በኦሮምያ ዜጎችን ማሰሩ እንደቀጠለ ነው

ኀዳር ፱(ዘጠኝ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በኦሮምያ የሚታሰሩ ዜጎች ቁጥር መበራከት የአለምን የመገናኛ ብዙሃን ሰፊ ሽፋን ባገኘ ማግስት፣ አሁንም ዜጎችን በሰበብ አስባቡ እያሰሩ ለፍርድ አቅርቦ ማስፈረድ ቀጥሎአል።
አፍሪካ ቀንድ የሰብአዊ መብት ሊግ ያወጠው ሪፖርት እንደሚያሳየው ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በአምቦ ከተማ እና በሚዳ ቀኒ ወረዳ ከ20 ያላነሱ ተማሪዎች፣ መምህራንና አርሶ አደሮች ታስረዋል። እስራቱ የተፈጸመው መንግስት የአካባቢውን መሬት ለኢንቨስተሮች መስጠቱን ተከትሎ በተነሳ ተቃውሞ ነው። ከታሰሩት መካከል
አርሶ አደር ኪጣጣ ረጋሳ፣ ተማሪ ቶሎሳ ተሾመ፣ ድሬ ማሾ፣ ታሪኩ ቡልሾ፣ ያለው ባንቲ፣ ቢንያሳ ኢባ፣ ተስፋይ ቢይነሳ እና ነጋዴ መግስቱ ሞሲሳ ይገኙበታል።
እንዲሁም ከመጪው ምርጫ ጋር በተያያዘ በክልሉ በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች የጅምላ እስራቶች እየተከናወነ ነው። ብዙዎቹ በህጋዊ መንገድ የሚታገለው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ አባላት በመሆናቸው ብቻ መታሰራቸውን የሚገልጸው ሊጉ፣ በጅማ የድርጅቱ አመራሮች የሆኑት አቶ አጀብ ሼክ ሙሃመድ፣ አቶ ሙሃመድ
አሚን ካልፋና አቶ ነቢብ ጀማል ታስረው 2 አመት ከስድስት ወር እንደተፈረደባቸው ጠቅሷል።
ተፈጸመ ስለተባለው እስራት ያነጋገርናቸው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ዋና ተጠሪ አቶ በቀለ ነገአ ሰዎቹ በሃሰት እንደተፈረደባቸው አረጋግጠዋል። መሳሪያ የሌላቸውን ህገወጥ መሳሪያ ደብቃችሁዋል በሚል በሃሰት ተመስክሮባቸው መታሰራቸውን አቶ በቀለ አስረድተዋል ከታሳሪዎች መካከል የአቶ አጀብ ሼክ ሙሃመድ
ባለቤት የሆኑት ወ/ሮ አዳነች ለኢሳት እንደገለጹት ደግሞ ባለቤታቸው በሀሰት ተመስክሮባቸው ከታሰሩ ጀምሮ እርሳቸውም በሚደርስባቸው ማስፈራሪያ ከቤት ለመውጣት መቸገራቸውን ገልዋል። ወደ ጎረቤት ሄደው እሳት እንዳይጭሩ ከመከልከላቸውም ሌላ፣ ቤታቸው በደንጋይ የደበደባል። የባለቤታቸው ወንድም ተመሳሳይ ችግር ስላጋጠመው ስራውን ትቶ ወደ ከተማ መምጣቱንም ወ/ሮ አዳነች ተናግረዋል። አምነስቲ ኢንተርናሽናል ሰሞኑን እስር ቤቶች በኦሮሞ ተወላጆች መሞላቱን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ አለም የመገናኛ ብዙሃን ሰፊ ሽፋን ሰጥተውታል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የእስክንድር ጥሪና የቀጠለው የኢትዮጵያ ቢቲኒ ግስጋሴ | Hiber Radio Special program
Share