በሐረር ከተማ ባሉ ነጋዴዎች ላይ እየተደረገ ያለው ጫና ተጠናክሮ ቀጥሏል

(ዘ-ሐበሻ)  በሐረር ከተማ ያለው የንግድ ማኀበረሰብ ከአቅም በላይ ግብር በመጠየቃቸው በርካቶች ስራቸውን ለማቆም መገደዳቸውን አስታወቁ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በተለይ መንግስት ከዛሬ 3 ዓመት በፊት ሐረር ሸዋ በር የሚገኙ ሱቆች ሙሉ ለሙሉ ተቃጥለው በቢሎዮን ብር የሚቆጠር ንብረት ከወደመ በኋላ የቦታውና የሶቆቹ ባለቤቶች እራሳቸው ዳግም ለመገንባትና ወደ ስራ ለመግባት ቢፈልጉም እስካሁን መንግስት ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል፡፡ የክልሉ አመራሮች ከኢህአዴግ የፌደራሉ አመራሮች ጋር በመመሳጠር ቦታውን ለገዥው ስርዓት ትስስርና ቅርበት ላላቸው ባለሃብቶች በህገወጥ መንገድ ለመሸጥ መንቀሳቀሱ ቁጣን ቀስቅሷል፡፡

የሱቆቹ ባለቤቶችም ንብረቶቹን ያቃጠለውና ያወደመው መንግስት ሆን ብሎ ነው የሚል እምነት እንዳላቸውም እየተገለፀ ይገኛል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ጀጎል ግንብ ዙሪያ ያሉ ሱቆችም በቅርቡ ሊፈርሱ መሆኑም ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
በሚፈርሱ ሱቆች ምክንያትም የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሳይንስና ባህል ማዕከል(ዩኔስኮ) ለነጋዴዎች የሚሆን በቂ ካሳ ቢመድብም ምንግስት ለራሱ አድርጎት ያለምንም ካሳ ነጋዴዎችን ለማስነሳት እየተንቀሳቀሰ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡ በዚህ ዙሪያ የክልሉን እና የከተማውን መስተዳደር ለማናገር ተደጋጋሚ ጥረት ብናደርግም አልተሳካም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢሕአዴግ በምርጫው በደረሰበት መደናገጥ የ5 ለ1 ጠርናፊዎቹን መገምገም ጀመረ
Share