ሰሞኑን በቁጥጥር ስር የዋሉትን ግለሰቦች በተመለከተ በአዲስ አበባ የሚገኙ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች አስተያየታቸውን ሰጡ

ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና የእስር ውሳኔውን ‹‹ጥሩ ነው›› ካሉ በኋላ ‹‹ስጋትም አለኝ›› ብለዋል

ሰሞኑን በቁጥጥር ስር የዋሉትን ግለሰቦች በተመለከተ በአዲስ አበባ የሚገኙ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች አስተያየታቸውን ሰጡ፡፡

በሙስናና በሰብዓዊ መብት ጥሰት ተጠርጥረው ሰሞኑን በቁጥጥር ስር የዋሉትን ግለሰቦች በተመለከተ ከአዲስ ዘመን አስተያየታቸውን የተጠየቁት የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አበበ አካሉ ‹‹ባለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት ስርዓቱ በሙስና የተዘፈቀ መሆኑን በተደጋጋሚ ስናነሳ ነበር፡፡›› ካሉ በኋላ በብድርና በእርዳታ የመጣ የደሀ ህዝብ ሀብት ያለአግባብ ለግለሰቦች ጥቅም ይውል እንዲሁም ከአገር እንዲወጣ ይደረግ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ‹‹በዚህ ምክንያትም በርካታ የተፎካካሪ ፓርቲዎች አባላት ተደብድበናል፤ ታስረናል፤ ብዙ ስቃይም ተቀብለናል›› ብለዋል፡፡አሁን በዚህ ደም መጣጭ ድርጊት የተሳተፉ ግለሰቦች በዚህ መልኩ ለፍርድ እንዲቀርቡ ማድረግ መቻሉ «አንጀት የሚያርስ» ተግባር ነው ሲሉ ገልጸዋል፡፡ ህዝቡ አሁንም ለውጡን በመደገፍ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጎን መቆሙን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስረድተዋል፡፡ አቶ አበበ ጨምረውም « እኛ ሙስናን በተዋጋን የሰብዓዊ መብት ጥሰት አለ ተገርፈናል፤አሁን ገራፊዎቻችን ጥፍር ነቃዮች፣ ሴቶችን የደፈሩ እና ያንገላቱ ወንዶችን ያሰቃዩ ግለሰቦች በዚህ መልኩ ለፍርድ ሲቀርቡ ማየታችን የነጻነት ቀናችንን ያከበርን ያህል ይሰማናል፤ ይህንን ሳያዩ የሞቱት ወገኖቻችን በጣም ያሳዝኑናል » ብለዋል። አሁንም በርካታ ሙሰኞች በየቤቱና በየተቋሙ ስላሉ እነዚህንም አጥርቶ ለፍርድ ማቅረቡ ቀጣይ የቤት ሥራ ሊሆን እንደሚገባም አሳስበዋል።

እርምጃው ጥሩ እንደሆነና ሲታገሉለት እንደነበረም ለአዲስ ዘመን የገለፁት፣ ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ‹‹የእኔ ስጋት ትላልቅ አሳዎቹ ይኑሩበት አይኑሩበት እርግጠኛ መሆን አልቻልኩም፣ እንደ አስፈላጊ እርምጃ ግን በጥሩ ጎኑ የሚታይ ነው›› ብለዋል፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ መንግሥት እርምጃ አብዛኛውን ጊዜ ትኩረቱን የሚያደርገው ትናንሽ አሳዎች ላይ ነው›› ያሉት ፕሮፌሰሩ፣ ‹‹ስለ ትልልቆቹ አሳዎች መረጃ ላይኖረኝ ይችላል፤ አልያም በሌላ ምክንያት ይታለፋሉ፤ አሁንም ይህ ሥራ እንደዚህ ላለመሆኑ እርግጠኛ ባንሆንም እርምጃው ግን በጣም የሚያስደስት ነው›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ታዋቂው የሙዚቃ ሰው ቴዲ ምትኩ በጠና ታሞ ሆስፒታል ገባ

ፕሮፌሰር መራራ ጉዳዩ መነካካቱ ጥሩ መሆኑን ጠቅሰው፣ የአንድ ሰሞን ግርግር እንዳይሆን ግን ስጋቱ አለኝ ይላሉ፡፡መንግሥት የአንድ ሰሞን የግርግር በሽታን ትቶ ውጤታማ የፍትህ ስርዓት በዳይን የሚቀጣ ተበዳይን የሚክስ አካሄድ መከተል እንደሚጠበቅበት አስታውቀዋል፡፡

የሲዳማ ሀርነት ንቅናቄና የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲ መድረክ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሚሊዮን ቱማቶ ደግሞ ‹‹ፓርቲያችን የሚታገልለት ዋናው ቁምነገር በሀገሪቱ የህግ የበላይነት እንዲሰፍን ነው›› ካሉ በኋላ ‹‹አሁን በመንግሥት እየተወሰደ ያለው እርምጃ እንደ ፓርቲ የምንደግፈውና ከለውጡ ጎንም እንድንቆም የሚያስችለን ነው›› ብለዋል።

ዶክተር ሚሊዮን ጨምረውም ‹‹በሀገሪቱ ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን የመገንባት ዋናው ነገር የህግ የበላይነት እንዲከበር ነው፡፡በዚህ ልክ እርምጃ መወሰድ መጀመሩ አገሪቱ ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ የሰጠችውን ቦታ እንዲሁም ለውጡ ምን ያህል የእውነት እንደሆነ ያመለክታል፡፡ ወደፊትም ሌሎች ህዝብ የተበደለባቸውንና ያለቀሰባቸውን ነገሮች በማጥራት ፍትህ እንዲገኝ ማድረግ ይገባል።

በአገሪቱ የተጀመረው ህዝቦችን የማቀራረብና ብሔራዊ መግባባትን የመፍጠር እርምጃ ይበል የሚያሰኝ ነው›› በማለት ይህ እርምጃ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አስስበዋል።
https://www.youtube.com/watch?v=Kiw-PSSXvLY

2 Comments

Comments are closed.

Share