በኤርምያስ ለገሰና ፣ተወልደ (ተቦርነ) በየነ አማካይነት ጁላይ 13፣ 2017 የ 34ኛውን የፌዴሬሽን አመታዊ በዓል አስመልክቶ አንድ ሰዓት ከሃያ ደቂቃ የፈጀ የእፍታ ፕሮግራም ተላልፎ ነበር።
በግሌ በፕሮግራሙ ከቀረበው ቁምነገር አንጻርና በቀጥታ ፌዴሬሽኑን በሚመለከተው ጉዳይ ፣ ከአስራ አምስት እስከ ሃያ ደቂቃ ባለ ጊዜ ሊቀርብ ይችል የነበረ ቢመስለኝም፣ የፕሮግራሙ አዘጋጅም ሆነ የድርጅቱ ኃላፊ ባለመሆኔ በአስተያየት ደረጃ ብቻ የሚቀመጥ ይሆናል።
ፕሮግራሙ ላይ የቀረቡ አስተያየቶች ላይ ስናተኩር ግልጽ የሚሆነው ነገር ኤርምያስም ሆነ ተቦርነ ስለ ፌዴሬሽኑ ያላቸው ግንዛቤና እውቀት ውሱን መሆኑንና፣ ሲያትል በቆዩባቸው ጊዜአትም ቢያንስ የዘንድሮውን ዝግጅት አስመልክቶ በአንዳንድ ጉዳዮች ሁነኛ መረጃ ለማሰባሰብ በቂ ጥረት እንዳላደረጉ ነው። ይሄም በመሆኑ ዘገባቸው በአንዳንድ መሰረታዊ ጉዳዮች ላይ የተሳሳተ መረጃ እንዲያቀርቡ አድርጓቸዋል።
ስለ ፌዴሬሽኑ ባላቸው ውሱን እውቀት ላይ በመመስረት የቀረበውን ዝግጅት የተከታተሉ ወገኖች፣ የተሳሳተ አመለካከት እንዳይኖራቸው፣ በዝግጅቱም ላይ የቀረቡትን አንዳንድ የታዛቡ መረጃዎች ለማስተካከል ይጠቅማል በሚል እንደ አንድ ለፌዴሬሽኑ ተቆርቋሪ አባል ይሄንን አጭር ጽሁፍ የመጻፍ ግዴታ ተሰምቶኛል። በቀረበው ሪፖርት የተዛባ ዘገባ ቅር ቢለኝም ግን፣ በዓሉን አስመልክቶ የሚወክሉት ተቋም ሌሎች የዜና ተቋማት ለፌዴሬሽኑ አንዳደረጉት ሁሉ ፣ላደረገው ትብብር ምስጋናዬን አቀርባለሁ።
እንደመንደርደሪያ
የሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያውያን ስፖርት ፌዴሬሽን ፣ እያንዳንዱ ክለብ በአማካይ ከሀያአምስት አስከ ሰላሳ አባል ያሏቸው፣ በሰላሳ አንድ ክለቦች የተዋቀረ ፌዴሬሽን ነው።የድርጅቱን ዓመታዊው በዓል ድምቀት ሰጥተው እውን አንዲሆን የሚያደርጉት እነዚህ ክለቦች፣ በያሉበት ከተማ አመቱን ሙሉ ተቀናጅተው እግር ኳስ የሚጫወቱ ሲሆን ፣ መሃል ዓመት ላይ ደግሞ አካባቢያዊ ውድድር በማካሄድ ራሳቸውን ለአመታዊው ዝግጅት ያሰናዳሉ።
ድርጅታዊ አሰራርን በተመለከተ የፌዴሬሽኑ የስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ፣ አመቱን በሙሉ ሊባል በሚችል መልኩ ፣ በሳምንት አንድ ጊዜ በመሰብሰብ ሃላፊነቱን ይወጣል። የፌዴሬሽኑ የቦርድ አባላትና የስራ አስኪያጅ ኮሚቴው በአንድነት፣ በዓመት ሁለት ጊዜ በአካል በመገናኘት፣ ቀናት የፈጁ ስብሰባዎች ሲያካሂዱ፣እንዳስፈላጊነቱ ደግሞ በዓመት ውስጥ ሶስትም ሆነ አራት አምስት ጊዜ በቴሌ ኮንፈረንስ ስብሰባ ያካሂዳሉ።
ለአመታዊው ዝግጅት ከ 18 እስከ 25 ተጫዋቾችና አሰላጣኞችን በሚመለከት የጉዞ፣ የሆቴልና የቀለብ ወጪ፣ በዋናነት የእያንዳንዱ ክለብ ሃላፊነት ነው። ፌዴሬሽኑ ለእያንዳንዱ ክለብ አራት አራት ክፍሎችን፣ በጠቅላላው 124 ክፍሎችን በራሱ ወጭ ስለሚሸፍንና፣አቅም በፈቀደ መጠንም ሌላ ድጎማ ስለሚያደርግ ፣ትንሽም ቢሆን የክለቦቹን ወጪ ይቀንስላቸዋል።
ይሄም ሆኖ ግን አንድ ተጫዋች የጉዞ ወጭ ከፍሎ፣የሰባትና ስምንት ቀን ሆቴልና ቀለብን ለመሸፈን በአማካይ አስከ አንድ ሺህ ብር ድረስ ያስፈልገዋል። ይሄ ወጭ እያንዳንዱ ከስራ ገበታው ባለመገኘት የሚያጣውን( አንደየግለሰቡ የስራ አይነትና ገቢ ይለያያል ) አይጨምርም። ይሄንንም ወጭ እያንዳንዱ ተጫዋችና ወይንም ክለብ ማውጣት ስላለበት ከተጫዋቾቹ ኪስና፣ በሚኖሩባቸው ከተሞች ካሉ አባላቶቻቸውና ደጋፊዎቻቸው በሚገኝ መዋጮ በማሰባሰብ፣ የኛ የሚሉትን ፌዴሬሽን ላለፉት 34 ዓመታት አቅፈውና ደግፈው ፣ በሰሜን አሜሪካ ብቸኛው ኢትዮጵያውያንን አሰባሳቢ ድርጅት ለማድረግ በቅተዋል።
ይሄ የፈለጉትን የፖለቲካ አመለካከትና ሃይማኖት ይኑራቸው አይኑራቸው፣ ኢትዮጵያውያንና ኳስ አፍቃሪ በመሆናቸው ብቻ የሚሰባሰቡበት ድርጅት፣ የረጅም ጊዜ ቆይታውና የጥንካሬው ሚስጥር በዋናነት ባለቤትነት በሚሰማቸው ከ750 በላይ ባሉ አባላቱና በየክለቦቹ ባሉ መሪዎችና፣ በፌዴሬሽኑ ሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ መስዋአትነት ነው።
የክለቦቹና የፌዴሬሽኑ ኢትዮጵያውያንን፣ ኢትዮጵያውያን በመሆናቸው ብቻ ለማሰባሰብ የሚያደርጉት ጥረትም ፣በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ በርካታ ኢትዮጵያውያን ዘንድ ተቀባይነት በማግኘቱ፣ አድሜ ጠገብ ብቻ ሳይሆን ምናልባት ከኢትዮጵያ ውጭ በአስር ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ ለሳምንት በማስተናገድ ብቸኛው ተቋም ለመሆን በቅቷል።
ከዚህ ቀጥሎ በአፍታ ዝግጅት ላይ የተሳሳቱ መረጃዎችን አስመልክቶ ስለአናዳንዶቹ የራሴን ሃሳብ አቀርባለሁ።
‘የዛሬ አምስት ዓመት ድርጅቱ ለሁለት ሲከፈልና አደጋ ውስጥ እያለ ‘ … በሚል ስለተዘገበው
ድርጅታችን የዛሬ አምስት ዓመት የተወሰኑ ግለሰቦች ስማችንን በሕገ ወጥ መንገድ ቀምተው ለመደራጀት ጥረት እያደረጉ መሆኑን ስለደረሰበት ፣ የመደራጀት መብታቸውን የመቃወም አንዳችም ስልጣንም ሆነ ፍላጎት ሳይኖረን፣ ስማችንን ግን ከቀማኛ የማስጣል ሃላፊነት ስለነበረብን ክስ መስርተን፣ በሕግ አግባብ ስማችንን አስመልሰናል። ከዚህ ውጭ በፌዴሬሽኑ ከታቀፉ 30 ክለቦች ውስጥ ከሶስት ክለቦች የተወሰኑ ግለሰቦች አዲሱን ስብስብ ከመቀላቀላቸው የዘለለ ፣ ፌዴሬሽናችን ክፍፍልም ሆን የህልውና አደጋ አልነበረበትም። ግልጽነት ያለው፣ አባላቱ ፌዴሬሽኑ ላይ የባለቤትነት ስሜት ያላቸው፣ ህልውናውን አስመልክቶ ቀናኢ የሆኑ ፣ ድርጅቱም በራሱ የሚተማመን በመሆኑ ፣ ምንም ኃይል ሰርጎ ገብቶ ያዳክመናል ወይንም ያፈርሰናል የሚል ፍራቻ የለንም። እንዲህ ያለ ፍራቻ ባይኖረንም ግን ነቅተን ከመጠባበቅ ወደኋላ ብለን አናውቅም።
ከዚህ በመነሳትም ፌዴሬሽናችን ስማችንን በህጋዊ መንገድ ካስመለሰ በኋላ ፣አሳዋን ይባል የነበረውን ድርጅት አስመልክቶ አንድም ቀን አንደተቀናቃኛችን ወይንም ተፎካካሪያችን አይቶ፣ ድርጅቱን ለማወክም ሆነ ለማፍረስ ሳይንቀሳቀስ ድርጅቱ (ድርጅት ከተባለ)በራሱ ክሽፈት የከሰመ ድርጅት ነው።
‘በዚህ ወቅት መስዋአትነት የከፈሉ ሙዚቀኛች ‘…
ከፌዴሬሽኑ ጋር ኮንትራት ተፈራርመውና የሚከፈላቸውን ገንዘብ ተደራድረው ለታዳሚዎቻችን የሙዚቃ ዝግጅት ያደረጉ ዘፋኞቸና የሙዚቃ ባለሞያዎች ፣ ሁልጊዜም ተገቢውን ክብር እንድምንሰጥ፣ ከዚህ ውጭ ግን፣ በሌለና ባልነበረ የመከፋፈል አደጋ መስዋአት ከፈሉ የሚያስብል የማውቀው አንድም ነገር ስላልነበረ ብዙም ማለት አይቻልም።
የሐመልማል አባተን መድረክ ላይ መገኘት አስመልክቶ
‘
‘ልዩ እንግዳ አለን በሚል ማን እንደሆን ሳያስታውቁ (ለማን?) በጓሮ በር አስገብተው…ወዘተ የሚል ወቀሳ መሰንዘሩ የሚገርም ነው። በአንድ የሙዚቃ ዝግጅት ላይ ልዩ እንግዳ መኖር፣ ያልዩ እንግዳ ማንነትም አለመታወቅ አዲስ ነገር አይደለም። ሐመልማል አሉ ከሚባሉት ዘፋኞች አንዷ መሆኗ የሚያጠራጥር አይመስለኝም፣ ይሄን ብቃቷን ደግሞ ዳግም መድረክ ላይ አስመስክራ እንግዶቻችንን አስደስታለች።
ፌዴሬሽናችን ሐመልማል መድረክ ላይ ለመጫወት ከመፈለጓ ውጭ ፣ለመጫወት አንዳችም ቅድመ-ሁኔታ ሳያደርግ በገዛ ፍቃዱዋ ከመዝፈኗ በፊት ባደረገችው ንግግር ምንም ሚና የለውም። (በግሌ ይሄ ሙዚቀኞች ላይ የሚጠራ አድማና ይቅርታ ካልጠየቃችሁ የሚል ማስፈራሪያ ውጤት አልባና ዱልዱም ፖለቲካ ሆኖ ይሰማኛል።)
ዋናው ቁምነገር ግን ፌዴሬሽናችን ማንንም አሾልኮ የሚያስገባበት የጓሮ በር የለውም፣ ገቢ ወጭው ሁሉም ፊት ለፊት ባለው በር ነው። ምናልባት ድርጅቱን የከበበው አጥር ባለው ጭፍርግ አሾልኮ በማየት፣ ባለው ቀዳዳ እገባለሁ የሚል ካለ ጭፍርጉ ውስጥ የተሰገሰገው የአጋም እሾክ አያፈናፍንምና፣ መግባት ለፈለገ ሁሉ ፌዴሬሽናችን የተመሰረትንበትን ዓላማ አስከተጋራ ድረስ የፊት በራችን ክፍት ነው።
ለማናቸውም የትኛው የሙዚቃ ባለሞያ ወይንም ዘፋኝ በዝግጅታችን ላይ ይገኝ አይገኝ የሚለውን ውሳኔ የሚወስነው ድርጅቱ ነው ።ውሳኔውም መሰረት የሚያደርገው የግለሰቡ/ቧን ሙያዊ ክህሎትና ለታሰበው ዝግጅት ሁነኛ ነው/ነች የሚል አንጂ፣ የፖለቲካ ወይንም የሃይማኖት አቋማቸው ምንድነው ብሎ መርምሮ አንዳልሆነ፣ በምንም መልኩ ማንም የሙዚቃ ባለሞያ ወይንም ዘፋኝ ላይ ፣ ከፖለቲካ አመለካከታቸው ወይንም ሃይማኖታቸው ተነስቶ አንዳችም ዓድማ አነድማያካሂድና፣ ከሌሎች አድመኞች ጋርም እንደማያብር መታወቅ አለበት። ከዚህ በተረፈ በአመታዊ ዝግጅታችን ማንን እንጋብዝ የሚለውን ትናንትም ሆነ ዛሬና ለወደፊቱም፣ ከፌዴሬሽኑ ውጭ ፣ ሌላ ማንም የውጭ ቡድን የዚህ ውሳኔ አካል አንዳልሆነና፣ ሊሆን አንደማይገባውም ሊሰመርበት ይገባል።
ዘንድሮ የመዝጊያ ምሽት ላይ ለተፈጠረው ችግር፣ ባለቀ ሰዓት በጣልቃ ገብነት አንድ የውጭ ቡድን የማፍያ ዘዴ በመጠቀም፣ እከሌ ከዘፈነ ረብሻ አንፈጥራለን የሚል ያልተገባ አጅ ጥምዘዛ በማካሄዱና፣ ይሄንንም መቋቋም የሚገባቸው አንዳንድ የድርጅቱ ኃላፊዎች ባለመቋቋማቸው የተነሳ ነው የሚል እምነት አለኝ ። እስካሁን ላጣራ አንደቻልኩትም፣ድርጅቱን አላስፈላጊ ንትርክ ውስጥ ከቶ አጣብቂኝ ውስጥ ይከተዋል ከሚል ግላዊ ፍራቻ በመነሳት ብቻ ፣ኃላፊዎቹ ረብሻ እናስነሳለን ባዩን ቡድን ወይዱ ባለማለታቸው የተፈጠረ ችግር ነው። እንግዶች ያላግባብ ተጉላልተውና የመዝጊያው የሙዚቃ ዝግጅት የታዳሚው ትዕግስት ተሟጦ፣ አጅግ ከረፈደ በኋላ እንዲጀመር በመደረጉ ታዳሚዎቻችንን በእጅጉ ያሳዘነ ክስተት የተፈጠረ ከመሆኑም በላይ፣ በውጭ ኃይል ጫና፣ ይዘፍናል ተብሎ በማስታወቂያ የተነገረው ጎሳዬ አንዳይዘፍን መደረጉ፣ ትልቅ ስህተት በመሆኑም ጭምር ፣ለወደፊት እንዲህ ያለ አካሄድ በፍጹም እንደማይታሰብ፣ በመዝጊያው ምሽት የተፈጠረውን ችግር ሁኔታውን በቅጡ አብራርቶ የፌዴሬሽኑ አመራር አጥጋቢ መልስ መስጠት ይጠበቅበታል።
ፌዴሬሽኑ ወጭና ገቢን አስመልክቶ ግልጽነት ያስፈልገዋል ስለተባለው አስተያየት
ፌዴሬሽኑ አሜሪካን ሀገር በሕግ የተቋቋመ፣ ለትርፍ የማይሰራ ድርጅት በመሆኑ፣ በታክስ አዋቂዎች የተዘጋጀ፣ ገቢ ወጭውን በስነሥርዓት አቀነባብሮ አመታዊ ሪፖርቱን ለሚመለከተው የመንግስት ተቋም ከማቅረቡም በላይ፣ ዋና ተጠያቂነቱ ለአባላቱ መሆኑን ስለሚገነዘብ ግልጽ የሆነ አመታዊ የሂሳብ ዘገባ ያቀርባል።ከዚህ ውጭ ስለ ፌዴሬሽኑ ወጪ ገቢ ማወቅ እንፈልጋለን የሚሉ ወገኖች ኢንተርናል ረቨኑ ሰርቪስን በመጠየቅ ሊያገኙት የሚችሉ መብታቸው በመሆኑ ይሄን መብታቸውን ተጠቅመው አስፈላጊውን መረጃ ሊያገኙ ይችላሉ።
የኩባንያዎች ድጋፍን አስመልክቶ
እርግጥ ነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለፌዴሬሽኑ ከሰላሳ ዓመት በላይ ድጋፍ ይሰጥ የነበረ ድርጅት የነበረ ቢሆንም፣ ባለፉት ሁለት አመታት ግን ግልጽ ባልሆነልን ምክንያት አቋርጧል ። ለምን እንደተቋረጠ አጣርተንም አለመግባባቶችም ካሉ አስወግደን ወደፊት ድጋፋቸውን እንድሚለግሱ ተስፋ ማድረግ ይቻላል። ሆኖም የድጋፍ ትንሽ የለውም እንጂ፣ አየር መንገዱ ድጋፉን በለገሰባቸው አመታት ዋነኛው ደጋፊያችን ሆኖ አያውቅምና በዚህ በኩል ዘገባው የተሳሳተ ነው።
ለአስር ዓመት ያህል ጠቀም ያለ የገንዘብ ድጋፍ ያደርግልን የነበረው የሜድሮክ ቡድን እንደነበረና፣ ከሚያደርገው ድጋፍ ተነስቶ አላግባብ ተፅእኖ ለማድረግ መፈለጉን፣ ፌዴሬሽኑ እምቢኝ ስላለ እንደተቋረጠ ይታወቃል። ከዚህ ሌላ ከዚህ ቀደም ዶሾ ዲዛይን፣ ዌስተርን ዩንየን፣ መኒ ግራም፣ ሰንሻይን ኮንስትራክሽን፣ ፍሊንትስቶን ሆምስ የመሳሰሉ ድርጅቶችም የተወሰነ ድጋፍ አድርገውልን የነበረ ሲሆን፣ በኛ በኩል ባለ የትጋትና ክትትል ማነስም ሆነ በነሱ ቸልተኝነት ተቋርጧል።
በዚህ ሁኔታ ነው እንግዲህ የሲያትል አዘጋጅ ኮሚቴ የኡበር ድርጅትን የገንዘብ ድጋፍ ሊያሳካ የቻለውና ፣በተገኘውም ገንዘብ በጣም ውድ የሆነው የሆቴል ወጭ በክለቦች ላይ የሚፈጥረውን ተጨማሪ እዳ ለመቀነስ ፌዴሬሽኑ እንዲጠቀምበት የረዳው ።
በዓመታዊ ዝግጅት ላይ የሚሳተፉ ክለቦች አጠቃላይ ወጭ ከ$750 ሺህ ብር በላይ ስለሆነና ክለቦችም ላይ ጫናው ስለሚበዛ ችግሩን ለመቅረፍ ፣ ከኩባንያዎች የሚገኝ ድጋፍን ለማጠናከርና የየክለቦችን ወጭ ለመቀነስ እንዲረዳ በማሰብ ፌዴሬሽኑ አንድ ኮሚቴ አዋቅሮ ተስፋ የሚሰጡ ፍንጮች ታይተዋል። በዚህም ረገድ ከኡበር ጋር ዘንድሮ የተድረገው ስምምነት ሌሎች በሮችን ይከፍታል የሚል ተስፋን ይዘናል ።
ከዚህ ሌላ ሌሎች ብዙ በፕሮግራሙ የተነሱ ጉዳዮች ከፌዴሬሽኑ ጋር ምንም አይነት ቀጥተኛ ግንኙነት የሌላቸውና፣ ከፕሮግራሙ አዘጋጆች ጋር ተመሳሳይ ዓላማ አለን ስለሚሉ ወገኖች በመሆኑ አስተያየት መስጠት አስፈላጊ አይደለም።
በመጨረሻም አዘጋጆቹ ስለራሳቸውም ሆነ ስለሚወክሉት ተቋም ከሌሎች የሚድያ ተቋማት የገዘፈ ተክለ ሰውነት አለን የሚል ግምት ቢኖራቸውም ፌዴሬሽኑ ግን ትልቅ ትንሽ ሳይል፣ ዘሃበሻንም ሆነ ኢትዮ– ሚዲያን፣ አባይ ሚዲያንም ሆነ ኢትዮ–ሚዲያ ፎረምን ፣ ኢቢኤስንም ሆነ ኢሳትን አንድሚዲያ ተቋምነታቸው በእኩል እንድሚያቸውና አስፈላጊውን ትብብር አንደሚያደርግ ማወቅ ይኖርባቸውል።
https://youtu.be/Day8AfDD8Fs