ሕዳር 10/2014 ዓ.ም (አሚኮ) የአሸባሪው የትግራይ ወራሪ ኃይል አባላት ለወረራ በተንቀሳቀሱባቸው የአማራና አፋር አካባቢዎች በርካታ አረመኔያዊ ግፍና በደል መፈፀማቸውን አጋልጠዋል፡፡
የመከላከያ ሠራዊቱንና ሌሎች የጸጥታ ኃይሎችን ምት መቋቋም ተስኗቸው የተማረኩት እነዚህ የአሸባሪው አባላት አጎራባቾቻቸው ያሉትን የአማራና የአፋር ሕዝብ ለማጥፋት ከሽብር ቡድኑ መሪዎች ጥብቅ ትዕዛዝ እንደተሰጣቸው መግለጻቸውን ከመከላከያ ሠራዊት የተገኘ መረጃ ያመላክታል።
በኢፌዴሪ አየር ሃይል በቅርቡ ጥቃት በተፈፀመባቸው አግበ ፣ አጉላዕ ፣ ኩሃ እና እዳጋ ሃሙስ በተሰኙ ወታደራዊ ማሰልጠኛዎች በተሰጣቸው የአጭር ጊዜ ስልጠና ለግዳጅ መሰማራታቸውን ምርኮኞቹ ገልጸዋል፡፡
በከሃዲዎቹ ብርጋዴር ጄኔራል አብርሃ ድንኩል፣ ኮሎኔል ዋልታ መኮንን፣ ኮሎኔል አፈራ አሰፋ እና ሌሎች የሽብርተኛው ወታደራዊ ክንፍ አመራሮች እየታዘዙ እስከ ተንታ፣ ወረኢሉ እና አጣዬ ሾልከው በመግባት ሕዝቡን በማፈናቀል፣ ወጣቶችን በአሰቃቂ ሁኔታ በመረሸን፣ ሴቶችን በመድፈር፣ ንብረት በመዝረፍና በማውደም በርካታ አፀያፊ ተግባራትን መፈፀማቸውን በመከላከያ ሠራዊት የተማረኩት አባላት አረጋግጠዋል፡፡