በቤኒሻንጉል ክልል በሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ ጥቃት መፈጸሙ ተገለጸ

(BBN) በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ ጥቃት መፈጸሙ ተገለጸ፡፡ ጥቃቱ በክልሉ ልዩ ኃይል ፖሊስ እገዛ የተፈጸመ መሆኑም ተገልጿል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ የሟቾች ቁጥር ሃምሳ መድረሱ የተነገረ ሲሆን፣ ከ300 በላይ መኖሪያ ቤቶች መቃጠላቸውም ተነግሯል፡፡ በጥይት ተመትተው የተጎዱ ሰዎች ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውንም ስለ ጉዳዩ የተከታተሉ የመረጃ አካላት ተናግረዋል፡፡ አንዳንድ የሀገር ውስጥ ሚዲያዎች በከሉላቸው ተጎጂዎች ወደ ነቀምቴ ሆስፒታል መወሰዳቸውን ዘግበዋል፡፡

ድርጊቱ የተፈጸመው በቤንሻንጉል ክልል ከማሼ ዞን፣ ሎጅጋንፎይ ወረዳ፣ ሎደዴሳ ቀበሌ መሆኑን የገለጹት መረጃዎች፣ እንዳሁኑ አይሁን እንጂ ከዚህ ቀደምም ግጭት ይከሰት እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡ የአሁኑ ግጭት ግን በስፋትም ሆነ በመጠን ገዘፍ ማለቱ ነው የተነገረው፡፡ የግጭቱ መነሻ የተባለው ጉዳይ፣ በተጠቀሱት ስፍራዎች የሚገኙ የአማራ ተወላጆችን ንብረት ከመዝረፍ ጋር የተያያዘ እንደሆነ ነው የተገለጸው፡፡ ይህ ዓይነቱ ድርጊት ከዚህ ቀደምም ሲፈጸም መቆየቱን የጠቆሙት መረጃዎች፣ አሁን ግን ተባብሶ ከፍተኛ ግጭት እንዲፈጸም ምክንያት መሆኑን መረጃዎቹ ይጠቁማሉ፡፡

በትላንትናው ዕለት በተፈጸመው ጥቃት የክልሉ ልዩ ፖሊስ እጅ እንዳለበት የተነገረ ሲሆን፣ ፖሊስ ከአካባቢው ማኅበረሰብ ጋር ተባብሮ ድርጊቱን እንደፈጸመው እየተገለጸ ይገኛል፡፡ ጥቃቱን ተከትሎ የበርካታ ሰዎች አስከሬን በየቦታው ወድቆ መታየቱን ከዓይን እማኞች መረዳታቸውን የተለያዩ አካላት ገልጸዋል፡፡ ጥቃቱ የተፈጸመው ትላንት ጥቅምት 17 ቀን 2010 መሆኑን የጠቀሱት መረጃዎች፣ አካባቢው በአሁን ሰዓት በከፍተኛ ውጥረት ላይ ይገኛልም ብለዋል-መረጃዎቹ፡፡ ጉዳዩን አስመልክት እስካሁን ድረስ የፌደራል መንግስቱ የሰጠው መግለጫ የለም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የስርዓቱ ደጋፊ የሆነችው ድምጻዊት ሃመልማል አባተ ለሁለተኛ ጊዜ ከአሜሪካ አፍራ ወደ ኢትዮጵያ ተመለሰች
Share