የአድዋ ድል፦ የዘመኑ ኢትዮጵያዊ ትውልድ የማንነት ፈተና – ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት

ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት             ረቡዕ የካቲት ፳፫ ቀን ፪ሺህ፰  ..            ቅፅ ቁጥር

ነፃነት-ወዳድ ለሆነው የዓለም ጥቁር ሕዝብ በሙሉ መመኪያ የሆነው የአድዋ ድል ለ፻፳ኛ (ለአንድ መቶ ሃያኛ) ጊዜ ዛሬ ተከብሮ ይውላል። ይህንን ቀን ኢትዮጵያውያን በታሪካቸው በድሉ ትክክለኛ የነፃነት መንፈስ ለማክበር ያልታደሉባቸው ዘመኖች፦ በፋሽስት ጣሊያን ወረራ ከ፲፱፻፳፰ እስከ ፲፱፻፳፱ ዓም በነበሩት ፭(አምሥት) ዓመታት፣ እንዲሁም ከ፲፱፻፹፫ ዓም ወዲህ ለ፳፭(ለሃያ አምሥት) ዓመታት በትግሬ-ወያኔ አገዛዝ ነው። የአድዋ ድል ሲነሣ ምንጊዜም ተነጥሎ የማይቀረው የኢትዮጵያን አርበኞች እየመሩ ጦርነቱን በድል የተወጡት ታላቁ ንጉሠ-ነገሥታችን ዳግማዊ አፄ ምኒልክ እና ባለቤታቸው እቴጌ ጣይቱ ብጡል፥ ብርሃን-ዘኢትዮጵያ ናቸው። በእኒህ ታላላቅ ኢትዮጵያውያን መሪዎች ሥር ቁጥራቸው በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ አርበኞች በየጦር መሪዎቻቸው ሥር ተሰልፈው ለውዲቷ አገራቸው ሕይዎታቸውን ገብረዋል፣ ደማቸውን አፍስሰዋል፣ አጥንታቸውን ከስክሰዋል። ስለዚህ የአድዋን ድል የምናከብረው እኒህን ለአገራችን ባለውለታ የሆኑ ታላላቅ አርበኞቻችንን ለመዘከር፣ እንዲሁም እኛም በዘመናችን የበኩላችንን የትውልድ አደራችንን እንድንወጣ ቃልኪዳን ለመግባት መሆን ይገባዋል። ነገር ግን ባለፉት ፳፭(ሃያ አምሥት) በነበረው ጊዜ ለአድዋ ድል አከባበር ኢትዮጵያውያን ያደረጉት እንቅስቃሴ የተዘበራረቀ ምሥል ይታይበታል።

ከሦሥት ዓመታት በፊት «ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት» ፻፲፯ኛውን የአድዋ ድል በዓል በሕዝባዊ ስብሰባ ለመዘከር በዋሽንግተን ዲሲ ከተማ ጥሪ ሲያደርግ በዝግጅቱ ላይ ለመካፈል የተገኙት ታዳሚዎች ከ፶ አይበልጡም ነበር። በተመሣሣይ ቀን እና ሰዓት «የኢትዮጵያዊነት ውርስ እና ቅርስ ማኅበረሰብ በሰሜን አሜሪካ» በጠራውም ዝግጅት የተገኙት ታዳሚዎች ጥቂት መቶ ነበሩ። በዋሽንግተን ዲሲ እና በአካባቢዋ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ-ኢትዮጵያውያን እንደሚኖሩ ይታወቃል። በመሆኑም ይህ ማኅበረሰብ የራሱን የድል በዓል ለመዘከር ቸልታ ያሣየበትን ምክንያት በጥልቀት ካልመረመርነው እንቆቅልሽ ሊሆንብን ይችላል። ነገር ግን በወቅቱ «አለን አለን» የሚሉ የፖለቲካ ድርጅቶች እና ልሂቃን በታላቁ ኢትዮጵያዊ ንጉሠነገሥት በዳግማዊ አፄ ምኒልክ ላይ ያወርዱ የነበረው የተቀነባበረ የማጥላላት ፕሮፓጋንዳ አንዱ አብይ ምክንያት እንደነበረ መታወቅ አለበት። እኒህ ድርጅቶች እና ልሂቃን አሁንም ከዚሁ አቋማቸው ፈቀቅ አላሉም። ሌሎችም በኢትዮጵያ ስም የተደራጁ የፖለቲካ እና የሲቪክ ድርጅቶች በአድዋ ድል እና ለድሉም መገኘት የመሪነቱን ሚና በተጫወቱት በታላቁ ንጉሠነገሥታችን በዳግማዊ አፄ ምኒልክ ላይ ያላቸውን ግልፅ አቋም በይፋ ለሕዝብ አላሣወቁም፣ ወይም ለሕዝባዊ ስብሰባ ሲጠሩ «የእናቴ መቀነት አደናቀፈኝ» ዓይነት አልባሌ ምክንያት እየደረደሩ ተወካዮቻቸውን ሣይልኩ የሚቀሩ ናቸው። ስለዚህ እኛ ኢትዮጵያውያን በጠቅላላ እኒህን የፖለቲካ እና የሲቪክ ድርጅቶች እንዲሁም «ልሂቃን» በዚህ የኢትዮጵያዊነት መለኪያ በሆነ አብይ ጉዳይ ላይ ያላቸውን አቋም እንዲገልፁ ፊት ለፊት ተጋፍጠን መጠየቅ ይገባናል። ይህ የዜግነት እና የትውልድ ግዴታችን ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያዊነት ወንጀል: ኢትዮጵያዉያን አገራቸዉ እና መዳረሻቸዉ የት ይሆን?

«ሣይደግስ አይጣላም» ይባላል። የአድዋ ድል በዓል አከባበር በአገራችን በኢትዮጵያ የደበዘዘውን ያህል፣ በውጪ አገሮች በስደት በሚኖረው ኢትዮጵያዊ ማኅበረሰብ በኩል የሚታየው እንቅስቃሴ ግን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ወደትክክለኛው መሥመር የመምጣት አዝማሚያ ይታይበታል። በዚህ ረገድ በውጪ አገር ኃላፊነቱን ወስደው በዓሉ በትክክለኛ ገፅታው እንዲከበር የሚያደርጉት የሲቪክ ድርጅቶች ሊመሠገኑ ይገባል። ሆኖም ኃላፊነታችን በዚህ አያቆምም፣ ሊቆምም አይገባውም። በየትኛውም የዓለም ክፍል ያለን እኛ ኢትዮጵያውያን፣ የአድዋ ድል በትክክለኛው የድሉ በዓል መንፈስ እንዲከበር በመጀመሪያ በየማኅበረሰባችን ይህ በዓል በየዓመቱ በጋራ ከምናከብራቸው በዓሎች አንዱ ሆኖ እንዲቆጠር ማድረግ አለብን። ለዚህም በኢትዮጵያ ስም የተደራጁ የሲቪክ እና የፖለቲካ ድርጅቶች የጋራ ኃላፊነቱን እንዲወስዱ ማስገደድ ይገባናል። ከዚያ ባሻገር ከኢትዮጵያ ውጪ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ማኅበረሰብ ለዚህ በዓል ያለው ግንዛቤ እንዲጎለብት ከፍተኛ የማስተዋወቅ ሥራ ማራመድ ተገቢ ነው። ይህንን ካደረግን ትውልዳችን ካሉበት ብሔራዊ ግዴታዎች ቢያንስ አንዱን ለመወጣት እንደሞከረ ታሣቢ ይሆንለታል። ይህንን ሣናደርግ ከቀረን ግን ለተተኪው ኢትዮጵያዊ ትውልድ የምናወርሰው «ለነፃነቴ አልበገርም» ባይነትን ሣይሆን በኢትዮጵያዊ ማንነቱ ማፈርን መሆኑን ለቅፅበትም ያህል መዘንጋት አይገባንም።

 

የአድዋ ድል የመላው ጥቁር ሕዝብ መመኪያ ነው!

ኢትዮጵያ በጀግኖች ልጇቿ መስዋዕትነት ለዘለዓለም ፀንታ ትኖራለች!

1 Comment

  1. Its good and proud history of our fore father they did their own history they defended our country by primitive weapon.. However at this time the border of our country given for Sudan and our land of wolkite taken away ,our people identity changed by force instead of only talking about history why don’t you do our history.

Comments are closed.

Share