አዕምሮህ በትቢት ተወጥሮ
ልብህ በቅናት ነፍሮ
እንባህ ጥላቻን ያበቀለ
የቀረበውን አርቆ የወረደውን የሰቀለ
ህዝብን ክህዝብ እያጣላህ
የአሉባልታ ወሬ እያስፋፋህ
የሰላምን ተስፋ ያጨለምክ
የዕድገትና የሰላም ችግኝ የነቀልክ
የግል ኑሮህ አልሳካ ቢል
አገር ትጥፋ ህዝብም ይለቅ የምትል
ይድረስ ለሚመለከትህ
ይህ ከሆነ ገፀ ባህሪህ
ቀናተኛ የማትሠራ
ቀኑ የከዳህ ስታወራ
የድሃ ጉሮሮ አናቂ
የወሬ ቋት አሳባቂ
ከሞቀበት አዳናቂ
የኔ የምትለው የሌለህ
የአዕምሮ ድሃ የሆንህ
ይድረስ ለሚመለከትህ
ይህ ከሆነ ገፀ ባህሪህ
ለከርሳሙ ሆድህ ብለህ
ሰብዕናህን ለንዋይ ሽጠህ
የውርደት ሸማን ተላብሰህ
አባ ዳኘው ሞት ሲጠራህ
የት ይሆን ያኔ መግቢያህ
ይድረስ ለሚመለከትህ
ይህ ከሆነ ገፀ ባህሪህ
ሙሉ እንጀራ አስጠልቶህ
ፍርፋሪ የሚያስምኝህ
የራስህን ሆድ አብልጠህ
የማታስብ ለልጆችህ
በአኩይ ዓላማ ደንዝዘህ
ትቀራለህ ከንቱ ሁነህ
ይድረስ ለሚመለከትህ
ይህ ከሆነ ገፀ ባህሪህ
የኢትዮጵያ አምላክ ተፋርዶ
ሳትሞት በቁምህ አዋርዶ
የሞት ሞትን አስጎንጭቶ
ከጌቶችህ ጋር አጋጭቶ
በህሊና ፀፀት ገርፎ
የሠራ አካላትክን አርግፎ
በቁምህ ፍዳ ያስከፍልህ
የከሰረና ብኩን ያርግህ
ተማርኩ ብለህ የደነቆርክ
በትዕቢት የተወጠርክ
የኢትዮጵያን ሞት የተመኘህ
ዜሮ ራስህ ባዶ ያርግህ
የወለድከውን አያስምህ
የዘራኸውን አያስቅምህ
ዜሮ እንደሆንክ ዜሮ ያርግህ
ይድረስ ለሚመለከትህ
ይህ ከሆነ ገፀ ባህሪህ
ይድረስ ለሚመለከትህ ( እኔን ጨምሮ ) (ዘ-ጌርሣም)
የእንግዳ ልኡክ ጽሁፎችን የአርትዖት አምዶችን ወይም አስተያየቶችን እና ትንታኔዎች መጣጥፎችን እንቀበላለን:: ሀሳበወትን እና እውቀትዎን ለአንባቢዎቻችን እንዲያካፍሉ እንጋብዛችኋለን። ጽሑፋችሁ በዓለም ዙሪያ በሚሊዮን የሚቆጠሩ አንባቢዎችን ይደርሳል፣ ያለቀ ጽሁፍ በ admin@zehabesha.com በኩል ያቅርቡ! የሚሰነዘሩ አስተያየቶች ደራሲውን ብቻ የሚያንፀባርቁ እንጂ የዘ-ሐበሻ ዶት ኮም ኦፊሴላዊ ፖሊሲ ወይም አቋም የሚያንፀባርቁ አይሆኑም!!