”ተቃዋሚ ፓለቲከኞች” ከተቃውሞው  መግለጫው በኋላስ? – ፊልጶስ

እንደመግቢያ፥
ይብላኝ ለአንች!—
ቦርቀሽ ሳትጨርሽ
ሩጠሽ – ሳትደርሽ
ሳይጠናም – አጥንትሽ፤
ደምሽ – ለፈሰሰው
የሴትነት ክብርሽ፣ በግፍ ለተቀማው፤
ገና በማለዳው፣ ቀኑ ለመሸብሽ
ጠላቶችሽማ ገና ይመጣሉ፣ ለታናሽ እህትሽ
ያንች ስላልበቃ መከረ-ስቃይሽ።—-

ይብላኝ ለአንተ !——
ለአገር -ለወገን ብለህ
የቀረህው -እንደወጣህ
መሰዋት የሆንከው፣ ሳትሰስት ለነፍስህ
አራጆችህስ ተፈቱ – በኩራት ሄዱ
በደም – በአጥንትህ ላይ እየተረማመዱ።
——-
ፓለቲካ የሥልጡኖች ሥርዓት ነው። ፓለቲከኛም መሆን መሰልጠንና ሰባአዊ መሆን ነው። ከራስ በላይ አገርንና ህዝብን ማስቀደም ነው። በአጠቃላይ ሰው መሆን ማለት ነው።

ስልጡን ፓለቲከኞች ለአገራቸውና ለህዝባቸው እድገት የሚበጅ ሥራዓት ይመሰረታሉ። ከድህነት ይልቅ፣ ብልጽግናን፣ ከጦርነት ይልቅ ሰላምን፣ ከልዮነት ይልቅ አንድነትና እና አብንሮነትን በማስፈን ትውልድና ዘመን የሚዋጅ ስርዓት ይገነቡበታል። በእኛ አገር ደግሞ ከዚህ በተቃራኒው ይፈጽምበታል።

እውነቱን ለመናገር በአገራችን ፓለቲካም ሆነ ፓለቲከኛ አለ ማለት ይከብዳል። አለ ከተባለም፤ በጎሳና በበታችነት መንፈስ ታውሮ አገርን ማፍራሻ፣ እርስ -በርስ መገዳደያ፣ ሀዝብን ከህዝብ መከፋፈያና ማረጃ፣ ከደሃ አርሶ አደር እፍ እየነጠቁ በአቋራጭ ሃብት ማካበቻና የጎጥን ሰው መጥቀሚያ፣ ክህደት፣ ሴራና ጥሎ ማለፍ፤ በአጠቃላይ እኩይነት የተሞላባት በመሆኑ፤ አገርና ህዝብ ህልውናው አደጋ ላይ ወድቆ፤ አሁን ላለንበት ታሪክና ትውልድ ይቅር ከማይለው ደረጃ ላይ ደርሰናል።ለዚህ ደግሞ መንግሥት ነኝ ከሚለው ገዥ አካል ባልተናነሰ በተቃውሞ ጎራ የተሰልፋትም እኩል ተጠያቂዎች ናቸው።
የወያኔ ፋጣሪዎችንና ገዳይ -አስገዳይ የነበሩትን የእነ እቶ ስበሃት ነጋን መፈታት ተከትሎ ፤ በኦንጋዊ ብልጽግና ገዥ ኃይል ህዝብ ተክዷል፣ ተንቋል፣ ተዋርዷል፣ በቁስሉ ላይ ጨው ተነስንሷል።

የአማራ ክልል ገዥዎች ደግሞ እንደ ትላንቱ ሁሉ ዛሬም ህሊናቸውን ሽጠውና በወገናቸው ደም እየታጠቡ፤ ” የወያኔዎች መፈታት” ትክክል ውሳኔ መሆኑን ብቻ አይደለም፤ ጦርነቱ እንደተጠናቀቀ አድርገው፣ ከኦነጋዊ ብልጽግና የተሰጣቸውን የቤት ሥራ ለዚያ መከራኛ ህዝብና በተለይም ለአማራ እታገላለሁ ለሚለው ለማሳመን ሲላላጡ ይታያሉ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በኢትዮጵያ ፀሐይ ያጠላው ጥቁር ደመና ቹቹ አለባቸው (ከፍትሕ መጽሔት)

—–ሥልጣንም ይያዛል፣ ሥልጣን ከተባለ

ህሊና ተሽጦ፣ ለሆድ እየዋለ።—-
ከምንም በላይ በህዝብ መሰዋትነት የተገኘው የአገርን አንድነት የመታደግና ህልውናን የማሰጠበቅ ትግል በዜሮ ተባዝቷል። ገዥው ኃይል በተደጋጋሚ የሚናገረው ውሸትና የሚፈጽመው ክህደት፤ በአንድ አገር መንግሥትና ህዝብ መሃከል የሚኖረው መተማመን እየተሸረሸረ መምጣቱ ገሃድ እየወጥ ነው። አገርም ያለባለቤት፣ ህዝብም ያለመሪ እየቀረ ነው። ይህ ደግሞ የኦነጋዊ ብልጽግና መንግሥትና ወያኔ ያላቸው ችግር ”እኔ ነኝ ተረኛ ” ከሚል እንጅ፤ ”በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊነት ላይ ያላቸው አቋም አንድ ነው ።” የሚለውን ፣ ገዥዎቻቸንም በየግዜው መድርክ ጠብቀው የሚነግሩንን ወደ ተግባር እየቀየሩት ለመሆኑ ማስረጃ ይሆናል።

ታዲያ በዚህ አገርና ህዝብ ፈትና ላይ በወደቀበት ግዜ፤ ሶስት ”ተቃዋሚ” የፓላቲካ ፓርቲዎች 1/ አብን፣ ኢዜማና እናት ፓርቲ የእነ አቶ ስበሃት ነጋን መፈታት በመቃወም፤ መንግሥት ወሳኔውን እንዲቀለብስ የሚያሳስብ መግለጫ አውጥተዋል።

ከዚህ ላይ እውነትኛ ወይም ስልጡን ተቃውሚ ዓላማው በመንግሥትና በህዝብ መሃከል ያለውን ክፍተት ለማጥበብና፤ እንዲሁም ገዡ ኃይል ለህዝብና ለአገር አንድነት ቅድሚያ እንዲሰጥ ማድርገ እንጂ በአቋራጭ ስልጣን ለመያዝ ወይም ግዚያው የፓለቲካ ትርፍ ለማግኘትአለመሆኑ ሊሰመርበት ይገባል።

የእነ እቶ ስበሃትን ”ምህረትና ይቅርታ” በሚል መንግስት የመፍታቱን ውሳኔ እንዲቀለበስ የጠየቁ ፓርቲዎች፤ ኦነጋዊ-ብልጽግና የዲሞክራሲ ሽታ በሌለብት ተወዳደርን ብለው፤ ለህዝብ የገቡትን ቃልና የፓለቲካ መርሃ -ግብራቸውን “ ዓላማ “’ የሚሉትን ሁሉ ረስተው፤ የስልጣን ፍርፋሪ ላይ የተሰማሩ፤ ከገዥው ጋር ሥልጣን የተጋሩ ናቸው። ታዲያ መግለጫው የምር ነውን?

የአሁኑ ወቅታዊ ጥያቄ ”ተቃዋሚ ፓለቲከኞች” ከተቃውሞው መግለጫው በኋላስ? መንግሥት ወሳኔውን ካልቀልበሰ ፤
– ቀጣይ የትግል ስልታችሁ ምንድነው ?
– ገዥውንስ በምን ኃይላችሁ ነው ውሳኔውን እንዲቀለብስ የምታስገድዱት?
– ወይስ እንደተለመደው የመግለጫ የማውጣት ሱስ ነው?
– ወይስ ገዥው ሌላ አጀንዳ እስኪሰጣችሁ ትጠብቃላችሁ?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ፍሬወይኒ መብርሃቱ እንደ ፋና ወጊ!  -  አበጋዝ ወንድሙ

የአገርና የህዝብ አንድነትን ለመታደግ ከፈለጋችሁ፤ ኦነጋዊ ብልጽግና አገርንና ህዝብን ሳይበታትን፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከመግለጫ ያለፈ ስልታዊ እርምጃ በመውሰድ የመንግሥትን ውሳኔ ማሻር ትችላላችሁ።ይኽውም፤
አንደኛ/ በመንግሥት ውስጥ ያላችሁን ስልጣን ልቀቁ፤ ገዥው ኃይል አሁንም በውሳኔው ከጸና ሁለትኛውን ርምጃ ውሰዱ። ሁለትኛው/ የፓርላማ ወንበራችሁን ልቀቁ፤ አሁንም ገዥው ኃይል በውሳኔው ከጸና ሶስተኛውን ርምጃ ውሰዱ። ሶስተኛው/ ህዝብን ለተቃውሞ ሰልፍ ጥሩ። ከዚህ በኋላ እንደ ሁኔታው እስከ የሥራ ማቆም አድማ መጥራት ሊደርስ ይቻልል።

ከላይ ያነሰዋቸው ጉዳዮች የተለምዱና ማንም የሚያውቃቸው የትግል ስልቶች ናቸው፤ ተቃውሚ ፓርቲዎችስ ይኽ ጠፍቷቸው ነወይ ሊባል ይችላል። ወይም በዚህ የአገር ህልውና አደጋ ላይ በውደቀብት ሰዓት ይህ መታሰብ የለበትም ሊባል ይቻላል። የኔ መልስ ግን መንግሥት ተብየው እነ እቶ ስበሃትን ሲፈታ ከህዝብ ጋር መለያይቱንና ለተከፈለው መሰዋአትነትም ምንም ደንታ እንደሌለው፤ አፍቅሮ ወያኔነቱን አሳይቷል። በተጨማሪም ኦነንጋዊ ብልጽግና የኢትዮጵያን ህዝብና አደጋ ላይ የሚጥል ውሳኔ ሲወስን ይህ የመጀመሪያ እንዳልሆነ ሁሉ፤ ለዚህ ዓይነቱ አድራጎቱ ልጓም ካልተደርገለት ፣ በለመደው መንገድ መጓዙ አይቀርም።

አንድ የኦርሞኛ አባባል አለ፤ ”ዳገቱን መውጣት ካቃተህ፤ በቁልቁለቱ ተንደርደር።” ኦነጋዊ-ብልጽግና ተረኛ አገዛዝ ቁልቁለቱን እየተደረድረ ነው።
ታዲያ አሁን ያለው ገዥው ኃይል በየግዜው የሃሰትና የውሸት የድል ሰብካ እያደረግ ፤ አገርንና ህዝብን ወደ ገደሉ ይዞ እንዳይሂድ መታገል የግድ ይለናል።
ለምሳሌ መንግሥት ጦርነቱ በድል እንደተጠናቀቀና ወያኔ ከአሁን በኋላ ምንም ስጋት አንዳላደለ ደጋግሞ ይናገራል ። ይህን ነጭ ውሸት ብቻ ሳይሆን ህዝብን በተለይም በጎንደር፣ በወሎና በአፋር ያለውን ህዝብ ማዘናገት ነው። በዚህ ሰዓት እንኳን ወያኔ በወልቃይት፣ በማይጠምሪና በራያ ቆቦ ግንባር የማጥቃት ጦርነት ከፍቷል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሃሳብን ግልፅ በሆነ ምክንያታዊነት ለመተቸት ካልቻልን...

የተቃዎሚ ፓርቲዎች መገንዘብ ያለባችሁ፤ የትላንት መንግስትን ”እሽሩሩ” ለማንም እንደ አልበጅ ሁሉ፤ የዛሬውም ለማንም አይበጅም። ካለፈው ተምራችሁ ከህዝባችሁና ከአገራችሁ ጎን በተግባር ብትቆሙ ለሁላችንም ይበጀናል። ያለያ ግን መጸሃፍ እንደሚለው በኋላ ” —ለቅሶና ጥርስ ማፋጨት!–” ይሆናል።

ባልፋት ሶስት ዓመታት የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም በወያኔና በኦነጋዊ ተረኛ መንግሥት ምክንያት ምድር የማታውቀውን መከራ ሁሉ ከፍሏል። ታዲያ ይዚህ ሁሉ መከራ ቀንደኛ መስራቾችን፣ ፈጻሚዎችንና አስፈጻሚዎችን ከእስር መፍታት ማንን ለመጥቀም ነው? ማንስ ከማን ሊማር ነው?
ገዥዎቻችን ሆይ!— አሁንም ዋይታችን ስሙ! ፤ እነ አቶ ስበሃትን እንዲፈቱ

የወስናችሁትን ውሳኔ ፍጹም አደግኛ ነውና ውሳኒያችሁን ሻሩ። የህዝብን ድምጽ ሰምታችሁ ውሳኒያችሁን ብትሽሩ ታተርፋበታላችሁ፤ ከህዝብ ጋር የለያያችሁን ገመድ መቀጠል ትችላላችሁ። እንዲያውም ታመኔታን ታተርፋበታለችሁ።

ተቃዋሚ ፓርቲዎችም በተለመደው ፓለቲካችሁ በጥላቻና በብልጣብልጥነት ሳይሆን በቅንነት መንግሥትን ለማሳመን ሞክሩ። ከመግለጫ አልፋችሁ ለአገርና ለህዝብ ስትሉ ጥርስ አውጡ.. በኢትዮጵያና በኢትዮጵታዊነት ስም እሰክ አሁን የነገዳችሁት ይባቃችኋልና፤ ከዚህ በኋላ እንኳን እድሉን አግኝታችኋል የበደላችሁትን ይህን ትውልድ ካሱ፤ አዲስ ታሪክ ጻፋ።

እናም ለዛሬ በዮፍታሄ ንጉሴ ስንኝ ልሰናበት፤ ”—-አገሬ ተባብራ ካልረገጠች እርካብ  ነገራችን ሁሉ የእንቧይ ካብ፤ የእንቧይ ካብ።—‘”

ኢትዮጵያ ለዘልላለም ትኖራለች!!!
——//——-ፊልጶስ
ታህሳስ 2014

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share