኖ በጎላ ልዩነት ተወዳዳሪዎችን ያሸንፋል፡፡ ትግሬው አለቃ – የትም ቦታ አለቆቹ እነሱው ወይም እነሱው በቅርበት የሚቆጣጠሩት ሰው ነው – የዚህን ሰው ብሔር ሲያይ አማራ ነው፡፡ ይሄውና ሌላ ሰው እያፈላለገ ያን ሰው ያሸነፈበትን ቦታ ከለከለው፤ ይህ አንድ ትንሽ ምሣሌ እንጂ አማራ ዲግሪ ይዞ ትግሬው በማይምነት የሚመደብበት ቦታ ላይ አይመደብም፤ ኢትዮጵያ 100 በ100 የወያኔ ጥገት መሆኗን ስንናገር ተቃዋሚያችን ይበዛል እንጂ ብዙ ዝርዝር ማውጣት ይቻላል፡፡ አፓርታይድ በስንት ጣሙ! ፋሽዚም በስንት ጣሙ! ናዚዚም በስንት ጣሙ! በጥቁርና ነጭ መካከል ያለ መናናቅ በስንት ጣሙ! የዲያብሎስ ትምክህት በስንት ጣሙ!

በአሁኑ ወቅት ወያኔዎች በአማራው ላይ እያደረጉት ያሉት ፍዳና መከራ በአቦይ ገብረ ሕይወት የትዝታ ደግነት ሊሸፈን አይችልም፡፡ ትዝታ እውነታን ይጋርዳል፡፡  እንጂ ዱሮ በደጉ (በደርጉም ጭምር) ዘመንማ ትግሬና አማራ መቼ ተጣልተው ያውቁና፡፡ ወያኔ እኮ ነው አዲስ የዐመፃ ዘር ዘርቶ እያፋጃቸው የሚገኘው፡፡ ደግሞስ እንኳንስ አማራ ለትግሬና ኦሮሞ ለከምባታ የካናዳው ጆንና የእንግሊዙ ጆንሰን ልብሳቸውን እያወለቁ፣ ከገበታቸው ምግባቸውን እየቀነሱ የሚልኩልን በዘር በሃይማኖት ተሳስረናቸው ነው እንዴ? ሰው በመሆናችን ብቻ እኮ መረዳዳት አለብን፤ ሰውነት እኮ ከጎሣ በላይ ነው – ኅሊናው ላልታወረ፡፡

ግንቦት ሰባት ጠላቱን ቢያውቅ ለዚህ ሁሉ ችግር ባልተጋለጠ ነበር፡፡ ችግሩ ከትዕቢት ይጀምራል፡፡ አንድ ድርጅትም ይሁን ግለሰብ ሁሉን አውቃለሁ ብሎ በትዕቢትና በዕብሪት ከተወጠረ፣ በዝና ከሰከረና ባለውና በሌለው መታበይ ከጀመረ የማደጊያ ሥሮቹንና ቅርንጫፎቹን ቆራርጦ ጣለ ማለት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ግንድ ይሆናል፡፡ ግንድ ደገሞ አያድግም፡፡ ሊቀ ሣጥናኤል ከዚያ ሁሉ ክብሩና ግርማ ሞገሱ የተለዬውና ወደ ጨለማው ግዛት የወደቀው በትዕቢቱ እንደነበር መርሳት የለብንም፡፡ ስታጣ ብቻ ሳይሆን ስታገኝም ፍራ፡፡  ሲጠሉህ ብቻ ሳይሆን ሲያፈቅሩህም ፍራ፡፡ ስትከሳ ብቻ ሳይሆን ስትወፍርም ጠርጥር፡፡ ፀጥ ሲሉብህና ሲያድሙብህ  ብቻም ሳይሆን ሲያጨበጭቡልህና ሲያጅቡህም ፍራ፡፡ ሲያጥላሉህ ብቻ ሳይሆን ሲያሞግሱህም ፍራ፡፡ “የሚወዱህን ብቻም ሳይሆን የሚጠሉህንም ውደድ፡፡ የሚወዱትን ብቻ መውደድማ የማንም ባሕርይ ነው፡፡” ያለህ ሲመስልህ የሌለህ መሆንህንም አስብ፡፡ ከሁሉም ከሁሉም ትናንትን፣ ዛሬንና ነገን ከነልዩነትና አንድነታቸው አትዘንጋቸው፡፡ …

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሌሎችም ከደሴ አስተዳዳሪዎች ይማሩ ! ግርማ ካሳ

ግንቦት ሰባት ሻዕቢያን ለማስደሰት ብዙ ርቀት ተጉዟል፡፡ ትልቁን ማገር አማራን እስከማዋረድና እስከማንጓጠጥ ደርሶ የአሳዳሪዎቹን አመኔታ ለማግኘት ቢሞክርም በእስካሁኑ ሁኔታ የተሣካለት አይመስልም፡፡ መጻፍ ይቻላል፡፡ ቀላል ነው፡፡ ማለም ይቻላል፤ ይህም ቀላል ነው፡፡ ፍሬ ያለው ነገር ሠርቶ ለጠላትም ለወዳጅም ማሳየት ግን ከባድ ነው፡፡ ስለዚህ ይመስለኛል ይህ ድርጅት ተደጋግሞ እንደሚነገረው በአሥር ዓመታት ውስጥ አማራን ከማዋረድ ትልቅ ስኬቱ ውጪ አንድም ፋይዳ ያለው ነገር አከናውኖ ለድል ሊያበቃን ያልቻለው፡፡ በግንቦት ሰባት አመራር ውስጥ አማራን ላለማካተት ቆራጥነትን ማሳየት፣በጎሣ ከተደራጁ ሌሎች ዘውጎች ጋር ጠብ እርግፍ እያሉ ወድቆ በመነሳት ዕርቅና ድርድርን ሲያካሂዱ አማራን ግን ቤተ ክርስቲያን እንደገባች ውሻ በመቁጠር መወረፍና መሳደብ፣(what the ferenjis call double standard) ስለ አማራ በተናገሩ ቁጥር ይህን ብሔር ወንጀለኛና የታሪክ ተወቃሽ አድርጎ ማቅረብ፣ ወዘተ. ይህ ሁሉ አበሳ በርግጥም ግንቦት ሰባት አምኖበትም ባይሆን የአሳዳሪዎቹን አንጀት ያራራና ትግሉን ያቀላጠፈ መስሎት ሊሆን ይችላል፡፡ ቢሆንም “የወጋ ቢረሳ የተወጋ አይረሳ” እንደሚባለው ሆኖ ቀን ሲያልፍ ይህ ሁሉ ግንቦት ሰባት በአማራ ላይ ያስቀመጠው ጠባሳ መገለጡ አይቀርምና ቢያንስ ያስተዛዝባል፡፡ “አማራ በሁሉም ዘንድ የሰረፀ ስለሆነ ለብቻው መደራጀት አያስፈልገውም፤ መደራጀቱ አደጋ አለው፤ ለሌሎችም ጥሩ አርአያ አይሆንም” ከሚል ቅን አስተሳሰብ በመነጨም ከሆነ ሃሳቡ እንደሃሳብ ጥሩ ሆኖ ለአማራው ግን አይጠቅመውምና ይህ ቅቤ አንጓችነት ይቅርበት፤ ይልቁንስ ከቁስሉ አግዙት፤ ከውርጩ ተካፈሉለት፡፡ ዝምታውና ምናኔው አላዋጣውም፤ ለባሰ ዕልቂት ዳረገው እንጂ፡፡ ስለሆነም እርሱም ይደራጅና ይሞክረው፡፡

ለግንቦት ሰባት ምክር የሚለግሱ ሰዎች እንዲህ ሲሉ ይደመጣሉ፡፡ ግንቦት ሰባት አሥመራ ላይ መሽጎ ለኢትዮጵያ ምንም ለውጥ ስለማያመጣ ሌላ አዋጪ ሥልት ቢቀይስ ይሻለዋል፡፡ የሚዲያ ትግል አንድን ሀገር ነፃ አውጥቶ አያውቅም፡፡ “አሥር አረንጓዴ ጠርሙሶች በግድግዳ ላይ … ድንገት አንዱ ወድቆ ቢሰበር ዘጠኝ ይቀራል” ይባል የነበረውን የሂሣብ ማስተማሪያ ዘዴ ለውጠው “አንድ መቶ አማሮች በግድግዳ ላይ፣ ድንገት ዘጠና ዘጠኙ ወድቀው ቢሞቱ ስንት አማሮች ሞቱ” በሚል ተክተው ልጆቻቸው አማራን አምርረው እንዲጠሉ ከሚያስተምሩ ወያኔዎችና ሻዕቢዎች ለዚህች ሀገር መቅሰፍት እንጂ ደግ ነገር አይኖርምና ብዙ ሳይረፍድ ሌላ መላ ፈልጉ፡፡ “አገባሻለሁ ያለሽ ላያገባሽ፣ ከባልሽ ጋር ሆድ አትባባሽ” ይባላልና ከሃያና ሰላሳ ሚሊዮን አማራ ጋር ቂም ከምትያያዙ አካሄዳችሁን ፈትሹ፣ አስተካክሉም፡፡ ካልሆነላችሁም ሁሉንም ነገር ተውትና በሰላም ኑሩ፤ በካፈርኩ አይመልሰኝ እናንተንም ሀገራችሁንም  አትጉዱ፡፡ ኢትዮጵያን እንደሆነ ፈጣሪዋ አይተዋትም፡፡ ይዋል ይደር እንጂ ነፃ መውጣቷ አይቀርም፡፡ እናም ከመጥፎ ባል ፈት ሆኖ በግልሙትና መኖርም ወርቅ ነውና ሰድባችሁ ለሰዳቢ ከምታጋልጡን ይልቅ ሁሉም ይቅርባችሁና በየምትኖሩበት ሀገር የስደት ኑሯችሁን እስከነፃነት ቀን ድረስ ኑሩ፡፡ እናንተን ተስፋ እያደረገ አንጋጥጦ የሚጠብቀው የሕዝብ ቁጥር ብዙ ነው፡፡ እናንተን ተማምኖ ወደትግል በመግባት የጠላቶቹ ጭዳ ሆኖ የሚቀረውም ብዙ ነው፡፡ አሥመራ ገብቶ ያለቀውን የአማራ ልሂቅና ታጋይ በቤቱ ይቁጠረው ብቻ የምናልፈው አይደለም፡፡ እናንተ ግን አያርማችሁም፡፡ ዘላለም እዚያው ናችሁ፡፡ የራሱን ሕዝብ እንደጊንጥ እየነደፈ ከሚጨርስና በእሳት ወላፈን እየገረፈ ሀገሪቱን ባዶ ሊያስቀር ምንም ካልቀረው ዕብድ ሰው አንድም ነገር አታገኙምና ከምጣድ በማይወጣ የተስፋ ዳቦ ሕዝብን ዕንቁልልጭ ከምትሉና ለትዝብት ከምትዳረጉ ወደሰላማዊ ኑሯችሁ ተመለሱ፤ በቃ “ሞክረው ነበር አልሆነላቸውም” ቢባልም ለታሪክ ድርሣን ትበቃላችሁና ምንም ማለት አይደለም፡፡ የአንድን ነገር አዋጭነት ለማረጋገጥ አሥር ዓመት ከበቂ በላይ ነው፡፡ ለልባም ሦስት ቀናትም በቂ ናቸው፡፡ ለሰነፍ ደግሞ ሦስት ወራትም ብዙ ናቸው፡፡ አሥር ዓመት ግን ከዚያች የበሬው የአባለዘር ኮረጆ ይወድቅልኛል ብላ ስትከተለው እንደዋለች ከሚወራላት ቀበሮ የበለጠ ስም የሌለው ሞኝነት ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ደግሞ ሕይወቱን ለማትረፍ መከራ ስቃዩን የሚያየውን የአማራን ሕዝብ በታሪካዊ ጠላቶቹ ላይ ተደርቦ ደንቃራ መሆን ታሪክ ራሱ ይቅር የማይለው ትልቅ ጥፋት ነው፡፡ ቢቻል መርዳት እንጂ ማደናቀፍና ጥረትን ማንኳሰስ ተገቢ አይደለም፡፡

ከዚህ በተረፈ ግንቦቶችና የአማራ ንቅናቄዎች መግባባት ካልቻላችሁ በከንቱ ኃይልና ጊዜያችሁን ባታጠፉ ይመረጣል፡፡ ሰሞኑን እንኳን በሚዲያ ላይ የምናየው የብዕር ጦርነት የትግሉ ሁሉ መነሻና መድረሻ የተቃውሞው ጎራ የርስ በርስ ፍጭት እስኪመስል ድረስ ስንደናቆር ከረምን፡፡ ስለዚህ በከንቱ ጉልበታችሁን የምታባክኑ ሁሉ ተረሳሱ፡፡ ወያኔን ደስ ከሚያሰኙት ነገሮች ውስጥ አንዱና ምናልባትም ዋናው ይህ ዓይነቱ በተቃዋሚዎች መካከል የሚፈጠር ንትርክና እንካስላንትያ ነው፡፡ እነሱ ለወሬ ጊዜ የላቸውም፡፡ እኛ ግን ሌላ መሥራት ቢያቅተን እኛው በኛው እንጨቃጨቅ ብለን የቆረጥን እንመስላለን፡፡ ሙያ በልብ ብለን ወደሥራችን ካልገባን ስንጮህ ውለን ስንጮህ ብናድር ጠብ የሚል ነገር አይገኝም፡፡ ግን እነሱ ራሳቸው እንዴት ይስቁብን! በውነቱ ደህና አድርገው ሠሩልን፡፡ “ሠራሁለት!” የምትል የአንዲት ሴት ድምፃዊት ዘፈን አሁን ብዕሬን ላስቀምጥ ስል ትዝ አለችኝ፡፡ ጋበዝኳችሁ፡፡

2 Comments

  1. waw ! etsub dinq tshuf new !

    yehe tshuf angafawin Gazetegna Mulugeta Lulen astawesegn

    endeh new enji jal ! qomatan qomata kalalut gebto yefeteftal alu !

    awo be propaganda , 4 kilo yegeba tagay altaytom altesemtom !!

    ye G7 memereya tinish qolo yezeh ke asharo tetega !honena-

    beyederesebet timret timret eyale, be 6 wer netsa awtahalehu yalewin degafe, yehew 7 ametun yaze birr eyesebesebe ,tegbo be Amaraw lay yagesal !

    YALGEBACHEW NEGER BENOR Oromow, ke Gurage ke kembata sayhon , kegna l

    ende !ke 30 eske 35 oooooo , belay nen eko

    Amaroch tinish qolo yezen ke asharo metegat ayasfeligenim !

    yerasu yemetemamen sew ,,ye tutt abat ayasfelgewim !!

    ty

    ke Amaroch gar new yetegabaw ! meleyayet aychalim !YE dv tiwlidun wedegon entewewna !!

Comments are closed.

Share