June 18, 2014
6 mins read

የዘ-ሐበሻ 6ኛ ዓመት በሚኒሶታ በድምቀት ተከበረ፤ ጋዜጠኛ አህመድ ዋሴ የዓመቱ ምርጥ ሰው ሆነ

ahmed wasse with tamagne beyene 2
(ጋዜጠኛ አህመድ ዋሴ ከታማኝ በየነ እጅ ሽልማቱን ሲቀበል)

(ዘ-ሐበሻ) በሚኒሶታ የዘ-ሐበሻ ደጋፊዎች እና ተጋባዥ የክብር እንግዳው አርቲስትና አክቲቪስት ታማኝ በየነ በተገኙበት የዘ-ሐበሻ ጋዜጣና ድረገጽ 6ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል በድምቀት ተከበረ። በዚሁ የዘ-ሐበሻ 6ኛ ዓመት በዓል ላይ በሚኒሶታ መልካም ነገር ለማህበረሰባቸው ካደረጉ ወገኖች መካከል አንዱ የሆነውና በሚኒሶታ የኢትዮጵያ ራድዮ ላይ ላለፉት 25 ዓመታት ያገለገለው ጋዜጠኛ አህመድ ዋሴ የዓመቱ ምርጥ ሰው በሚል በዘ-ሐበሻ ተሸልሟል።

በዓሉን በንግግር የከፈተው የዘ-ሐበሻ መስራችና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ሔኖክ ዓለማየሁ የዘ-ሐበሻን አመሰራረትና ዓላማዋን አስረድቷል። “ዘ-ሐበሻ በሱዳን የ1 ዓመት የ6 ወር የስደት፣ በሊቢያ የ3 ወር እስርና በቱርክ የዓመት ከግማሽ የስደት ሕይወት ውስጥ ታስባ በሚኒሶታ የተቋቋመች የመረጃ ምንጭ ናት” ያለው ጋዜጠኛው “እነዚያ በስደት የቆየሁባቸው ሃገሮች ውስጥ የነበረው ፈተና በአሜሪካን ሃገር እንዲህ ያለውን ጠንካራ ሚዲያ ለመፍጠር ምክንያት ሆኖኛል” ሲል ገልጿል።

ስለዘ-ሐበሻ ከዩኒቨርሲቲ ኦፍ ሚኒሶታ ፕሮፌሰር ሰለሞን ጋሻው ባደረጉት ንግግርም ዘ-ሐበሻ በሚኒሶታ ካለው ኢትዮጵያ አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ እያሳየ የመጣውን ጠንካራ ተሳትፎ አድንቀው ዘ-ሐበሻን ለማጠናከር ሁሉም እንዲረባረብ ጠይቀዋል። በተለይ በኢትዮጵያ ውስጥ ስላለው የፕሬስ አፈናና የወቅቱን ወቅታዊ ጉዳዮች የዳሰሱት ፕሮፌሰር ሰለሞን ጋሻው “ዘ-ሐበሻ ከፖለቲካው ጉዳይ በተጨማሪም እንደ ጤናዳም ያሉ በህክምና ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ ድረገጾችን በመጨመር ሕብረተሰቡን እያስተማረ ነው” ካሉ በኋላ ዘ-ሐበሻ በኢትዮጵያ እንዳይታይ በመንግስት የታገደ ድረገጽ ቢሆንም መረጃዎቹ ግን ሕዝቡ ጋር በተዘዋዋሪ መንገድ እንደሚደረሱ አስታውሰዋል።

የእለቱ የክብር እንግዳ የነበረው ታዋቂው አክቲቪስት እና አርቲስት ታማኝ በየነ “እስካሁን ድረስ የምታዩኝ በኢሳት ፈንድራይዚንግ ላይ ነበር። ኢሳትን አቋቁመን የልባችንን ተንፈስ እያልን ነው ያለነው። አሁን ለዘ-ሐበሻ 6ኛ ዓመት እንድገኝ ጥሪው ሲቀርብልኝ የመጣሁት ትልቁ ምክንያት ሔኖክ በወጣትነት እድሜው ሰው ሃገር ላይ መጥቶ እንደማንም ሕይወቱን መኖር ሲችል ለሃገሬ ያገባኛል በሚል የበኩሉን ጥረት ዘ-ሐበሻን በመክፈት እያደረገ መሆኑን ስመለከት እንዲህ ያለ ጥረት በሰው ሃገር ላይ ሆነው የሚያደርጉ ወጣቶችን ለማገዝ ካለኝ ፍላጎት ነው” ብሏል። ታማኝ በዕለቱ ለዘ-ሐበሻ ማጠናከሪያ የሚውል የተዘጋጀውን የጨረታ ፕሮግራም የመራ ሲሆን በስፍራው የነበረው የዘ-ሐበሻ ደጋፊም በንቃት በመሳተፍ ድጋፉን አሳይቷል። (ቪድዮዎችን እንለቅላችኋለን)

የዚህ ፕሮግራም አንዱ አካል የነበረው የዓመቱ የሚኒሶታ ምርጥ ሰው ሽልማት የነበረ ሲሆን በዚህም በከተማችን ላለፉት 25 ዓመታት እየተሰራጨ ያለውን የኢትዮጵያ ድምጽ ራድዮ በማገልገል ለወገኖቹ ትልቁን ሥራ የሰራው ጋዜጠኛ አህመድ ዋሴ ሽልማቱን ከታማኝ በየነ እጅ ተቀብሏል። ስለአህመድ ሕይወትና ሥራ አቶ ዘውዴ በስፋት ጠለቅ ያለ መረጃ ያቀረቡ ሲሆን በስፍራው የነበረው ሕዝብም ሽልማቱ ይገባዋል ሲል የዘ-ሐበሻን ምርጫ አድንቋል። አህመድ ከሽልማቱ በኋላ ባደረገው ንግግር “ሽልማቱ ለኔ ይገባኛል ብዬ አላስብም። በዚህ ከተማ በንግዱም ዘርፍ፣ በሌላውም ነገር ሕዝቡን እያገለገሉ ያሉ ብዙ ሰዎች አሉ። ይህ ሽልማት ለኔ ሳይሆን ለነርሱ ነው የሚገባው። ሆኖም ግን ዘ-ሐበሻ እኔን በመሸለሙ ደስ ብሎኛል፤ አመሰግናለሁ” ብሏል።

ዘ-ሐበሻን ለማጠናከር የተዘጋጀውን የአጼ ቴዎድሮስ ምስል ጨረታ ያሸነፉት የአቶ አስናቀ ቤተሰቦች በአንድ ላይ
የዘ-ሐበሻ 6ኛ ዓመት በሚኒሶታ በድምቀት ተከበረ፤ ጋዜጠኛ አህመድ ዋሴ የዓመቱ ምርጥ ሰው ሆነ 1
refugnee
Previous Story

የዓለም ስደተኞች ቀን ጁን 20 በመላ ዓለም ይከበራል

Posterhealthfair2014 1
Next Story

የደ/ሰ/መ/ቤ/ክ ፓሪሽ ፕሮግራም አመታዊ ሄልዝፌር (በሚኒሶታ ለምትኖሩ ወገኖቻችን ነፃ የህክምና ምርመራና ትምህርት ቀን)

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop