June 11, 2014
5 mins read

በሐረር የተገኘ የጅምላ መቃብር ጥያቄ አስነሳ

Haraer ethiopia

በሐረሪ ክልል ሐረር ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው ሐማሬሳ ቀበሌ ውስጥ ሰሞኑን በተገኘ የጅምላ መቃብር ምክንያት አንዳንድ የከተማው ነዋሪዎች ጥያቄ ማንሳታቸውን ምንጮች ለሪፖርተር ገለጹ፡፡

ሰሞኑን አካባቢው ለጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጆች ሼድ መሥሪያ ሲቆፈር በጅምላ የተቀበሩ ሰዎች አፅም መገኘቱን የጠቆሙት ምንጮች፣ የከተማው አስተዳደር ቁፋሮ እንዲቆም ቢያዝም፣ አንዳንድ ነዋሪዎች ሙሉ በሙሉ መቆፈር እንዳለበትና በጅምላ የተቀበሩት ዜጎች ቁጥር መታወቅ እንዳለበት በመግለጽ ተቃውሞ ማቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡

ቦታው በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት የሦስተኛው ክፍለ ጦር መቀመጫ እንደነበርና በደርግ ዘመነ መንግሥትም የጦር ካምፕ ሆኖ መቀጠሉ ታውቋል፡፡

ምንጮች እንደሚሉት በተለይ በደርግ ዘመነ መንግሥት በርካታ ወጣቶችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገድለው በጅምላ ተቀብረዋል፡፡ ኢሕአዴግ አገሪቱን እንደተቆጣጠረ በተለያዩ አካባቢዎች በጅምላ የተቀበሩ ዜጎች አስከሬንን ማስወጣቱ ይታወሳል፡፡ በሐረር ከተማም በዘመኑ በሰዎች ላይ ግድያ በጅምላና በተናጠል የተፈጸመ ቢሆንም፣ የተቀበሩበት ቦታ አለመታወቁና ጠቋሚ በመጥፋቱ እስካሁን ድረስ አስከሬኖች ሳይገኙ መቆየታቸውን ምንጮች አስረድተዋል፡፡

ኢትዮጵያን ለ17 ዓመታት ሲመሩ የነበሩት ሌተና ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያምም፣ አሁን የጅምላ መቃብሩ በተገኘበት ቦታ ላይ የነበረው የሦስተኛው ክፍለ ጦር አባል እንደነበሩ የገለጹት ምንጮች፣ ሥልጣን ከያዙ በኋላ ተቃውሞ ባደረጉ የኢትዮጵያ ወጣቶችና የወቅቱን ሥርዓት ተቃዋሚዎች ላይ የተፈጸመው ጭፍጨፋ ሁሉንም የአገሪቱን ክልሎች ያዳረሰ ለመሆኑ፣ የሐረሩ የጅምላ መቃብር መገኘት ማጠናከሪያ ማስረጃ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በሐረር በተገኘው የጅምላ መቃብር ምክንያት በወቅቱ ለተሰው ዜጎች ማስታወሻ እንዲሆን ሐውልት ሊቆም እንደሚገባ አንዳንድ ነዋሪዎች የከተማ አስተዳደሩን መጠየቃቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

በሐረሪ ክልል ሐረር ከተማ አካባቢ ተገኘ ስለተባለው የጅምላ መቃብርና አንዳንድ ነዋሪዎች አንስተዋል ስለተባለው ተቃውሞ ማብራሪያ እንዲሰጥ የክልሉ መስተዳደር ለመጠየቅ ቢሞከርም ምላሽ ማግኘት አልተቻለም፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የክልሉ ከፍተኛ ባለሥልጣናት እንደገለጹት፣ የጅምላ መቃብር መገኘቱ እውነት ነው፡፡ የተገኘውም ቦታውን ለጥቃቅንና ለአነስተኛ ተደራጆች ሼድ ሠርቶ ለመስጠት ቁፋሮ ሲደረግ መሆኑን አረጋግጠው፣ አንዳንድ የግል አጀንዳቸውን ለማራመድ ሰበብ የሚፈልጉ ግለሰቦች ሕዝቡን ከለላ አድርገው ለመንቀሳቀስ ሞክረዋል ብለዋል፡፡ ሕዝቡ ሊተባበራቸው ባለመቻሉ አፍረው እንቅስቃሴያቸውን ማቆማቸውንም አስረድተዋል፡፡ ቁፋሮውም እንዲቆም ተደርጎ የክልሉ መንግሥት እየተነጋገረበት መሆኑን አስረድተዋል፡፡

Source: Ethiopian Reporter

Previous Story

በጋምቤላ ክልል ጎደሬ ልዩ ስሙ ዱንቻ አማርኛ ተናጋሪ ዜጎች ተፈናቀሉ ‪

addis ababa realethiopia 141
Next Story

በአዲስ አበባ የመሬት አስተዳደር ቢሮና በሌሎች ተቋማት ላይ ፓርላማ ዕርምጃ እንዲወስድ ተጠየቀ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop