ከሞት የማይሻል ዝምታ

በጠባቦች ፍልስፍና
በጭፍኖች ጉርምስና
በአጉራ ዘለሎች እርግጫ
በሳዲስቶች የግፍ ጡጫ
በራስ ወዳዶች በደል
እናት ሐገር ስትበደል
የእናት ሐገርን ስቃይ
ጣሯን
የእምዬን ምሬት
አሳሯን
ከሞት በማይሻል ዝምታ
ከሞት በማያስጥል ጉምጉምታ
ራሳችንን እጉልበታችን ስር ቀብረን
በእህህ የሆድ ዝማሬ
በውስጥ ዜማ ደንቁረን
ባለግዴታ ትከሻችን
በውዴታችን ሟሙቶብን
ባለብረት ሞራላችን
በእሳት እንደጭድ ላሽቆብን
ከእግር እስከራሳችን መክነን
እናድናት ዘንድ ቢሳነን
ይህቺ ምድር
የዓለም ብርሐን የነበረች
በሀያል ጨለማ አደረች
የሰው ሐገር የነበረች
በሰው ረሐብ አረረች።
እስክንድር ልሳነወርቅ
2006 ዓ/ ም

ተጨማሪ ያንብቡ:   የሚያልፍ ቀን የማያልፍ ስም ይሰጣል! - አገሬ አዲስ
Share