ከቦጋለ አበበ
የዓለምን እግር ኳስ በበላይነት የሚመራው ፊፋ የዓለም አገራት ወራዊ የእግር ኳስ ደረጃን ይፋ አድርጓል። በዚህም መሰረት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን «ዋሊያዎቹ» አምስት ደረጃዎችን አሻሽለዋል።
ኢትዮጵያ ያሻሻለችው አምስት ደረጃ ከአፍሪካ ሰላሳ አንደኛ ደረጃ ላይ ሲያስቀምጣት በዓለም ያላት ደረጃ ደግሞ መቶ ሰባተኛ ሆኗል።
በአፍሪካ ዋንጫ ላይ አስደናቂ እንቅስቃሴ በማሳየት የስፖርት ቤተሰቡን ያስደመሙት ዋልያዎቹ፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ እግር ኳስም ሆነ በዓለም ያላትን ደረጃ እንድታሻሽል ትልቅ አስተዋፅኦ አበርክተዋል።
ዋልያዎቹ በአፍሪካ ዋንጫ ጥሩ ጨዋታ ቢያሳዩም በውጤት ረገድ ስላልተሳካላቸው፣ ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት ወራት በፊፋ የነበራት ደረጃ የቀነሰ ነበር። ይሁን እንጂ ዋልያዎቹ ከአፍሪካ ዋንጫ መልስ በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ እያሳዩት ያለው ብቃትና ውጤት ደረጃቸውን መልሶ አሻሽሎታል።
በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ በምድብ አንድ ከደቡብ አፍሪካ፣ መካከለኛው አፍሪካና ቦትስዋና ጋር የተደለደሉት ዋልያዎቹ ባለፈው ወር ቦትስዋናን በሜዳቸው አንድ ለዜሮ በሆነ ውጤት ማሸነፋቸው ይታወሳል። ይህም ኢትዮጵያ የፊፋን ደረጃ ለማሻሻሏ ምክንያት ሆኗል።
በመጪው ዓመት ብራዚል በምታዘጋጀው የዓለም ዋንጫ ለመሳተፍ ዋልያዎቹ የተስተካከለ መንገድ ላይ ናቸው። ምድባቸውንም በሰባት ነጥብ እየመሩ ይገኛሉ። ሰባት ነጥቡን የሰበሰቡትም በሦስት ጨዋታዎች ሲሆን፣ በቀጣይም ሦስት የማጣሪያ ጨዋታ ይቀራቸዋል።
ዋልያዎቹ አርባ የአፍሪካ አገራት በአስር ምድብ ተደልድለው አስሩ ውስጥ ለመግባት ከምድባቸው የተሻለ እድል አላቸው። ይሁን እንጂ ዋልያዎቹ ይህን ምድብ አልፈው አስር አገሮች ተፋልመው አምስት አገሮች ብቻ ወደ ዓለም ዋንጫ ለማለፍ የሚያደርጉትን ፍልሚያ ለመቀላቀል ከቀሪዎቹ ጨዋታዎች ነጥብ መሰብሰብ ይጠበቅባቸዋል።
ዋልያዎቹ በሜዳቸው መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክንና ቦትስዋናን አሸንፈው ስድስት ነጥብ ሲሰበስቡ ወደ ደቡበ አፍሪካ ተጉዘው ደግሞ ነጥብ ተጋርተው መመለስ ችለዋል። በቀጣይ ደግሞ ከመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክና ቦትስዋና ጋር ከሜዳቸው ውጪ የማጣሪያውን ጨዋታ ያካሂዳሉ። ደቡብ አፍሪካን ደግሞ በሜዳቸው ያስተናግዳሉ።
በፊፋ የደረጃ ሰንጠረዥ መሰረት ከአፍሪካ ኮትዲቯር ደረጃዋን እንዳስጠበቀች ሲሆን፤ ሻምፒዮኖቹ ናይጄሪያዎች ደረጃቸውን ቀንሰዋል። ኮትዲቯር ከአፍሪካ አንደኛ ስትሆን በዓለም ያላት ደረጃ ደግሞ በአንድ ጨምሮ አስራ ሁለተኛ ሆናለች።
ጋና ሁለት ደረጃ ቀንሳ ከዓለም ሃያ ሁለተኛ ስትሆን፤ በአፍሪካ ያላትን የሁለተኝነት ደረጃ አላስደፈረችም። ጥቋቁር ከዋክብቱ በመባል የሚታወቁት ጋናውያን በአፍሪካ እግር ኳስ ታላላቅ ከዋክብትን ያፈሩ ቢሆኑም የአፍሪካ ዋንጫን ካነሱ ሰላሳ ሁለት ዓመት ሊሆናቸው ወራት ቀርተዋል።
ማሊ በአፍሪካ የሦስተኛነቱን መንበር ተቆናጣለች፤ በዓለም ያላት ደረጃ ደግሞ ሁለት ቀንሶ ሃያ ስድስተኛ ላይ ተቀምጣለች። የአፍሪካ ዋንጫ ሻምፒዮኗ ናይጄሪያ በበኩሏ ከአፍሪካ አራተኛ ብትሆንም በዓለም ያላት ደረጃ በአንድ ቀንሶ ሰላሳ አንደኛ ሆናለች። ናይጄሪያ ደረጃዋ ለመቀነሱ ዋነኛ ምክንያት ባለፈው ወር በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ በሜዳዋ ኬንያ ነጥብ ስላስጣለቻት ነው።
አልጄሪያ አንድ ደረጃን ዝቅ ብላ ከአፍሪካ አምስተኛ ከዓለም ደግሞ ሰላሳ አምስተኛ ሆናለች። ባለፈው የአፍሪካ ዋንጫ አስደናቂ ብቃት ያሳየችው ቡርኪናፋሶ የደረጃ ለውጥ ሳታሳይ ከአፍሪካ ስምንተኛ ከዓለም ደግሞ ሃምሳኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች።
የኢኳቶሪያል ጊኒና ጋቦን በጋራ ያዘጋጁትን የአፍሪካ ዋንጫን ያነሳችው ዛምቢያ ባለፈው በተካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ግጥሚያ ላይ ደካማ አቋም አሳይታለች። ከጊዜ ወደ ጊዜ ደረጃዋም እየቀነሰ መጥቷል። ዛምቢያ በዚህ ወር ከአፍሪካ ሰባተኛ ደረጃን ብትይዝም በዓለም ያላት ደረጃ በዘጠኝ ቀንሶ አርባ አምስተኛ ሆናለች። በርካታ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን በማንሳት የሚስተካከላት የሌለው ግብፅ ከአፍሪካ አስራ አምስተኛ ከዓለም ደግሞ ስድሳ ስምንተኛ ደረጃን አግኝታለች። ግብፅ ይህን ደረጃ ልትይዝ የቻለችውም ሰባት ደረጃዎችን አሻሽላ ነው። ለዚህም በዓለም ዋንጫ ማጣሪ ያሳየችው ጠንካራ አቋም ምክንያት ሆኗል።
በዓለም ደረጃ ስፔን፤ ጀርመንና አርጀንቲና የደረጃ ለውጥ ያልታየባቸው አገሮች ሆነዋል። እነዚህ አገሮች ከዓለም እንደየቅደም ተከተላቸው ከአንድ እስከ ሦስት ያለውን ደረጃ ይዘዋል። ክሮሺያ ደግሞ አምስት ደረጃዎችን አሻሽላ ትከተላለች።
ፖርቹጋል ሁለት ደረጃዎችን አሻሽላ ከዓለም አምስተኛ ደረጃን አግኝታለች። በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ አጣብቂኝ ውስጥ የምትገኘው እንግሊዝ፣ ሦስት ደረጃዎችን ዝቅ ብላ ሰባተኛ ሆናለች። እንግሊዝ ለደረጃዋ መቀነስ ምክንያት በተለያየ ጊዜ ባደረገችው የወዳጅነትና የማጣሪያ ጨዋታዎች ላይ ያሳየችው ደካማ አቋም ነው።
ጣልያንም በተመሳሳይ ሦስት ነጥብ ቀንሳ እንግሊዝን ትከተላለች። የበርካታ ከዋክብት መፍለቂያዋ ብራዚል አንድ ደረጃ ዝቅ ብላ ከዓለም አስራ ዘጠነኛ ላይ መቀመጧ የስፖርት ቤተሰቡን ያስገረመ ጉዳይ ሆኗል።
ብራዚል በፊፋ የተሰጣት ደረጃ ትክክል ይሁንም ስህተት ለአገሪቷ እግር ኳስ ደጋፊ መጥፎ ዜና ሆኗል። ብራዚል በመጪው ሰኔ የኮንፌዴሬሽን ዋንጫን የምታስተናግድ አገር ከመሆኗ በተጨማሪ በቀጣይ ዓመት የዓለም ዋንጫ አዘጋጅ መሆኗ ይታወቃል።