በሃገሪቱ ላለፉት 30 አመታት ሲንተከተክ የቆየው ጠባብ ዘውጌኝነት በተለይም ባለፉት 6 እና 7 አመታት ገንፍሎ በመውጣት ያልነካካው እና ያላዳረሰው የህብረተሰብ እና ተቋማት ክፍል የለም :: በተለይም የህዝቦች መተሳሰሪያ የሆኑት ማህበራዊ ድር እና እሴቶች( social fabrics and values) አንድ ባንድ ኢላማ ተደርገው እንዲበተኑ ሆኗል:: ቤተክርስቲያን የዚህ ማህበራዊ ድር ዋና ፈትል መሆኗ ደግሞ እንደ አሁኑ ገኖ እና ገዝፎ አይምጣ እንጂ ያለፈውን ሩብ ክፍለዘመን የዘርፈ ብዙ ጥቃቶች ኢላማ እድትሆን አድርጏታል::
ላለፉት 2 ወይ 3 ሳምንታት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክርስቲያን ስታደርግ የሰነበተችው
ትንቅንቅ ህልውናዋን የተፈታተነ ምዕመናንን ማቅ ያስለበሰ ከ37 በላይ የሚሆኑትን በጥይት እና በደቦ የዱላ ቅጥቀጣ ህይወታቸውን የቀጠፈ በሺዎች የሚቆጠሩትን ወደ ጅምላ እስር ያስጋዘ ቀሳውስቱን ይስደበደበ ያዋረደ እ ና ለእስር እና እንግልት የዳረገ ገና ያልተቋጨ እና ቀጣይ ፈተና እና ስቃይን የጋረጠ ክስተት ነበር::
ከላይ በግርድፉ ሲታይ ህዝብን በአፍ መፍቻ “ቋንቋው ” ማገልገል ሲጀመር ሃይማኖታዊ ግዴታ አለፍ ሲልም ከመብት መሰረታዊ ጥያቄነቱ ባሻገር ለአንድ እምነት( ሃይማኖት) ቁልፍ የመስፋፊያ ወይም ማዳረሻ መንገድ መሆኑ ፈፅሞ አሌ የሚባል አይደለም:: ላለፉት 30 አመታት ቤ/ክርስቲያኒቱ ከበቂ በላይ ሊባል ባይችል እንኳ የምትደርሳቸውን ምዕምናን ቋንቋ ና ባህል ያማከለ አገልግሎት ለማዳረስ አመርቂ ጥረት እና ውጤት የታየባቸው እንቅስቃሴዎች ማደረጏ የማይታበል ሃቅ ነው::
ይሁን እንጂ እነ አካለወልድ አሁን ይዘውት የተነሱትን ጥያቄ ሀቀኝነት ለመበየን ተከታዮቹን አንኳር ነጥቦች መመርመር ለድምዳሜያችን አመክንዮ ጥሩ ግብዓት ይሆናል::
የነ አካለወልድ ጥያቄ እና አቋም ሐይማኖታዊ እና ፍትሃዊ?
እነ አካለወልድ ይዘው የተነሱትን አቋም ከግብ ለማድረስ የነማንን እርዳታ ሽተዋል ? አግኝተዋል? ከሰሞኑ የተከሰቱ ሁነቶችን ላየ እነዚህ ሰዎች ከጀርባቸው ያለው ፖለቲካዊ አጀንዳ ና ሃይል ከውሃ ኩልል ብሎ ታይቷል:: ጥቂት ማሳያዎች :-
ስሞኑን ድምፁን ያጠፋው የኪሊማንጃሮው “የሰላም” ተጏዥ ባንድወቅት ባካሄደው የባህር ማዶ ስብሰባ ” 3 ትም 4ትም ብትሆኑ እንኳን የራሳችሁን መስጂድ የራሳችሁን ቤ/ክ ክፈቱ(መስርቱ ) እያለ ሲደሰኩር ተደምጦ ነበር:: በዘውጌያዊው ንፍቀ ክበብ ካለው ተደማጭነት አንፃር ይህ እንደ አቋም (policy) ተወስዷል ብሎ መገመት ይቻላል::
በግምት የዛሬ 3 ዓመት ግድም ተመሳሳይ ጥያቄ በሲኖዶሱ ተነስቶ የነበረ ሲሆን ያኔም ሽፋኑ “ቋንቋ” ይሁን እንጂ ግለሰቦቹ በሚሰጡት መግለጫ እና ማብራሪያ ፍላጎታቸው የቤተክህነት ስልጣን እና የዘውግ መዋቅር ያለው አደረጃጀት እንደሚሹ መሸሸግ አልቻሉም ነበር:: ይሄው ግብግብ በወቅቱ የጠያቂዎቹ አስተባባሪ ከሆኑት አንዱ በሲኖዶሱ ከፍ ያለ ሹመት በማግኘታቸው ለጊዜውም ቢሆን ሊዳፈን ችሏል::
በሃገሪቱ እየተቀረፁ እና እየተተገበሩ ያሉ ፖሊሲዎች እና እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎች የሚያሳዩት ኢትዮጵያ የምትባል ሃገር እንደሃገር መቀጠሏ ነገር እጅግ አጠራጣሪ እየሆነ የታያቸው ዘሬ ወደሚሉት በመንፏቀቅ ይወክለኛል ለሚሉት ቡድን አገር ምስረታ በውለታ መዝገብ መስፈርን እንደ አንድ እድል(opportunity) መጠቀምን መርጠዋል :: እነ አካለወልድ ነፃይቱ ኦሮሚያ መመስረቷ እንደማይቀር አምነዋል- እናም በነገይቱ ነፃ ኦሮሚያ የታሪክ መዝገብ ” የኦሮሚያ ኦርቶዶክስ ሲኖዶስን የመሰረቱ” ተብለው መጠራት ይህንኑ ተከትሎ የሚመጣው ዝና ክብር ስልጣን እና ምቾት ስጋን የሚፈትን ነው::
የአካለወልድ ቡድንን የሚያደራጀው የሚደግፈውና የሚዘውረው የመንግስት እና ሌሎች የፖለቲከኞች ቡድን ካለፉት አመታት ሁኔታ በግልፅ የተረዱት የሚፈልጉትን ፖለቲካዊ አጀንዳ የአንድ ዘውግ ስም እስከሰጡት ድረስ ይህን አጀንዳቸውን እየደበደበ እየገደለ እና እየዘረፈ የሚያስፈፅምላቸው ስፍር ቁጥር የሌለው ወጣት እንዳለ ነው:: ስለዚህ ያለምንም ሀፈረት እና ይሉኝታ የፈለጉትን የማፍረስ እና የመበተን እርምጃ በትእቢት እና ድንፋታ ጭምር በአደባባይ እየተሳደቡ እና እየፎከሩ በማስፈፀም ላይ ይገኛሉ:: ስራውን ይበልጥ ቀላል የሚያደርገው ደግሞ ” አማራ” እና ” አማርኛ” የሚሉትን ቃላት ጣል ማድረግ ነው – በ ታሪካዊ በቀል ተተብትቦ ያደገው ህልቆ መሳፍርት ወጣት ሳያመነታ በደቂቃዎች እንደሚነሳ ከዚህ ቀደም በደቦ ፍርድ ( mob justice) የተፈፀሙ ግድያዎች ስደቶች እና የንብረት ውድመቶች ቋሚ ማሳያዎች ናቸው:: ለአሁኑ ክስተት ደግሞ ሻሸመኔ እና የትዊተሩ “ኦርቶ- ማራ” ትርክት ዘመቻዎች አብነት ናቸው::
ሌላው ከላይ ከተነሳው ነጥብ ጋር ተያያዥነት ያለው ክስተት እነአካለ ወልድን የሚዘውረው ቡድን የነዚህን ሰዎች ጥያቄ ዘውጋዊ መልክ እስካስዚያዘው ድረስ ምንም ጥያቄ እንደማይነሳበት እጅግ በመተማመኑ ለ”ጵጵስና” ያጫቸውን ግለሰቦች ግለታሪክ(profile) እንኳ መለስ ብሎ ለማጥናት ባለመጨነቁ ” በርጫም ጨብሲም ሸሌም አለ” የሚሉ ዱርዬዎችን ጳጳስ አድርጎ መሾሙን ታዝበናል::
የጳጳሳት ሹመት ምዕመኑን በ”ቋንቋው” የማገልገል ጥያቄን ይመልሳል? በየአጥቢያው እና አድባራቱ ምዕመኑን የሚገለግሉት ካህናት ቀሳውስት እና ዲያቆናት ወይስ ጳጳሳት? አንድ ጳጳስ በስሩ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን በአመት ምን ያህል ግዜ ተገኝቶ ያገለግላል?
እንደየአካባቢው ቋንቋ ቀሳውስትን ዲያቆናትን እና መምህራንን የሚያሰለጥኑ መንፈሳዊ ኮሌጆች መስፋፋት ወይስ የጵጵስና ሹመት እና የክልል ሲኖዶስ መመስረት ቀዳሚ አጀንዳ መሆን የነበረበት?
የመላውን የቤተክርስቲያኒቱ አባላት ድጋፍ እና ይሁንታ ከመሻት ይልቅ የራሳቸው ዘውግ አባል የሆኑቱን ብቻ( ግንየእምነቱ ተከታይ ያልሆኑትን ጭምር ) ከጎናቸው ማሰለፉን ለምን መረጡ? ጵጵስና እና አባትነታቸው ለራሳቸው ብሄር አባላት ብቻ? ልንታደጋት ነው ከሚሏት ቤ/ ክ መሰረታዊ አስተምህሮ ጋር ይህ እርምጃቸው ይጣጣማል?
ተረማምደውበት የገቡት ደምና ሬሳ በእረኝነት ሊያግዷቸው ( ሊጠብቋቸው) የሚገባ የክርስቲያን ነብሳት አይደሉምን? ለጠፉት ነብሳት ጥቂት እንኳን አዘኔታ ( empathy) ማሳየት ለምን ተሳናቸው?
( በክፍል 2 እመለሳለሁ)