June 28, 2014
7 mins read

Sport: ናይኪ Vs አዲዳስ – ሌላኛው የብራዚሉ ዓለም ዋንጫ ጦርነት

brazil Nike

ፊፋ ለ64ቱ ጨዋታ 33 የመሐል ዳኞችና 57 ረዳት ዳኞችን መርጦ አዘጋጅቷል። ከ33ቱ የመሐል ዳኞች አፍሪካ፣ እስያ፣ የሰሜንና ደቡብ አሜሪካ ካሪቢያን ዞን አምስት- አምስት ዳኞችን ሲያስመርጡ ላቲን አሜሪካ 6፣ ኦሽኒያ በ 2፣ አውሮፓ በ10 ዳኞች ተወክለዋል።

በዚህ ሻምፒዮና ታዋቂዎቹ አርቢትሮች የሆኑት እንግሊዛዊው ሃዋርድ ዌብ፣ ጣሊያናዊው ኒኮላ ሪዞሊ፣ አርጀንቲናው ኔስተር ፒታናና ብራዚላዊው ሳንድሮ ሪቺ መካተታቸው ታውቋል። በዚህ ሻምፒዮና ላይ የጐል መስመር ቴክኖሎጂ ለመጀመሪያ ጊዜ ጥቅም ላይ እንዲውል ተደርጓል። ውሳኔዎች ሁሉ ፍትሃዊና ትክክለኛ እንዲሆኑ የጐል መስመር ቴክኖሎጂው ከፍተኛ ጥቅም አለው ሲሉ ሮልፍ ዲትሪች የተሰኙ የጀርመን ካምፓኒ ባለሙያ ተናግረዋል። የጐል ኮንትሮል 14 ከፍተኛ ፍጥነት ባላቸው ካሜራዎች የሚመራ ሲሆን፤ 7ቱ በቀጥታ በጐሎቹ ላይ የሚያነጣጥሩ ይሆናል። በቴክኖሎጂው ኳሷ መስመሩ ላይ ካረፈች ለመሐል ዳኛው ምልክት የምትሰጥ ሲሆን፤ የዳኛው ሰዓት የመንዘርና መብራት ምልክት የሚያሳይ ይሆናል። ይህ ሁሉ የሚሆነው በ1 ሰከንድ ውስጥ በመሆኑ የጨዋታው ሂደት ካለመቋረጡም በላይ የእግርኳስን ጣዕም እንደማያበላሽ ተነግሮለታል። ከዚህ በተጨማሪ የብራዚል የአለም ዋንጫ አዘጋጅ ኮሚቴ ለ12 ስታዲየሞች እደሳና ግንባታ 3.5 ቢሊየን ዶላር ወጪ ያደረገ ሲሆን፤ 600 ሚሊየን ዶላር ብቻ ለማራካኛ ስታዲየም ዕደሳ ወጪ ተደርጓል። 16 ቢሊየን ዶላር አለም ዋንጫውን ለማዘጋጀት የብራዚል መንግስት ያወጣው ወጪ ሲሆን፤ በርካታ ብራዚላውያንን ይህን በይፋ ተቃውመዋል። ለ64ቱ ጨዋታዎች 3.3 ሚሊየን የመግቢያ ቲኬቶች መዘጋጀታቸውን የገለፀው ፊፋ ደግሞ ውድድሩ በሰላም እንደሚጠናቀቅ ያለውን ተስፋ ገልጿል።

ከዚህም በተጨማሪ አወዛጋቢው ዦዜ ሞውሪንሆ በበኩላቸው ከየምድቡ የሚያልፉትን ሁለት- ሁለት ሐገሮች ገምተዋል። በዚህ መሰረት ከምድብ 1 ብራዚልና ሜክሲኮ፣ ከምድብ 2 ስፔንና ኔዘርላንድ፣ ከምድብ 3 አይቬሪኮስትና ግሪክ፣ ከምድብ 4 ጣሊያንና እንግሊዝ፣ ከምድብ 5 ፈረንሳይና ስዊዘርላንድ፣ ከምድብ 6 አርጀንቲናና ናይጄሪያ፣ ከምድብ 7 ጀርመንና ፖርቱጋል፣ ከምድብ 8 ሩሲያና ቤልጂየምን ወደ ቀጣዩ ዙር ያልፋሉ ሲሉ ግምታቸውን ሰንዝረዋል።

3.2 ቢሊየን ህዝብ በቴሌቪዥን መስኮት የሚመለከተውና 37 ሚሊዮን ፓውንድ ለአሸናፊው የተመደበበት አለምአቀፋዊው የእግርኳስ ድግስ የአለም ዋንጫ በብራዚል ሲጀመር፤ በመክፈቻው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ባንኪሙን ፣ የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን እና መራሄ-መንግስት አንጌላ ሜርክል ጨምሮ ከ11 በላይ የሀገራት መሪዎች ተገኝተዋል። ሻምፒዮናው እስከ ሐምሌ 6/2006 በድምቀትና በጉጉት ሲካሄድ ይሰነብታል። በሌላ በኩል ከ32ቱ ሐገራት በጣም ውድ ቡድን የተባሉ 6 ሐገራት ታውቀዋል። በዚህም መሠረት ስፔን 916 ሚሊዮን ዶላር በሚያወጡ ኮከቦቿ ቀዳሚ ሆናለች። ጀርመን በ828 ሚሊየን ዶላር፣ ብራዚል በ689 ሚሊየን ዶላር፣ ፈረንሳይ በ607 ሚሊየን ዶላር፣ አርጀንቲና በ577 ሚሊየን ዶላር፣ ቤልጂየም በ513 ሚሊየን ዶላር በሚያወጡ ስብስባቸው ከ2-6 ያለውን ደረጃ ይዘዋል።

የናይኪና አዲዳስ የአለም ዋንጫ ጦርነት

በሁለቱ ካምፓኒዎች መሐል የሚደረገው ፉክክር የአሜሪካና ጀርመን ቀዝቃዛ ጦርነት ተብሏል። የጀርመን ትጥቅ አምራች ድርጅት አዲዳስ በዘንድሮው አመት ያገኘው 2.7 ቢሊየን ዶላር ገቢ ከአምናው የአሜሪካን ናይኪ ካምፓኒ 1.9 ቢሊየን ዶላር ገቢ አንፃር ከፍተኛ ልዩነት የፈጠረ ነው ተብሏል።
ናይኪ ለአለም ዋንጫው 25 ቢሊየን ዶላር ወጪ ማድረጉ ታውቋል። ክርስቲያኖ ሮናልዶ፣ ኔይማር፣ ዌይን ሩኒና ጄራርድ ፒኬ የአዲዳስን ትጥቁን ለብሰው በብራዚሉ የአለም ዋንጫ የሚገኙ ሲሆን፤ ናይኪም ጀርመን፣ ስፔን፣ አርጀንቲናና ኮሎምቢያ ጋር ባለው ስምምነት በአለም ዋንጫው ትጥቁን እያስተዋወቀ ይገኛል።

ሁለቱም ካምፓኒዎች በገበያው ላይ ያላቸውን የበላይነት በማስፋት የየሐገራቸው መኩሪያ ለመሆን ከፍተኛ ሥራ እየሰሩ ነው። በተለይ ናይኪ ካምፓኒ በሊዮኔል ሜሲ ስም ጫማ አሰርቶ ለገበያ በማቅረብ አዲዳስ ላይ ብልጫውን ለመውሰድ እየጣረ ነው። አዲዳስም አርፎ አልተቀመጠም። ከ1970 ጀምሮ ከፊፋ ጋር የነበረውን ውል በማደስ ለቀጣዮቹ 60 ዓመታት የፊፋ ስፖንሰር ለመሆን አድሷል። አዲዳስ ከብራዚሉ የአለም ዋንጫ ጋር በተያያዘ 2.6 ቢሊየን ዶላር ገቢ ለማግኘት እንደሚችል እየተነገረለት ይገኛል። ምንጩ ከአሜሪካ የሆነው ናይኪና በጀርመን ውልደቱ የሚጠራው አዲዳስ የሐገራቸውን ስም ከፍ ለማድረግ በዓለም ዋንጫው ላይ እያደረጉ ያለው ትግል 20ኛው የዓለም ዋንጫው ሌላ አጓጊ ክስተት ተደርጐ ተወስዷል።

* በዘ-ሐበሻ ጋዜጣ ቁጥር 64 ላይ ታትሞ የወጣ

students 1
Previous Story

በአ.አ ዩኒቨርሲቲ 52 ተማሪዎች በ”ዲሲፕሊን” ሰበብ ፖለቲካዊ ክስ ተመሰረተባቸው (ዝርዝራቸውን ይዘናል)

Next Story

ከምእራብ እና ምስራቅ ወለጋ የተፈናቀሉ የአማራ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ፍትህ አሁንም ድረስ አለማግኘታቸውን ገለጹ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop