የብልፅግና ፓርቲ ዋና ፅ/ቤት አመራሮችና ሰራተኞች በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ለሁለት ቀናት ያደረጉት ውይይት ተጠናቀቀ

የብልፅግና ፓርቲ ዋና ፅ/ቤት አመራሮችና ሰራተኞች በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ለሁለት ቀናት ያደረጉት ውይይት ተጠናቀቀ::
የዋና ፅ/ቤቱ ሰራተኞች “በዘላቂ ድል ወደ ብልጽግና፤የድህረ ጦርነት መዛነፎችና እርምቶች “በሚል ርዕስ በተዘጋጀው ሰነድ ላይ ለሁለት ቀናት ውይይት አካሂደዋል::
በዚህምንበኢትዮጵያውያን አሸናፊነት የተጠናቀቀው የዘመቻ ህብረ ብሄራዊ አንድነት የመጀመሪያ ምዕራፍ በሌሎች ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ድሎች በሚጠናከርባቸው አቅጣጫዎች ላይ መክረዋል፡፡
በጦርነቱ የተጎዳውን ሀገራዊ ኢኮኖሚ የማነቃነቅና በወራሪው ሃይል የከፋ ጉዳት የደረሰባቸውን አካባቢዎች መልሶ መገንባት ሌላው ሀገራዊ ድል የምናስመዘግብበት የዘመቻ ምዕራፍ መሆን አለበት ብለዋል፡፡
አሸባሪውን ሃይል በመዋጋት የታየው ሀገራዊ አንድነት በሌሎች ብሄራዊ አጀንዳዎችም መደገም እንደሚገባው ተወያዮቹ አንስተዋል፡፡
የብልፅግና ፓርቲ ዋና ፅ/ቤት የዘርፍ ሃላፊ የሆኑት ዶ/ር አለሙ ስሜ በሰጡት ማብራሪያ አካታችና አሳታፊ ሀገራዊ የምክክር መድረክ በማካሄድ በሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ መግባባት ላይ ለመድረስ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
እንደ ኢዜአ ዘገባ፤ ይህን ለመፈፀም የሚያስችሉ ተጨባጭ ርምጃዎችም በመንግስት በኩል እየተወሰዱ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡
ከዘመቻ ህብረ ብሄራዊ አንድነት ድሎች በኋላ በሀገር ደረጃ እየተወሰዱ ያሉ ዉሳኔዎችና እርምጃዎች ዘላቂ ሀገራዊ ጥቅምን ታሳቢ ያደረጉ፣የተመዘገቡ ድሎቻችንን የሚያጎለብቱና በተለይ ከምዕራቡ አለም የሚደርስብንን ያልተገባ ጫና የሚያለዝቡ መሆናቸውም በውይይቱ ተነስቷል፡፡
በዋና ጽ/ቤቱ የዘርፍ ምክትል ሃላፊ የሆኑት አቶ ሙሳ አህመድ በበኩላቸው በጦርነቱ ድል አድርገናል፤ እነዚህ ድሎች በሰላም ወቅት በሚመዘገቡ ሌሎች ድሎች ጎልብተው ይቀጥላሉ ብለዋል፡፡
የዋና ፅ/ቤቱ ሰራተኞችና አመራሮችም በዚህ ተከታታይ የትግልና የድል ጉዞ ግንባር ቀደም ሆነው ሚናቸውን እንዲወጡ አቶ ሙሳ አህመድ አሳስበዋል፡፡
(ኢ.ፕ.ድ)

ተጨማሪ ያንብቡ:  በአዲስ አበባ ከተማ ዉስጥ ማንኛዉም አዲስ የእምነት ተቋም እንዳይገነባ መመርያ ወጣ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share