ሰማያዊ ፓርቲ ‹የዜጎች ቃል ኪዳን ሰነድ›ን ለውይይት ሊያቀርብ ነው

(ነገረ ኢትዮጵያ) አዲስ አበባ፡- ሰማያዊ ፓርቲ (ሰማያዊ) እሁድ ሰኔ 29/2006 ዓ.ም ባደረገው አስቸኳይ የብሔራዊ ምክር ቤት ስብሰባ በኮሚቴ ውይይት ሲደረግበት የነበረውን የዜጎች የቃል ኪዳን ሰነድ ለምክር ቤቱ በማቅረብ በሰነዱ ይዘትና አፈጻጸም ላይ ውይይት ካደረገ በኋላ በሚቀጥሉት ሳምንታት ውስጥ ለህዝብ ይፋ እንዲሆን ስምምነት ላይ መድረሱን የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

ሰነዱ ለውይይት በሚበቃ መልኩና ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በሚያስማማ መልኩ በኮሚቴ ታይቶ ስምምነት የተደረሰበት መሆኑን የገለጹት የህዝብ ግንኙነቱ በቅርብ ቀን ህዝብ፣ ምሁራን፣ የህግ ባለሙያዎች፣ ጋዜጠኞችና ሌሎችም ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሁሉ ተወያይተው በህገ-መሰረት እንዲጠቀሙበት እንዲያስችል እቅድ መያዙን ገልጸዋል፡፡ አቶ ዮናታን ‹‹የቃል ኪዳን መሰረቱ የተዘጋጀበት ዋናው ምክንያት ባለፉት 50ና 60 አመታት ህገ-መንግስት ተረቀቀ ቢባልም የህዝብ ሀሳብ ያልተካተተበትና የህዝብን ጥቅም መሰረት አድርገው ያልወጡ መሆናቸውን ተከትሎ ይህን ክፍተት ለመሙላት ነው፡፡›› ሲሉ የሰነዱን አላማ ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም የቃል ኪዳን ሰነዱ በርካታ አካላት የሚወያዩበት በመሆኑ የሰማያዊ ፓርቲ ብቻ እንደማይሆን የገለጹት የህዝብ ግንኙነቱ ‹‹ማንኛውም አካል ህግ ለማውጣት መሰረት እንዲያደርገው ለውይይት የምናቀርበው ሰነድ ነው ብለዋል፡፡›› ሰማያዊ ፓርቲ ስልጣን ቢይዝ ህገ-መንግስትነት ይጠቀመዋል ወይ ብለን የጠየቅናቸው ኃላፊው ‹‹የቃል ኪዳን ሰነዱን ህገ-መንግስት አናደርገውም፡፡ ነገር ግን ህገ-መንግስቱን ጨምሮ ሁሉም ህጎች ሲሻሻሉም ሆነ ሲቀየሩ የቃል ኪዳን ሰነዱ መነሻ ይሆናል›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

ምንጭ ነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ

ተጨማሪ ያንብቡ:  "በአማራ ሕዝብ ላይ በየቦታው እየተፈፀመ ላለው የዘር ማጥፉት ወንጀል ሙሉ ኃላፊነቱን መንግስት ይወስዳል" የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን

1 Comment

Comments are closed.

Share