ቀነኒሳ በቀለ ሞ ፋራህን በግማሽ ማራቶን ቀጣው፤ መሠረት እና ጥሩነሽ 2ኛና 3ኛ ወጡ

(ዘ-ሐበሻ) ዛሬ በሰሜን እንግሊዝ ታላቁ የግማሽ ማራቶን ሩጫ ውድድር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የተሳካ ውጤት አስመዘገቡ። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለኢትዮጵያዊያን አትሌቶች ራስ ምታት ሆኖ የነበረውና በ5 ሺህ እና በ10 ሺህ ሜትር የወርቅ ሜዳሊያዎችን ሲጠቀልል የነበረው እንግሊዛዊው አትሌት ሞ ፋራህ ዛሬ በሃገሩ ላይ በቀነኒሳ በቀለ ተቀጥቷል።

ቀነኒሳ በቀለ በዛሬው ውድድር ሞ ፋራህን ያሸነፈው ውድድሩን በአንድ ሰዓት ከ08 ደቂቃ በማጠናቀቅ ሲሆን ትውልደ ሶማሊያዊ እንግሊዛዊው ሞ ፋራህ በአንድ ሰዓት ከ09 ደቂቃ ሁለተኛ በመውጣት ውድድሩን ሲያጠናቅቅቅ አትሌት ኃይሌ ገብረ ሥላሴ ደግሞ ሶስተኛ በመሆን ውድድሩን አጠናቋል፡፡ እንደ ስፖርት ተንታኞች ከሆነ ኃይሌ ለቀነኒሳ ማሸነፍ ትልቁን ሚና ተጫውቷል። የቀነኒሳ ማሸነፍም ኢትዮጵያ ወደፊት በማራቶን ተተኪ አትሌቶችን እያገኘች መሆኑን የሚያሳይ መሆኑን አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ።

በተመሳሳይ ዛሬ መስከረም 5 /2005 (ሴፕቴምበር 15 ቀን 2013) ዓ/ም የተካሄደው የሰሜን እንግሊዝ ታላቁ ግማሽ ማራቶን ሩጫ መሠረት ደፋርና ጥሩነሽ ዲባባ ሁለተኛና ሶስተኛ በመውጣት አሸንፈዋል። በዚህ የሴቶች ግማሽ ማራቶን ውድድር ኬንያዊቷ አትሌት ጀፕቶ አንደኛ ስትወጣ አትሌቷ ጅፕቶ ከአስር ዓመት በፊት በፓዉላ ራድክሊፍ የተያዘ የ1፡05፡40 ሰዓት የቦታው ሪከርድ ለመስበር 9 ሰከንድ ብቻ እንደቀራት ከሥፍራው የተገኘው መረጃ ያመለክታል። የዚህ ውድድር ያለፈው ዓመት አሸናፊ ኢትዮጵያዊቷ ጥሩነሽ ዲባባ ነበረች። በ5 ሺህ እና በ10 ሺ ሜትር በድል ያስጨፈሩን መሰረት እና ጥሩነሽ በዚህ የግማሽ ማራቶን ያገኙት ውጤት የሚያኮራ ነው።

እንኳን ደስ ያለን!!
https://www.youtube.com/watch?v=U9vRc6XCUME

ተጨማሪ ያንብቡ:  የወልዲያ ከተማ ወቅታዊ ሁኔታ
Share