አሥሩ ዋንጫዎች:- አሥሮቹ ጀግኖችና አሥሩ ዓመታት በኦልድትራፎርድ – ክፍል 2

ከይርጋ አበበ
በትናንቱ የክፍል 1 ዘገባ የእንግሊዙ ታላቅ ክለብ ባለፉት 10 ዓመታት ውስጥ ከውጤታማው አሠልጣኝ ጋር ያጣጣማቸውን 10 ዓመታት ስንመለከት ቡድኑ ካስፈረማቸው ተጫዋቾች መካከል ነጥረው የወጡትን አሥር ተጫዋቾች ለይተን እያየን አምስተኛው ውጤታማ ተጫዋች ላይ ስንደርስ ነበር ቀሪዎቹን ዛሬ ልናይ የተለያየ ነው፡፡ ዛሬ ከቆምንበት ስንቀጥል እንዲህ ሆኖ እናገኘዋለን።
6. ማይክል ካሪክ
የማንቸስተር ዩናይትድ ደጋፊዎች ብዙም ያላጨበጨቡለትና ያልዘመሩለት የመሐል ሜዳው ሞተር እንደ ሥራው ተገቢውን ከበሬታ እንዳላገኘ ይነገርለታል። ልክ እንደቀድሞው ብራዚላዊ መድፈኛ ጂልቤርቶ ሲልቫ ሁሉ ማይክል ካሪካም ከካሜራ የተደበቁ ድንቅ ሥራዎችን በትጋት ሲከውን ነው የሚያመሸው። አየርላንዳዊው ሮይኪን ትቶት የሄደውን ቦታ ለመድፈን የሌሎች ክለቦችን በር ያንኳኩት ሰር አሌክስ ፈርጉሠን ማረፊያቸው የሰሜን ለንደኑ ቶተንሃም ሆትስፐርስ የመሐል ሜዳ አንቀሳቃሽ ማይክል ካሪክ ሆነ። 18 ነጥብ6 ሚሊዮን ፓውንድ የግሌዘር ቤተሰቦችን ያስከፈለው ወጣት የማንቸስተሩን ክለብ የመሐል ሜዳ ለማስጠበቅ ብዙም ፈተና አልገጠመውም ነበር። 16 ቁጥር ያረፈበት ቀይ ማለያ ለብሶ ሜዳ የሚገባው እንግሊዛዊ ማንቸስተር ይናይትድ ካገኛቸው ስኬቶች ጀርባ አሻራው ከፍተኛ ነበር። ለ308 ጊዜ ቀዩን ማለያ ለብሶ የተጫወተው ካሪክ 20 ግቦችን ሲያስቆጥር የጣሊያኑን ዋና ከተማ ክለብ ሮማን 7ለ1 ሲረታ ያስቆጠረው ግብ ምንጊዜም «በደጋፊዎች ልብ ውስጥ አይጠፋም» በላንክሻየሩ ክለብ ያሳየው ምርጥ አቋም ስቴቨን ጄራርድና ፍራንክ ላምፓርድ በተቆጣጠሩት የሦስት አናብስቶቹን ማሊያ 27 ጊዜ እንዲለብስ አስችሎታል።
7. ሮበን ቫንፔርሲ
አርሴናልን ለብስጭትና ለንዴት ጥሎ በ24 ሚሊዮን ፓውንድ ከለንደን ወደ ማንቸስተር የተጓዘው የ29 ዓመቱ ሆላንዳዊ ማንቸስተር ዩናይትድ የ2012/13 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዋንጫን ሲያነሳ የአንበሳውን ድርሻ የተወጣው ይኸው ባለግራ እግሩ ሆላንዳዊ ነው። በመጀመሪያ ዓመት የኦልድ ትራፎርድ ቆይታው እስካሁን ድረስ ብቻ 30 ግቦችን ሲያስቆጥር ከ10 በላይ ኳሶችን ደግሞ ለጓደኞቹ አስተካክሎ በማቀበል ግብ ጨራሽ ብቻ ሳይሆን ግብ ፈጣሪነቱንም በሰር አሌክስ ፈርጉሰን ቡድን ውስጥ አሳይቷል። የእንግሊዝን ፕሪሚየር ሊግ ለ20ኛ ጊዜ ማንቸስተር ዩናይትድ ሲወስድ 20 ቁጥር ለባሹ ሆላንዳዊ የፈጸመው ተግባር በክለቡ ደጋፊዎችና የስፖርት ተንታኞች ከ10 ዓመቱ የኦልድ ትራፎርድ ምርጦች አንዱ እንደሆነ አስችሎታል።
8. ሀቪየር ሄርናንዴዝ ቺቻሪቶ
ሜክሲኳዊው ወጣት በ21 ዓመት ዕድሜው በደቡብ አፍሪካ የዓለም ዋንጫ ያሳየውን ብቃት ብዙዎች ድንቅ ብለውታል። ቺቻሪቶ ከዓለም ዋንጫው በፊት ግን ስኮትላንዳዊው የማንቸስተር አለቃ ልጁን በደንብ ያውቁት ነበር። ገና በሜክሲኮው ሲ. ዲ ጓዳላጅራ ክለብ ሲጫወት ቀልባቸውን የሠረቀው ትንሹ አተር ወደ ኦልድ ትራፎርድ እንዲመጣላቸው ለክለባቸው አመራር ትዕዛዝ አስተላለፉ፡፡ በፈርጊ ላይ እምነት ያለው የክለቡ አመራር ባልተገለጸ የዝውውር ሂሳብ ወደ ክለባቸው አመጡት። የመጀመሪያ የነጥብ ጨዋታውን በዊብሌይ ቸልሲን 3ለ1 አሸንፈው የኮሚዩኒቲ ሸልድ ዋንጫ ሲያነሱ ተቀይሮ የገባው 14 ቁጥሩ በፒተርረቼክ መረብ ላይ ኳስ ማሳረፍ ጀመረ። የራሱን ፊት ገጭታ መረብ ላይ ባረፈች ኳስ ከግብ ጋር መተዋወቅ የጀመረ ሲሆን በመጀመሪያ ዓመት ቆይታው 13 እጅግ ወሳኝ የፕሪሚየር ሊግ ግቦችን ለቀያይ ሠይጣኖቹ ማስቆጠር ቻለ፡፡ በ26 ጨዋታዎች 13 የሊግ ግቦችን ያስቆጠረላቸውን ሜክሲኳዊ ለማድነቅ ቃላት የሚቸግራቸው ፈርጊ የ2010/11 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮን እንዲሆኑ ከኮከቡ ዋይኒ ሩኒ ያልተናነሰ አስተዋጽኦ አበርክቷል። እግር ኳስ ተጫዋች ከሆነ ቤተሰብ የተገኘው ይህ ተጫዋች በሮቢን ቫንፐርሲ መፈረምና ዳኒ ዋልቤክ መጎልበት የቋሚ ተሰላፊነት ቦታውን እያጣ ቢመጣም ዕድሉን አግኝቶ በሚሰለፍባቸው ጨዋታዎች ሁሉ የቀድሞውን ምርጥ ግልጋሎት ከመስጠት አልታቀበም።
በቀጣዩ የውድድር ዓመት ኮከባቸውን ሮዳሜል ፋልኮኦን እንደሚያጡ እርግጠኛ የሆኑት አትሌቲኮ ማድሪዶች ቺቻሪቶን ከማንቸስተር ለመግዛት ተደጋጋሚ ጥያቄዎችን እያቀረቡ ይገኛሉ። የፍሎሬንቲኖ ፔሬዙ ሪያል ማድሪድም ቢሆን በጎንዛሎ ሂጉየንና ካሪም ቤንዜማ ግብ የማግባት ችሎታ ባለመደሰታቸው ሜክሲኳዊውን የ24 ዓመት ወጣት ወደ ቤርናባው ለማስኮብለል የፈርጊን ፈቃድ በመጠባበቅላይ ናቸው። ማሬንጌዎቹ ቤካምንና ሮናልዶን እንደወሰዱ ሁሉ ትንሹን አተር ከኦልድ ትራፎርድ ማስኮብለል ይችሉ እንደሆነ የምናየው ይሆናል።
ቺቻሪቶ ግን በእስካሁኑ የክለቡ ቆይታው ከክለቡ ምርጦች ውስጥ ስሙን ለማስፈር ችሏል።
9. ካርሎስ አልቤርቶ ማርቲኔዝ ቴቬዝ
ከቦካ ጁኒየርስ ወደ ብራዚሉ ኮረንቲያስ ዝውውር ሲያደርግ በአሳዳጊ ክለቡ ደጋፊዎች «ገንዘብ አሳዳጅ» ተብሎ የተሰደበው «ቴብዝ» በእንግሊዝ ቆይታውም ከዚህ የተለየ አልጠበቀውም፡፡ ገና በኮረንቲያስ በነበረበት ጊዜ የቀያይ ሰይጣኖቹን ማሊያ ለብሶ ጋዜጣዊ መግለጫ መስጠት ሲጀምር ወደ ኦልድ ትራፎርድ የሚወስደውን መንገድ ማመቻቸት ጀመረ። በአርሴናሉ አሠልጣኝ አርሰን ቬንገር በጥብቅ ሲፈለግ አሌክስ ፈርጉሰን ግን ከተጫዋቹ የኢኮኖሚ ባለመብት ኢራናዊው ኪያ ብራብችያን ላይ በሁለት ዓመት ውሰት 25 ሚሊዮን ፓውንድ ከፍለው 32 ቁጥር ማሊያን አልብሰው የክለባቸው ተጫዋች አደረጉት። ይበልጥ በታጋይነቱ እና ሜዳውን ሙሉ አካሎ መሮጡ መታወቂያዎቹ ሲሆኑ በኦልድ ትራፎርድ ቆይታው የደጋፊዎቹን ልብ ማሸፈት ችሎ ነበር። ለሁለት ዓመታት ብቻ በቀዮቹ ቤት የቆየው ደቡብ አሜሪካዊ ለ99 ጊዜ የማንቸስተርን ማሊያ ለብሶ ወደ ሜዳ ገብቷል። በ99ኙ ጨዋታዎቹ 34 ኳሶችን መረብ ውስጥ የዶለ ሲሆን በ2008ቱ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታ የፈጸመው ተጋድሎ የላንክሽየሩ ክለብ ወደ ሞስኮ ያደረገውን ጉዞ የሚያሳምሩ 5 ግቦችን ለክለቡ አስቆጥሯል።
በዌስትሀም ዩናይትድ ደጋፊዎች በእጅጉ የሚፈቀረው አርጀንቲናዊ በ2008 የውድድር ዘመን ማንቸስተር ዩናይትድ አፕተን ፓርክ ላይ የምሥራቅ ለንደኑን ክለብ ሲገጥም የዌስትሀም ደጋፊዎች « አንድ ካርሎስ ቴቬዝ ብቻ ነው» እያሉ ነበር የዘመሩለት። በ2006/07 የውድድር ዘመን ከመውረድ በታደጋቸው ደቡብ አሜሪካዊ ላይ የ2008/09 የውድድር ዘመን መጠናቀቁን ተከትሎ ከማንቸስተር ዩናይትድ ወደ ከተማ ተቀናቃኙ ማንቸስተር ሲቲ ዝውውር ማድረጉ በሻፒዮናዎቹ ዩናይትድ ደጋፊዎች ጥርስ ነከሱበት። ከአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ታሪካዊ ተቀናቃኝ ወደ ብራዚል ዝውውር ሲያደርግ በሀገሩ ጥላቻን ማትረፍ ሳይበቃው በእንግሊዝ የፈፀመው ዝውውርም በቀድሞ ክለቡ ደጋፊዎች እና የቡድን አጋሮቹ (ጋሪ ኔቭል በጣም ይጠላው ነበር) እንደ ከሀዲ አስቆጥሮታል። ቢሆንም ግን በአልድትራፎርድ በቆየባቸው 2ዓመታት የፈጸመው ሥራ ከክለቡ ምርጥ የ10 ዓመት ግዥዎች ዝርዝር ውስጥ እንዲካተት አድርጎታል።
10. ዲሚታር ኢቫኖቭ ቤርባቶቭ
የእንግሊዝ ክለቦችን የዝውውር ሪከርድ በሰበረ ዋጋ ከፈርናንዶ ቶሬዝና ሮቢንሆ ሪከርዱ በቤርባ እጅ ነበር ከሰሜን ለንደን ወደ ላንክሻየር ሲቀላቀል ብዙ ተጠብቆ ነበር። 30 ነጥብ75 ሚሊዮን ፓውንድ ከግሌዘር ቤተሰቦች ካዝና ወደ ቶተንሃም ሆትስፐር አካውንት ያዘዋወረው የቡልጋሪያ 7 ጊዜ ኮከብ ተጫዋችና አምበል በቀዮቹ ቤት በነበረው ቆይታ 149 ጊዜ ቀዩን ማሊያ ለብሶ ሜዳ ውስጥ ታይቷል። በ149 ጨዋታዎች 54 ጊዜ ኳስና መረብን ያገናኘ ሲሆን በ2010 ኅዳር ወር ላይ በብላክበርን ሮቨርሱ ፖል ሮቢንሰን መረብ ውስጥ የጨመራቸው አምስት ግቦች ብቸኛው ተጫዋች እንዲሆን አስችለውታል። በአንድ ጨዋታ አምስት ግብ ያስቆጠረ።
እንደ ክለብ ጓደኞቹ ታጋይነት የማይታይበት መሆኑ ስሜት የሌለው እያሉ ቢተቹትም አንድ ጊዜ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ኮከብ ግብ አስቆጣሪ ዘውድን መድፋት ችሏል። የቀድሞው ሲ.ኤስ.ኬ ሶፊያ ተጫዋች ለሀገሩ 77ጨዋታዎችን አድርጎ 48 ግቦችን ያስቆጠረ ሲሆን፣ በአሌክስ ፈርጉሰን ቡድን ውስጥ በነበረው የሦስት ዓመታት ቆይታ እንደ እነ ቺቻሪቶ እና ቴቪዝ ባይሆንም ጥሩ ሊባል የሚችል የውድድር ጊዜያትን አሳልፏል። እነዚህ ሥራዎቹ ደግሞ እንደ ሉዊስናኒ፣ አንቶኒዮ ቫሌንሽያ፣ ሉይስ ሳሃ፣ ኦውን ሃርግሬቭስ፣ ራፋኤል ዳሲልቫ እና ደቡብ ኮሪያዊው ፓርክጄ ሱንግ የተሻለ ደረጃ ሊያሰጠው ችሏል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በሽብርተኝነት የተከሰሱት የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ወደ ማዕከላዊ ተዛወሩ
Share